ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የዘመን መለወጫን በዓል አስመልክተው አባታዊ ቃለ በረከት አስተላለፉ።

መስከረም ፩ቀን ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የፌስቡክ ገጽ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

“ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕረትከ፤ወይጸግቡ ጠላተ ገዳም።”
“በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል።” መዝ ፷፬÷፲፩

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

ከሁሉ አስቀድሜ ልዑል እግዚአብሔር አምላካችን ያለፈውን ዓመት በሰላምና በጤና በሕይወት ጠብቆ አሁን ላለንበት ጊዜና ሰዓት ያደረሰን ፈጣሪ ስሙ የተመሰገነ ይሁን።

ውድ የሰላምና የፍቅር ተምሳሌት የሆነችው የበረሃዋ ንግስት የድሬዳዋ ከተማና አካባቢው ነዋሪዎች እንዲሁም በሀገር ውስጥና በውጪው ዓለም የምትገኙ ውድ ኦርቶዶክሳውያን የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንና መላው የሀገራችን ሕዝቦች በሙሉ።

እንኳን ለ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም በሰላምና በጤና አደረሳችሁ አደረሰን የሰላም አምላክ የፍቅር ጌታ የደስታ ሁሉ ባለቤት መጪውን ጊዜ ዘመነ ቅዱስ ማቴዎስ ጌታ እግዚአብሔር ለሀገራችን ኢትዮጵያና ለቤተክርስቲያናችን ሰላምና ፍቅር ሰጥቶን በጋራ ሀገራችን ኢትዮጵያንና ቅድስት ቤተክርስቲያናችንን የምናለማበትና የምናሳድግበት የተጣላን የምንታረቅበት ከድኅነት ከችግር ነፃ የምንወጣበት የበረከትና የይቅርታ ዓመት ያድርግልን። ውድ ኦርቶዶክሳውያን መላው የሀገራችን ሕዝብ ሆይ እግዚአብሔር አምላክ በደላችንን ይቅር እንዲለን ከክፋት፣ከተንኮል፣ከሀሜት፣ከዘረኝነት ጸድተን በንጽህናና በቅድስና ሆነን ዘወትር ሁሉን ማድረግ ወደሚችለው አምላክ እንጸልይ ጌታ እግዚአብሔር ተአምራትን ያደርጋል ዓመቱን የሰላም፣የፍቅር፣የይቅርታ፣የአንድነት ያድርግልን አሜን።

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ !

አባ በርተሎሜዎስ
የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
መስከረም ፩ቀን ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም
ድሬዳዋ ኢትዮጵያ