የጥምቀት በዓልን በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን

የ2015 ዓ/ም የከተራ እና የጥምቀት በዓልን በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን ለማክበር ዓርብ ምሽት የተጓዙት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ እና የኒውዮርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቆይታቸውን በመግታት ወደ አዲስ አበባ ገቡ።

በበረዶዋማ ፊንላንድ አገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የጥምቀት በዓልን በድምቀት አከበሩ።

የስዊድን፣ ስካንዲናቪያንና የግሪክ ሀገሮች ሀገረ ስብከት በፊንላንድ ሄልሲንኪ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን፣ ዛሬ ጥር 13 ቀን 2015 ዓ.ም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሰሱ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በርካታ ምእመናን በተገኘበት በድምቀት ተከሯል።

የጋምቤላ የጥምቀት በዓል አከባበር

የጋምቤላ የጥምቀት በዓል አከባበር ዛሬም ቀጥሏል እስከ ሰኞ ጥር 15 ይቀጥላል።

የ ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የጥምቀት በዓል በሰላም ተከብሮ መዋልን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የተሰጠ መግለጫ ፤

የ ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የጥምቀት በዓል በሰላም ተከብሮ መዋልን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የተሰጠ መግለጫ ፤
******

ጥር ፲፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
አዲስአበባ ኢትዮጵያ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በየ ዓመቱ ጥር፲ ና ፲፩ቀን የሚከበሩት የከተራና የጥምቀት በዓላት ዘንድሮም በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት ተከብረው ውለዋል።ይህ በቤተክርስቲያናችን የሰላም፣የስምምነት ፣የአንድነትና የመከባበር መገለጫ የሆነው በዓላችን ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ከበዓሉ ቀድሞ ዐቢይ ኮሚቴ በማቋቋም በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ቆይቷል።

የተቋቋመው ዐቢይ ኮሚቴም ንዑሳን ኮሚቴዎቻችን በማደራጀት በየተመደበበት ኮሚቴ ውጤታማ ሥራዎችን አከናውኗል።ይህም በመሆኑ በልዑል እግዚአብሔር ረድኤትና በረከት ስኬታማ በዓል ለማክበር ችለናል።

በተለይም የጠቅላይ ቤተክህነትና የመንግስት የጸጥታ አካላት ያደረጉት የተጣመረ እንቅስቃሴ ለበዓሉ ድምቀትና ማማር እንዲሁም ሰላማዊ በሆነ መልኩ መከበር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደነበረው ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን ትገነዘባለች።

ለዚህ ስኬታማ የበዓል አከባበር ቤተክርስቲያናችን ከበዓሉ ቀደም ብላ ከካህናት፣ከወጣት የቤተክርስቲያናችን ልጆችና ኦርቶዶክሳዊ ከሆኑ የሚዲያ ተቋማት ጋር ያደረገቻቸው ውጤታማ ውይይቶች በእርግጥም ተነጋግሮ፣ተመካክሮና ተናቦ መስራት ለውጤት የሚያበቃ መሆኑን ያረጋገጡ ናቸው።ይህ አይነቱ የመመካከር ፣የመወያየትና ተናቦ የመስራት ተግባርም ለወደፊቱ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል።

ሕዝበ ክርስቲያኑ በተለይም ደግሞ ወጣት ልጆቻችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በበዓል አከባበሩ ዙሪያ በተደጋጋሚ በሚዲያዎች ያስተላለፈቻቸውን መልዕክቶች በመቀበል በዓሉ የቤተክርስቲያያችንን ክብር በሚመጥን መልኩ ተከብሮ እንዲውል በማድረግ ረገድ ያሳያችሁት ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ጨዋነትን የተላበሰ የበዓል አከባበር ሥርዓት የሚደነቅና ተጠናክሮ መቀጠል የሚገባው ነው።
በዚህም ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን የተሰማትን ደስታ ትገልጻለች።

በማዕከል ደረጃ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖትት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሚኒስትሮች፣ክብርት ከንቲባ አዳነች አቤቤና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት በጃንሜዳ ባህረ ጥምቀት የተከበረው በዓልም እጅግ ባማረና በደመቀ መልኩ ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ የአዲስአበባ ከተማ አስተዳደርና ክብርት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ቅዱስነታቸው እና የክብር እንግዶች በዓሉን ያከበሩበትን ስቴጅና ሳውንድ ሲስተም ከነ ሙሉ ግበዓታቸው እንዲሁም ደረጃቸውን የጠበቁ ድንኳኖችን በማቅረብ ለበዓላችን ድምቀትና ማማር ትልቁን አስተዋጽኦ በማበርከት የሚያስመሰግን ተግባር ፈጽመዋል፤ለዚህም ቤተክርስቲያናችን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለች።

በአጠቃላይ በዓላችን በድምቀት ተከብሮ መዋል እንዲችል የደከማችሁ አካላት ሁሉ ልዑል እግዚአብሔር የድካማችሁን ዋጋ እንዲከፍላችሁ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን የዘወትር ጸሎቷ ነው።

በተለይም በዓሉ ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ ሌት ከቀን ስትደክሙ የሰነበታችሁ የጸጥታና ነደህንነት የጋራ ግብረ ሃይል አባላት ድካምና ልፋታችሁ ፍሬ አፍርቶ በዓሉ በሰላም ተከብሮ በመዋሉ ቅድስት ኦሮቶዶሳዊት ቤተክርስቲያናችን የተሰማትን ደስታ ከታላቅ መንፈሳዊ ምስጋና ጋር እየገለጸች እግዚአብሔር አምላክ ሥራችሁን ሁሉ እንዲባርክና የዘወትር ጥበቃው እንዳይለያችሁ አጥብቃ እንደምትጸልይላችሁ ትገልጻለች።

ከበዓሉ በፊት በዓሉን በተመለከተ የቤተክርስቲያናችንን መልዕክት በማስተላለፍ፣በበዓሉ ወቅትም የበዓል አከባበር ሥርዓቱን ለመላው ዓለም በቀጥታና በዜና ሥርጭት በመዘገብ ላይ ለሰነበታችሁ የሚዲያ ተቋማትና ጋዜጠኞችም ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ልባዊ ምስጋናዋን እያቀረበች ሥራችሁ ሁሉ የተሳካና ውጤታማ እንዲሆንላችሁ ልባዊ ምኞቷን ትገልጻለች።

በነገው እለት ወደየ አብያተክርስቲያናቱ የሚገቡት ታቦታትም ልክ እንደዛሬው የበዓል አከባበር ሥነሥርዓት ፍጹም ሰላማዊና ደማቅ በሆነ በመልኩ ይከብሩ ዘንድ ሕዝበ ክርስቲያኑ በተለይም ወጣት ልጆቻችን ታቦታቱ በሰላም ወደየ መንበረ ክብራቸው እንዲመለሱ ቤተክርቲያን ባስተማረቻችሁ የመተሳሰብ፣የመደጋገፍና የመከባበር ሥርዓት መሰረት የሚጠበቅባችሁን ሃይማኖታዊ ግዴታ እንድትወጡ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን መልእክቷን ታስተላልፋለች።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት

ጥር ፲፩ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
አዲስአበባ ኢትዮጵያ

ፎቶ ሪፖርታዥ፦ የ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የጥምቀት በዓል አከባበር

ፎቶ ሪፖርታዥ፦ የ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የከተራ በዓል አከባበር

የከተራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በተገኙበት በጃን ሜዳ በታላቅ ድምቀት ተከበረ

ጥር ፲ቀን ፳፻ ፲ወ፭ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“””””””””””””””””””””

የ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የከተራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በተገኙበት በጃንሜዳ ባህረ ጥምቀት በታላቅ ሥነሥርዓት ተከብሮ ውሏል።በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒዩወርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፣ክቡር ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን፣የጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች፣በተገኙበት ነው የተከበረው።

በጃን ሜዳ ባህረ ጥምቀት የባለተራው የደብር ደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ሊቃውንት መሪነት”ወረደ ወልድ እምሰማያት”በቁም ዜማ በዝማሜና በጸናጽል ከዘመሩ በኋላበፍስሐ ወበሰላም የሚለውን አመላለስ ለ፴ ደቂቃ ያህል አሸብሽበዋል።

በመቀጠልም የደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ፍቁረ እግዚእ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች “ወነዋ ተወልደ ወነዋ ተጠምቀ መድሃኔ ዓለም። ፍሥሐ ለከኲሉ ኲሉ ዘየአምን”የሚለውን ለ፲፭ ደቂቃ ወረብ አቅርበዋል ።

በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ታቦታቱ ወደ ተዘጋጀላቸው ድንኳን ገብተው የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

እነሆ በውኃ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ማን ነው?

ይህ ቃለ ሃይማኖት ከኢትዮጵያዊው ጃንደረባ አንደበት የተሰማ ድምፅ ነው (ግብ.ሐዋ. 8፥39)። ምሥራቅ አፍሪካዊቷ ሀገራችን ቅድስት ኢትዮጵያ በኖረችባቸው ብዙ ሺህ ዓመታት ሁሉ መሠረታዊ ታሪኳ ከአምልኮተ እግዚአብሔር ጋር የተሳሰረ ስለሆነ ሀገረ እግዚአብሔር በመባል ትታወቃለች።

በቀዳማዊ ምኒልክ አማካኝነት በንጉሡ በዳዊት ልጅ በሰሎሞን ዘመን ጽላተ ሙሴን ከነመስዋዕቱ፥ ሕገ ኦሪትን ከነሥርዐቱ ተቀብላ ሀገራችን ኢትዮጵያ አምልኮተ እግዚአብሔርን በዘመነ ብሉይ ስትፈጽም እንደነበር በቅዱስ መጽሐፍ ተመዝግቧል (1ነገ. 10፥9)። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ በዚህ ንስሓ በማይገባ ትውልድ ንግሥተ አዜብ ትፈርድበታለች፤ ከምድር ዳርቻ የሰሎሞንን ጥበብ ለማየት መጥታለች ብሎ ሀገራችንን ጠቅሷታል (ማቴ. 12፥40)።

ቀደምት ኢትዮጵያውያን አባቶቻችንም ጣዖት ያላመለኩ፥ በሕገ ኦሪት በአምልኮተ እግዚአብሔር የኖሩ ስለነበር ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም እየሄዱ ይሰግዱ፥ ሥርዐተ ኦሪትን፥ ሕገ ኦሪትን ይፈጸሙ ነበር። በዚያም መሠረት ነው «ወሖረ ኢየሩሳሌም ይስግድ ወእንዘ ይገብእ ነበረ ዲበ ሠረገላሁ ያነብብ መጽሐፍ ኢሳይያስ ነቢይ – የኢትዮጵያ ሰውም ሊሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር፤ ሲመለስም በሠረገላ ተቀምጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ያነብ ነበር። መንፈስ ቅዱስ ፊልጶስን ወደዚህ ሠረገላ ቅረብና ተገናኘው አለው» (ግብ.ሐዋ. 8፥28-32)።

ፊልጶስም መንፈስ ቅዱስ በነገረው መሠረት ወደ ሠረገላው ሲቀርብ ኢትዮጵያዊውን መጽሐፈ ኢሳይያስን ጸሪቀ ሐዲስ በመባል የሚታወቀውን ምዕራፍ ሃምሳ ሦስትን ሲያነብ አገኘው። ፊልጶስም በውኑ የምታነበውን ታስተውለዋለህን አለው። ያለ መምህር እንዴት እረዳዋለሁ፥ እባክህ ነቢዩ ስለምን እንደሚናገር አስረዳኝ አለው። ፊልጶስም ለጃንደረባው ኢትዮጵያዊ ወንጌል ሰበከለት።

በመላው ዓለም ወንጌልን እንዲሰብኩ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የታዘዙትን ሐዋርያት እኛን ኢትዮጵያውያንን ያገኙን ጣዖት እያመለክን አይደለም፤ ብሉይ ኪዳንን እያነበብን፥ እግዚአብሔርን እያመለክን እንጂ። በብሉይ ኪዳን በሕገ ኦሪት የለሰለሰ እርሻ ስለነበር ባለመቶ አድርጎ የወንጌልን ፍሬ ለማብቀል ጊዜ አልወሰደበትም። ከፊልጶስ ጠቅላላ ነገረ ክርስቶስን፥ ቅዱስ ወንጌልን ከሰማና ከተማረ በኋላ «ውኃ ይኸውና፥ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምንድን ነው» ብሏል።

ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስም «ከአመንክ ተፈቅዷል» አለው። ኢትዮጵያዊው ጃንደረባም «ወይቤ አነ አአምን ከመ ኢየሱስ ክርስቶስ ወልዱ ለእግዚአብሔር — ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ» አለ፤ ከዚያም በኋላ ሠረገላው እንዲቆም ሆነ። ወወረዱ ኅቡረ ኀበ ማይ ፊልጶስ ወውእቱ ኅጽው ወአጥመቆ እማይ ወእመንፈሰ እግዚአብሔር — ፊልጶስና ጃንደረባውም ወደ ውኃው ወረዱ፤ አጠመቀውም።

ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ የተናገረው የእምነት ቃል እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው እኔን ማን ይለኛል ብሎ በተናገረ ጊዜ፦ «ሌሎች ሙሴ ነህ፥ ኤልያስ ነህ፥ ዮሐንስ መጥምቅ ነህ፥ ወይም ከነቢያት አንዱ ነህ» ይሉሃል አሉ። ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ «አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ» ብሏል (ማቴ. 16፥16-20)። እንዲሁም ሐዋርያው ናትናኤል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከበለስ ሥር አየሁት ሲለው፥ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፥ ወልድ ነህ በማለት እምነቱን ገልጿል (የሐዋ.ሥራ 1፥48-53)። ሐዋርያው ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስም በወልድ የሚያምን የዘለዓለም ሕይወት አለው ብሏል።

ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ከፊልጶስ ቅዱስ ወንጌልን ተምሮ ሃይማኖቱን ሲገልጽ፦ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ ብሎ ሃይማኖቱን ተናግሮ፥ መስክሮ በሐዋርያው እጅ ተጠምቋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደመ ክርስቶስ፥ በትምህርተ ሐዋርያት የተመሠረተች ጥንታዊት፥ ሐዋርያዊት ናት የምትባለውም ስለዚህ ነው።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት «ሑሩ ወመሐሩ ኵሎ አሕዛበ ወእንዘ ታጠምቅዎሙ በሉ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ መሐርዎሙ ይዕቀቡ ኵሎ ዘአዘዝኩክሙ ወናሁ አነ እሄሎ ምስሌክሙ በኵሉ መዋዕለ እስከ ሕልፈተ ዓለም — እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ፥ ያዘዝኋችሁን ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችሁ ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ» (ማቴ. 18፥19-20) ሲል መሠረታዊውን የቤተ ክርስቲያን ተልዕኮና ሼል ለደቀ መዛሙርቱ ተናግሯል።

በዚህ በጌታችን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ ትእዛዝ መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምንጊዜም ሥራዋና ተልዕኮዋ ቅዱስ ወንጌልን ማስተማር፥ ማጥመቅ፥ ማቍረብ ነው። ቤተ ክርስቲያን ሰፋች፥ ጠነከረች፥ ታነጸች የሚባለው ብዙ ቍጥር ያላቸው ሰዎች እያመኑ ተጠምቀው የክርስቶስ ተከታዮች ሲሆኑ ነው።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይት በተነሣ በ40 ቀኑ ወደ ሰማይ ሲዐርግ እጆቹን በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ ዘርግቶ ባርኮ ሥልጣነ ክህነትን ለሐዋርያት ሰጥቷል (ሉቃ. 24፥50)። ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ያጠመቁት፥ ከጌታ በምድር የሠራችሁት በሰማይ የታሠረ ነው፤ በምድር የፈታችሁት በሰማይ የተፈታ ነው ተብሎ በተሰጣቸው ሥልጣነ ክህነት ነው። ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ከጌታ ያገኙትን ሥልጣነ ክህነት በአንብሮተ እድ አስተላልፈዋል (ግብ.ሐዋ. 6፥1-6)። ይህም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትመራበት ሥልጣነ ክህነት ከአበው ወደአበው ሲተላለፍ ይኖራል (1ጢሞ. 5፥22)።

እንግዲህ ከላይ በተገለጸው መሠረት የሥላሴን ልጅነት ከሚያስገኘው ከመርገመ ኀጢአት፥ ከዲያብሎስ ቁራኝነት የሚያላቅቀው የክርስትና ጥምቀት ሥልጣነ ክህነት ባለው ካህን መፈጸም አለበት። ጥምቀተ ክርስትና ለአማኙ የሚፈጸመው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ብቻ ነው። የተጠመቀ ሰው በዕለቱ መቍረብ አለበት። ስለ ጥምቀተ ክርስትና አፈጻጸም ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 3 ከቍ. 20-30 እንዲህ ይላል፦

«ጥምቀትሰ ሥርዕ ላዕለ ዕደው ወአንስት ገውሶሙ ወዐቢዮሙ በእንተ ዘይቤ እግዚአብሔር ሎቱ ስብሐት ዘኢተወልደ እማይ ወእመንፈስ ቅዱስ ኢይሬእያ ለመንግሥተ እግዚአብሔር — ጥምቀትስ ለወንዶችም ለሴቶችም፥ ለትልቁም ለትንሹም የታዘዘ፥ የተገባ ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን በወንጌል ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም ስለአለ» ይልና፤ አያይዞም ስለዚህ ይህ አንቀጽ አፈጻጸሙ ሲናገር «ኢያጥምቅ ዘእንበለ ኤጲስቆጶስ አው ቀሲስ ወዲያቆናት ይትልአኩ ምስሌሆሙ — ከኤጲስ ቆጶስ ወይም ከቄሱ በስተቀር ማንም አያጥምቅ፤ ዲያቆናት ግን ከእነርሱ ያገልግሉ፤ ይላላኩ።» «ወለእመቦ ብእሲ ዘተወክፈ ጥምቀተ እምአላውያን ኢኮነ ውእቱ ምእመነ — ከመናፍቃን ጥምቀትን የተቀበለ ሰው ቢኖር አማኝ የክርስቶስ ተከታይ አይደለም ይላል»፤ ይቀጥልና፦ ሴቶች ወንዶችን ክርስትና አያንሱ፤ ወንዶች ወንዶችን፥ ሴቶች ሴቶችን ያንሱ በማለት ያስረዳል።

ወንጌላዊው ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ከጌታ ጎን በፈሰሰው ማየ ገቦ አማኞች ተጠምቀው ልጅነት እንደሚያገኙ በሀብተ መንፈስ ቅዱስ እንደሚከብሩ ሲገልጽ፦

«አኮ በማይ ባሕቲቱ አላ በማይኒ ወለአምኒ ወበመንፈስ ውእቱ ዘስምዐ ይከውን ከመ መንፈሰ ጽድቅ፥ ሠለስቲሆሙ አሐዱ እሙንቱ — በውኃ ብቻ አይደለም የዕለት ጽንስ በመሆን በደማዊ አካል በመገለጽ የባሕርይ አምላክ እንደሆነ በሚመሰክር በመንፈስ ቅዱስም ነው እንጅ» (1ዮሐ. 5፥6-10)። ይህም ማለት ካህናት ዕለት ዕለት በስመ ሥላሴ በሚለውጡት ማየ ገቦ፥ በሚያሰጡት ሀብተ መንፈስ ነው። በደምኒ ማለት በደመ ላሕም፥ በደመ በግዕ ሳይሆን በራሱ ክቡር ደም በደመ ገቦ፥ በመንፈሰ ረድኤት ሳይሆን በመንፈሰ ልደት ነው።

ሠለስቲሆሙ አሐዱ ማለት ደግሞ ሦስቱ እንደ ሰው ይቀበልቸዋልና በአንድ ቄስ እጅ ሲሰጡ ይኖራሉ። አንድ ክብረ መንግሥተ ሰማያትን ያስገኛሉ፥ በማለት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ይተረጒማሉ።

ታላቁ ሐዋርያ መምህረ አሕዛብ ቅዱስ ጳውሎስ «ከመ ትኩን አሐደ ሥጋ ወአሐደ መንፈስ በከም ተጸዋዕክሙ ለአሐዱ ተስፋክሙ አሐዱ እግዚአብሔር ወአሐቲ ሃይማኖት ወአሐቲ ጥምቀት — በአንድ ተስፋ እንደተጠራችሁ እንደ አካልና እንደ መንፈስ አለ አንድ ጌታ፥ አንዲት ሃይማኖት፥ አንዲት ጥምቀት»  (ኤፌ. 4፥4-6)። በዚህ የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ አስተምህሮ መሠረት ጥምቀተ ክርስትና አንድ ጊዜ ብቻ ይፈጸማል እንጅ አይደገምም፤ ጥምቀት አንዲት ናትና። በአንዲት ጥምቀት እናምናለን ተብሎ የተጻፈውም ስለዚህ ነው። ሃይማኖትን መለወጥ ጥምቀትን ማርከስ ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር የሚለይ ክፉ በደልና ክሕደት ነው።

በእግዚአብሔር አምኖ በስሙ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ሥልጣነ ክህነት ባለው ካህን እጅ መጠመቅ የመንግሥተ ሰማያት በር መግቢያ ቁልፍ መያዝ፥ የዘለዓለም ሕይወት ማግኘት ነው። ስለዚህም ነበር ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ልጅነትን የምታሰጥ፥ የኀጢአት ሥርየት ብቻ የምትሆን ጥምቀት እያጠመቀ ፍጹም ለሆነ መርገመ ኀጢአት ለሚወገድበት፥ የሥላሴ ልጅነት ለሚገኝበት ጥምቀት ሲናገር፦ «ንስሐ ግቡ፤ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና» ብሎ ነበረ (ማቴ. 3፥4)። ይህም ማለት መንግሥተ ሰማያት በልጅነት በሃይማኖት ልትሰጥ ቀርባለችና እያለ ያስተማረውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትምህርቱ መጀመሪያ አድርጎታል። በዮሐንስ አድሮ የተናገረ እርሱ ስለሆነ ነው። (ማቴ. 4፥17)

ቅዱሳን ሐዋርያትም በበዓለ ጰራቅሊጦስ ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ከአስተማሩ በኋላ ትምህርታቸውን የተቀበሉ ሕዝብ ምን እናድርግ ሲሏቸው፦ ንስሐ ግቡ ኀጢአታችሁ ይሰረይ ዘንድ ልጅነትን እንድታገኙ ከኀጢአት መርገም እንድትላቀቁ በኢየሱስ ክርስቶስ ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ ትቀበላላችሁ፤ የተስፋው ቃል ለእናንተና ለልጅ ልጆቻችሁ ጌታ አምላካችን ወደ እርሱ ለሚጠራቸው በሩቅ ላሉት ሁሉ ነውና (ግብ. ሐዋ. 2፥37-40)።

የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን በመባል በሚታወቀው በበዓለ ጰራቅሊጦስ ቅዱሳን አበው ሐዋርያት በረድኤተ መንፈስ ቅዱስ ሲያስተምሩ በዚያች ቀን ብቻ ሦስት ሺህ ሰዎች አምነው ተጠምቀው ልጅነት ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለዋል።

ጥንታዊት ሐዋርያዊት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በትምህርተ ሐዋርያት የተመሠረተች በመሆኗ የምንጊዜም የዕለት ተዕለት ተልዕኮዋ ወንጌል ማስተማር በመዓርገ ክህነት ማጥመቅ፥ ማቍረብ ነው። ቅድስት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን አበው ሐዋርያት ትውፊትና ቀኖና፥ ሥርዐትና አስተምህሮ በመጠበቅ እስከ ሕልፈተ ዓለም ትኖራለች።

 

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሕረትና ይቅርታ በሁላችን ላይ ይሁን።

 

መጋቤ አእላፍ ኤፍሬም በየነ

የልሣነ ተዋሕዶ መጽሔት ዋና አዘጋጅ

 

አስተርአየ ዘኢያስተርኢ — የማይታየው ታየ

«አስተርአየ ዘኢያስተርኢ — የማይታየው ታየ»

(ድጓ ዘዘመነ አስተርእዮ)

መግቢያ

ዘኅቡእ እምኅቡኣን ወልዑል እምልዑላን ከተሠወሩት የተሠወረ፥ ከልዑላን በላይ ልዑለ ባሕርይ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር ዓለምን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ባሕርዩን በባሕርዩ ሠውሮ የኖረ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ። ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም ይህን ሲያስረዳ፦ «ወአስተርአየ በደኃሪ መዋዕል በእንቲኣነ — በኋለኛው ዘመን ስለእኛ ተገለጠ» በማለት። ቅድመ ዓለም ባሕርዩን በባሕርዩ ሠውሮ ይኖር የነበረ ስለእኛ (እኛን ለማዳን) የተገለጠ መሆኑን አስረድቷል። (1ጴጥ. 1፥20)

የማይታየው ፈጣሪ ዓለምን በመፍጠሩ ተገልጿል። ዓለምን ከፈጠረበት ጀምሮ በተለያየ ጊዜ በልዩ ልዩ ምሳሌ በፍጹም ሃይማኖት፥ በምስጋና፥ በጸሎት፥ በትሕትና፥ በንጽሕና፥ በቅድስና ሁነው ለሚሹትና ለሚፈልጉት ሁሉ በየጊዜው ተገልጿል።

በየጊዜው ሲገለጽም በራእይ፥ በሕልም፥ በአምሳል፥ በረድኤት በመሳሰለው ለወዳጆቹ የተገለጸላቸው ሲሆን፤ በኩነት የተገለጸው ግን በዘመነ ሥጋዌ ነው። ይህም በቅደም ተከተል እንደሚከተለው በዚህ ጽሑፍ በመጠኑ ተዳሷል። በመሆኑም፦

  1. ዘመነ አስተርእዮ ምን ማለት ነው?
  2. አስተርእዮ በጥንተ ፍጥረት
  3. አስተርእዮ በማኅበረ መላእክት
  4. አስተርእዮ በዘመነ አበው
  5. አስተርእዮ በዘመነ መሳፍንት
  6. አስተርእዮ በዘመነ ነገሥት
  7. አስተርእዮ በትንቢተ ነቢያት
  8. አስተርእዮ በዘመነ ሥጋዌ
  9. አስተርእዮ በባሕረ ዮርዳኖስ
  10. ማጠቃለያ፥ በሚሉ ንኡሳን አርእስት በቅደም ተከተል በአጭሩ ይቀርባል።

 

1) ዘመነ አስተርእዮ ምን ማለት ነው?

«ዘመነ አስተርእዮ» የሚለው ሐረግ ከሁለት የግእዝ ቃላት የተገኘ ሲሆን፤ «ዘመን» ማለት በቁሙ ዘመን፥ ዓመት፥ ሴኮንዶች ደቂቃዎችን፥ ደቂቃዎች  ሰዓታትን፤ ሰዓታት ዕለታትን፥ ዕለታት ሳምንታትን፥ ሰምንታት ወራትን፥ ወራት ዘመንን ያስገኛሉ። አንዱ ዘመን ዘመነ መፀው፥ ዘመነ ሐጋይ፥ ዘመነ ጸደይ ዘመነ ክረምት ተብሎ በ4ት ተከፍሏል። ከአንዱ ዘመን ውስጥም ዘመነ ጽጌ፥ ዘመነ አስተምህሮ፥ ዘመነ ስብከት፥ ዘመነ ልደት፥ ዘመነ አስተርእዮ፥ … ወዘተ. እየተባለ ተሰይሟል። ስለዚህ «ዘመን» የሚለውን ቃል የግእዝ መዝገበ ቃላት በቁሙ ዘመን፥ ዓመት፥ ጊዜ፥ ወራት በየስሙና በየክፍሉ ብሎ ተርጒሞታል። (መጽ.ሰዋ.ወግስ ገጽ 4)@3)

«አስተርእዮ» ማለት ደግሞ መታየት፥ መገለጥ ማለት ነው። ሁለቱ ቃላት ሲናበቡ «ዘመነ አስተርእዮ» የሚለውን ሐረግ ይሰጡናል፤ ዘመነ አስተርእዮ የሚለው ሐረግም ሲተረጐም የመታየት ዘመን፥ የመገለጥ ጊዜ … ተብሎ ይተረጐማል። በሌላ ቃልም «ኤጲፋንያ» ወይም በጽርዕ «ሄፒፋንያ» የሚለውን ቃል በተመሳሳይ ትርጓሜ አስተርእዮ መታየት፥ መገለጥ፥ ዕለተ ጥምቀት በማለት ይተረጒመዋል። (መጽ.ሰዋ.ወግስ ገጽ 2)%)

ቅዱሳን ሐዋርያትም በመጽሐፈ ዲድስቅልያ «ግበሩ በዓለ ኤጲፋንያ ዘውእቱ በዓለ ጥምቀት፥ ወይኩን በኀቤክሙ ክቡረ፥ እስመ ቦቱ ወጠነ እግዚእነ ከመ ያረኢ ስብሐተ መለኮቱ አመ ተጠምቀ በውስተ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ — የኤጲፋንያ (የአስተርእዮ) በዓልን አድርጉ፥ እርሱም በዓለ ጥምቀት ነው፤ በእናንተም ዘንድ የከበረ ይሁን። ጌታችን በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ በተጠመቀ ጊዜ የጌትነቱን ክብር ያሳይ ዘንድ ጀምሮበታልና» ሲሉ፥ የበዓሉን ታላቅነት ገልጸው ትእዛዝ አስተላልፈዋል። (ዲድስቅልያ አንቀጽ @9)

ስለዚህ ጌታ በዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ፥ አብ በደመና ላይ «የምወደው ልጄ ይህ ነው» ብሎ ሲመሰክርለት፥ መንፈስ ቅዱስም በራሱ ላይ በአምሳለ ርግብ ወርዶ ሲቀመጥ ምሥጢረ ሥላሴ የተገለጠበት ስለሆነ ዘመነ አስተርእዮ ተብሏል።

በመሆኑም ከዚህ አስቀድሞ ለወዳጆቹ በየጊዜው እንዴት ይገለጽላቸው እንደነበር በመጠኑ መግለጽ አስፈላጊ ይሆናል።

 

2) አስተርእዮ በጥንተ ፍጥረት

ዓለምን ከመፍጠሩ አስቀድሞ የማይታይ የማይመረመር የነበረው ጌታ ዓለምን በመፍጠሩ ፈጣሪነቱ፥ ህልውናው፥ አምላክነቱ፥ ጌትነቱና ክብሩ በፍጥረቱ ለፍጥረቱ ታውቋል። ይህንንም ብርሃና ለቤተ ክርስቲያን የተባለው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲመሰክር «ወዘኢያስተርኢ እግዚአብሔር እምፍጥረተ ዓለም ይትዐወቅ በፍጥረቱ በሐልዮ ወበአእምሮ ወከመዝ ይትአመር ኀይሉ ወመለኮቱ ዘለዓለም — ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ታይቶ የማይታወቅ እግዚአብሔር የፈጠረውን ፍጥረት በማሰብና በመመርመር ይታወቃል፤ ከሃሊነቱ፥ የዘለዓለም ጌትነቱም እንዲህ ይታወቃል» ብሏል። (ሮሜ 1፥@፤ መዝ. 08፥1)

ስለዚህ «ሥነ ፍጥረት» የመጀመሪያው የእግዚአብሔር መገለጥ መሆኑን በዚህ እንገነዘባለን።

 

3. አስተርእዮ በዓለመ መላእክት

የሥነ ፍጥረትን ምሥጢር አምልቶ አስፍቶ የጻፈው ኤጲፋንዮስ የተባለው የቤተ ክርስቲያን ሊቅ አክሲማሮስ በተባለው መጽሐፉ እንደገለጸው፥ ጌታ በመጀመሪያ ከፈጠራቸው ፍጥረታት ለባውያን ነባብያን ሁነው የተፈጠሩ ቅዱሳን መላእክት ናቸው። ጌታ እነርሱን ፈጥሮ ተሰውሯቸዋል።

ትጉሃን መላእክትም በአእምሮ በለብዎ ተፈጥረዋልና፥ ማን ፈጠረን? ከወዴትስ መጣን? እያሉ ሲመራመሩ፥ አቡሃ ለሐሰት የተባለው ሐሰተኛው መልአክ ድምፃቸውን ሰምቶ ወደላይ ቢያዳምጥ የሚሰማው ድምፅ ቢያንጋጥጥም የሚያየው ገጽ ስለአጣ እኔ ፈጠርኳችሁ … በማለት ለማሳሳት ሲሞክር መልአከ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል «አምላካችንን እስከምናገኘው ድረስ በያለንበት እንቁም (እንጽና)Âť ብሎ አጽንቷቸዋል። በዚህ ጊዜ አምላከ ብርሃን እውነተኛው የብርሃን ጌታ እግዚአብሔር በብርሃን ተገልጾላቸዋል። «ወውእቱ ብርሃነ ኮኖሙ ጥበበ ወአእምሮ እንዳለው ሊቁ … በዚህ ብርሃን አንድነቱን ሦስትነቱን ገልጾላቸው ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር … ብለው አመስግነውታል። (መቅ.ወን. አክሲማሮስ፥ ሥነ ፍጥረት)

 

4. አስተርእዮ በዘመነ አበው

ጌታ በዘመነ አበው በየዘመኑ ለአባቶቻችን በልዩ ልዩ ራእይ ተገልጿል። ይኸውም በገሃድ፥ በራእይ በሕልም በልዩ ልዩ አምሳል መገለጹን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ። ለማስረጃም፦

  • ለአባታችን ለአዳም በበደለ ጊዜ ለዘለፋ፥ ንስሓ በገባ ጊዜ ለውሂበ ተስፋ መገለጹ፥ (ዘፍ. 3፥9፤ መጽሐፈ ቀሌምንጦስ)
  • ለአቤል መሥዋዕት ባቀረበ ጊዜ መገለጹ (ዘፍ. 4፥4)፥ ለሄኖክ ወደ ደቂቀ ሴት በላከው ጊዜ መገለጹ፥ (ሄኖ. 4፥$9)
  • ለኖኅ ቅድመ ማየ አይኅ መርከብ እንዲሠራ ባዘዘው ጊዜ፥ ድኅረ ማየ አይኅ ኖኅ መሥዋዕት ባቀረበ ጊዜ መገለጹ፥ (ዘፍ. 6፥03፤ 7፥1፥ 8፥@1፥ 9፥1፥ @2፥04)
  • ለአብርሃም በተደጋጋሚ መገለጹ፤ ይልቁንም በአምሳለ እንግዳ በቤቱ (በድንኳን) ማረፉ፥ (ዘፍ. 02፥1፤ 7፤ 05፥1፤ 08፥#3)
  • ለይስሐቅ መገለጹ፥ (ዘፍ. @6፥@4፤ ለያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ መገለጹ በመጽሐፍ ቅዱስ የተመከረ ሐቅ ነው፥ (ዘፍ. @8፥02-05፤ #2፥#)

ቀደምት አበው እግዚአብሔር አምላክ በልዩ ልዩ ራእይ፥ ሕልም፥ አምሳል እየተገለጸላቸው ያለ ምንም መምህር እርሱን ሲያመልኩ ኑረዋል። ድምፁን ሰምተዋል፤ ቃል በቃልም ተነጋግረዋል።

 

5. አስተርእዮ በዝመነ መሳፍንት

ከዘመነ አበው ቀጥሎ ያለው ዘመነ መሳፍንት ይባላል። ጌታ ሕዝበ እስራኤልን ከግብጽ ምድር ሲወጡ ጀምሮ መንፈሳዊ ምግብናውን ለካህን፥ ሥጋዊ አስተዳደሩን ለመስፍን ሰጥቶ፥ ካህን ሲሞት ካህን፥ መስፍን ሲሞት መስፍን እየተካ ለብዙ ዘመናት መርቷቸዋል። በዚያ ዘመንም በተለያየ ራእይ በየዘመኑ እየተገለጸላቸው ሲመራቸውና ሕጉን፥ ትእዛዙን ሲገልጽላቸው ኑሯል። ለዚህ ማስረጃ በመጠኑ ለማሳየት ያህል፦

  • ለመጀመሪያው መስፍንና ሊቀ ነቢያት ሙሴ በተለያየ ጊዜ፥ በተለያየ ራእይ መገለጹ፥ (ዘፀ. 3፥1-07፤ 09፥@፤ #4፥@8)
  • ለኢያሱ፥ (ኢያ. 1፥1)
  • ለጌዴዎን፥ (መሳ. 6፥@3፤ 7፥2-0)
  • ለዮፍታሔ፥ (መሳ. 01፥@9)
  • ለሳሙኤል፥ (ሳሙ. 3፥4) … ለመሳሰሉት ሁሉ መገለጹን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ።

6. አስተርእዮ በዘመነ ነገሥት

ከዘመነ መሳፍንት ቀጥሎ ያለው ዘመን፥ ዘመነ ነገሥት ይባላል። በዚህ ዘመን፥ ንጉሠ ነገሥት፥ እግዚአ አጋእዝት፥ መኰንነ ኵሉ ፍጥረት የተባለው አምላካችን እግዚአብሔር በልዩ ልዩ መገለጥ ታይቷል። ይኸውም፦

  • ሥርወ መንግሥት ለተባለው ለንጉሥ ዳዊት መገለጡ፥ ይህ ልበ አምላክ የተባለው ነቢዩና ንጉሡ ዳዊት «ዘልፈ እሬእዮ ለእግዚአብሔር ቅድሜየ ውእቱ በኵሉ ጊዜ እስመ በየማን ውእቱ ከመ ኢይትሀወክ ለዓለም — ሁልጊዜ እግዚአብሔርን በፊቴ አየዋለሁ በቀኜ ነውና አልተውክም» በማለት እግዚአብሔር የተገለጠለት መሆኑን ገልጿል፥ (መዝ. 05፥8)
  • ለጥበበኛው ንጉሥ ለሰሎሞን መገለጹ፥ (ነገ.ቀዳ. 3፥5)
  • ለሌሎችም አበው ቀደምት ነገሥት በየጊዜው በገሃድ፥ በራእይ፥ በሕልም፥ በረድኤት፥ በተአምራት በመሳሰለው ሁሉ ተገልጧል።

7. አስተርእዮ በዘመነ ነቢያት

አስተርእዮ በዘመነ ነቢያት የሚለው ንኡስ ርእስ እጅግ ብዙ መጠነ ሰፊ ዳሰሳ የሚያስፈልገው ነው። ምክንያቱም ጌታ ለቅዱሳን ነቢያት በየዘመናቸውና በየጊዜያቸው በተለያየ ምሳሌ ያልተገለጸለት ነቢይ የለም። የጻፉትም እርሱ የገለጸላቸውንና ያናገራቸውን ነው። በዚህ ጽሑፍም በመጠኑ ለማሳየት ያህል፦

  • ልዑለ ቃል ለተባለው ነቢይ ለኢሳይያስ (ኢሳ. 6፥1-7)፥
  • ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ ለመረጠው ለነቢዩ ኤርምያስ፥ (ኤር. 1፥4-9)
  • ለነቢዩ ሕዝቅኤል በፈለገ ባሕር፥ (ሕዝ. 1፥1-@8) …
  • በባዕድ ሀገር ሁኖ አምልኮቱን አጽንቶ ለኖረው ዳንኤል፥ (ዳን. 7፥9)

በመሳሰለው ሁሉ በየጊዜው ለወዳጆቹ ተገልጿል።

ይህ ሁሉ አስተርእዮ የተስፋ፥ የረድኤት፥ የተአምራት፥ የትንቢት፥ የራእይ፥ የሕልምና የመሰለው አስተርእዮ ነው። ዋናውና አማናዊው አስተርእዮ የተስፋውና የትንቢቱ ፍጻሜ ሲደርስ በዘመነ ሥጋዌ የተደረገው አስተርአዮ ነው።

 

8. አማናዊ አስተርእዮ በዘመነ ሥጋዌ

«እግዚአብሔር እግዚእ አስተርአየ ለነ ግበሩ በዓለ በትፍሥሕት በኀበ እለ ያስተሐምምዎ … ጌታ እግዚአብሔር ተገለጸለን፥ በዓልን በደስታ አድርጉ …Âť  በማለት ነቢዩ ዳዊት እንደተናገረው፥ የእግዚአብሔር መገለጥ በብሉይ ኪዳን ምን እንደሚመስል፥ ማለትም በረድኤት፥ በተስፋ ድኂን፥ በምሳሌ፥ በትንቢት፥ በራእይ፥ በሕልም፥ በገሃድ … በመሳሰለው ሁሉ እንዴት እንደተገለጸ በመጠኑ አይተናል። (መዝ. )08፥@7)

ይህ ሁሉ በተስፋ ሲጠበቅ የነበረው ጊዜ ሲደርስ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ወደ ዓለም ላከ፤ ይህንም ብርሃና ለቤተ ክርስቲያን የተባለው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ይገልጸዋል፦ «ወአመ በጽሐ ዕድሜሁ ፈነወ እግዚአብሔር ወልዶ ወተወልደ እምብእሲት ወገብረ በሕገ ኦሪት — ቀጠሮው በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ላከ፥ ከሴትም ተወለደ፤ በኦሪት የታዘዘውንም ፈጸመ» (ገላ. 4፥4፤ ኤፌ. 1፥0)

ይህ በቀጠሮው ጊዜ የተፈጸመው ተስፋ አበው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ከሰማይ መላእክትን፥ ከምሥራቅ እጅ መንሻ የሚያቀርቡ ነገሥታትን፥ ከቅርቡ መንጋቸውን የሚጠብቁ ኖሎትን (እረኞችን) በአንድ አሰባስቦ በተአምራት በብርሃን ስቦ አንድ መዝሙር እንዲዘምሩ አደረገ። (ሉቃ. 2፥6)

በዚህ ጊዜ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት «ይገንዩ ቅድሜሁ ኢትዮጵያ፥ ነገሥተ ተርሴስ ወደሰያት አምኃ ያበውኡ ነገሥተ ሳባ ወዐረብ ጋዳ ያመጽኡ ወይሰግዱ ሎቱ ኵሎሙ ነገሥተ ምድር — በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ፤ ጠላቶቹም አፈር ይልሳሉ፥ የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የሳባና የዐረብ ነገሥታት እጅ መንሻ ያቀርባሉ፤ ነገሥታት ሁሉ ይሰግዱለታል» ሲል የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ (መዝ. &1፥9-01፤ ማቴ. 2፥1-02)። ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያውም የዚሁ አማናዊ አስተርእዮ በረከት ተካፋይ ሁናለች። ቀድሞ ንግሥተ ሳባ ለሰሎሞን ንጉሥ ገጸ በረከት እንደሰጠችው እውነተኛው ንጉሥ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜም የኢትዮጵያው ንጉሥ ባዜን እጅ መንሻውን ለጌታ ካቀረቡት ነገሥታት አንዱ እንደነበረ አበው ሊቃውንት በትርጓሜ ዳዊት ገልጸዋል። (መዝ. 71፥9-11)

 

9. አስተርእዮ በፈለገ ዮርዳኖስ

እንዲህም አድርጎ «በበሕቅ ልህቀ በ# ክረምት በዮርዳኖስ ተጠምቀ …Âť እንዲል በየጥቂቱ አደገ፤ # ዓመት ሲሞላው በፈለገ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ ተጠመቀ።

ኮከበ ሊቃውንት፥ ጥዑመ ልሳን ቅዱስ ያሬድ ይህን አስተርእዮ ሲሰብክ «ሐዳፌ ነፍስ ለጻድቃን ቀተስፋ ቅቡጻን ክርስቶስ አስተርአየ ውስተ ዓለም እምድንግል ተወልደ ክሡተ ኮነ እንዘ ይትኤዘዝ ለአዝማዲሁ ከዊኖ ሰብአ በዮርዳኖስ ተጠምቀ — ነፍሳትን የሚያሻግር፥ ተስፋ ለቆረጡት ተስፋቸው ክርስቶስ በዓለም ተገለጠ፤ ከድንግል ተወለደ፥ ለዘመዶቹ ሲታዘዘ ተገልጦ ታየ፥ ሰው ሁኖ በዮርዳኖስ ተጠመቀ» በማለት ይሰብከዋል። (ድጓ ዘዘመነ አስተርእዮ)

ስለዚህ በፈለገ ዮርዳኖስ ስለተፈጸመው አማናዊ አስተርእዮ ነቢዩ ዳዊት አስቀድሞ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት «ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኅሬሁ — ባሕርም አይታ ሸሸች፤ ዮርዳኖስም ወደኋላው ተመለሰ» በማለት ዘምሯል። (መዝ. )03፥3)

የባሕረ ዮርዳኖስ ትንቢታዊ ምሳሌና ምሥጢራዊ ትርጒም ከዚህ አስቀድሞ በወጣው የጥምቀት መጽሔት በሰፊው ስለተገለጸ ከዚህ ላይ አልፈዋለሁ።

 

ማጠቃለያ

ከላይ በርእሱ እንደተገለጸው ታላቁ የዜማ አባት ኢትዮጵያዊው የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ይህ የመገለጥ በዓል እንደሚከተለው ገልጾታል «አስተርአየ ዘኢያስተርኢ ኮነ እሙነ አስተርእዮቱ ለመድኀኒነ ክርስቶስ  — የማይታየው ታየ፤ የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መታየቱ እውነት ሆነ። በማለት ስለዚህ ታላቅ የመገለጥ በዓል ዘምሯል (ድጓ ዘአስተርእዮ)፤ ይህንም እንዲሁ ከልቡናው ብቻ አቅንቶ አልተናገረም፤ በቅዱሳት መጻሕፍት ሾለ እግዚአብሔር መገለጥ የተጻፈውን መሠረት አድርጎ እንጅ።

ስለዚህ የአስተርእዮ (የመገለጥ በዓል) ከላይ በመጠኑ እንደተገለጸው አስቀድሞ ትንቢት ተነግሯል፥ ምሳሌ ተመስሏል። ልበ አምላክ የተባለው ነቢዩ ዳዊትም ስለዚህ በዓል፦ «ርእዩከ ማየት እግዚኦ፥ ርእዩከ ማየት ወፈርሁ ደንገፁ ቀላያተ ማያት ወደምፃ ማያቲሆሙ — አቤቱ ውኃዎች አዩህ፥ ውኃዎችም አይተው   ሸሹ፤» ብሏል። ይህም በብሉይ በሙሴ ዘመን በባሕረ ኤርትራና በኢያሱ ዘመን በባሕረ ዮርዳኖስ የተፈጸመውን ድንቅ ተአምር የሚያስረዳ ሲሆን፤ በሐዲሱ ሲተረጐም ደግሞ ጌታ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ የተፈጸመውን ድንቅ ተአምር ያስረዳል። (መዝ. &6፥06)

ሐዋርያውም እግዚአብሔር  ለምን (ሾለ ምን) እንደተገለጸ ሲያስረዳ «ወበእንተ ዝንቱ አስተርአየ ወልደ እግዚአብሔር ከመ ይስዐር ግብሮ ለሰይጣን … ስለዚህ ነገር የሰይጣንን ሼል ይሽር ዘንድ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ» ብሏል። (1ዮሐ. 3፥8)

ከዚህ ከሐዋርያው ትምህርት እንደምንረዳው ይህ የአስተርእዮ (የመገለጥ) በዓል፦

 

  1. ይህ በዓል እግዚአብሔር ወልድ በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ በትሕትና ሲጠመቅ የታየበት የትሕትና በዓል ነው፥
  2. ይህ በዓል እግዚአብሔር አብ በደመና ሁኖ «የምወደው ልጄ ይህ ነው …Âť ብሎ ፍቅርን የሰበከበት የፍቅር በዓል ነው፥
  3. ይህ በዓል እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ በራሱ ላይ ወርዶ ሲቀመጥ የታየበት፥ በዚህ ዕለት በቅንነት ላገለገለ ሁሉ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በሰፊው የሚገኝበት፥ … በአጠቃላይ ምሥጢረ ሥላሴ በገሃድ የተገለጠበት የነገረ ድኅነት መሠረት፥ የመንግሥተ ሰማያት መግቢያ በር የሆነችው ምሥጢረ ጥምቀትን ጌታ በተግባር የፈጸመበት (ያስተማረበት) ዕለት ስለሆነ በዓሉ እጅግ ታላቅ በዓል ነው።

በዓለ አስተርእዮ የመገለጥ በዓል ስለሆነም ታቦተ ሕጉ ከቤተ እግዚአብሔር ወደ ጥምቀተ ባሕር ወርዶ፥ በካህናት በሊቃውንት፥ በመዘምራንና በምእመናን ታጅቦ ከባሕረ ጥምቀቱ ሲደርስ በተዘጋጀለት ድንኳን ያድራል።

ለበዓሉ የሚገባው አገልግሎት ሲፈጸም አድሮ ቅዳሴ ከተቀደሰ በኋላ ባሕረ ጥምቀቱ ይባረካል። ባሕረ ጥምቀቱ ተባርኮ ሕዝቡ ከተጠመቀ በኋላ ታቦተ ሕጉ በከፍተኛ ድምቀት በያሬዳዊ ዜማና በልዩ ልዩ አገልግሎት ታጅቦ ወደ መንበረ ክብሩ ይመለሳል።

በዚሁ በዘመነ አስተርእዮ ከሚከበሩ በዓላት መካከል የእመቤታችን የዕረፍቷ በዓል «አስተርእዮ» ይባላል።

 

በጥምቀቱ ውኃን ለጥምቀታችን የቀደሰልን አምላካችን ይክበር ይመስገን፤ አሜን።

 

መጋቤ ምሥጢር ፍሬ ስብሐት ዱባለ

የሊቃውንት ጉባኤ ም/ሰብሳቢ

ጥምቀት በተዋሕዶ

መግቢያ

“ወአገሐዶ ዮሐንስ ወአጥመቆ በውስተ ዮርዳኖስ ተመከረ በገዳም ወተዐውቀ ከመ እግዚአብሔር ውእቱ’ ‘ዮሐንስ ገለጠው ፤ በዮርዳኖስም አጠመቀው ፤ በገዳም ተፈተነ ፤ እርሱም የባህርይ አምላክ አንደ ሆነ ታወቀ” (ሃይ.ም.7ገጽ 30)

ጥምቀተ ክርስቶስ ለምንና እንዴት እንደ ሆነ ቅዱስ ሄሮኔዎስ “ዮሐንስ ገለጠው ፤ በዮርዳኖስም አጠመቀው….” በማለት “ጥምቀት” የመገለጥ በዓል እንደ ሆነና በሥጋ የተገለጠው ወልደ እግዚአብሔር ወልደ እጓለ እመሕያው ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን በመገለጡ ተዋናይና ምሥክር የሆነው ደግሞ መጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ነው። ጥምቀት በግእዙ ተጠምቀ ተጠመቀ ፤ ተዘፈቀ ፤ ብቅ ጥልቅ አለ ማለት ነው። በግርከኛና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎችም “አጲፋንያ” “ኤጲፋኒ” (epiphaneia/៥ ἐπιφάνεια/Epyphany) የሚለው ቃል መገለጥ ፤ መታየት ማለት ነው። ትንቢቱ ሲፈጸም ፤ ጊዜው ሲደርስ የተገለጠው ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ቅዱስ ዮሐንስ:- “ወአንሰ ኢያአምሮ ዳእሙ ከመ ያእምርዎ እስራኤል በእንተዝ መጻእኩ አነ ከመ አጥምቅ በማይ’ ‘እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ”(ዮሐ.1:31) ይላል። የጥምቀት ክብረ በዓልን ዐውድ ስንመለከት የአደባባይ በዓልና ከስሙ ትርጉም ጋር የሚዛመድ ነው። ጥምቀት ዘርፈ-ብዙ ምሥጢራት የሚተነተኑበት ኃይለ ቃል ሲሆን በዚህ ጽሑፍ የምንመለከተው ግን “ጥምቀት በተዋሕዶ” በሚል ርእስ በሥሉስ ቅዱስ የተገለጠውና ለአማንያን የተሰጠው “አንድነት”ን ብቻ የሚመለከት ይሆናል።

 

1. የሥላሴ አንድነትና ሦስትነት በጥምቀት

ሥላሴ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ የሦስትነት ስም ነው። በቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ አግዚአብሔር አምላክ ስነ ፍጥረትን መፍጠር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በአንድነትና በሦስትነት ሲጠራ አንደ ነበረ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት አስረግጠው ይናገራሉ። ለምሳሌ “እግዚአብሔርም አለ። ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር” (ዘፍ.1:26) ፤ “እግዚአብሔር አምላክም አለ። እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ” (ዘፍ.3:21) ሲል ከአንድ ቁጥር በላይ መሆኑን ሲያመለክት የሚከተሉት ጥቅሶች ደግሞ ሦስትነቱን ያረጋግጣሉ። “ዓይኑንም አነሣና እነሆ፥ ሦስት ሰዎች በፊቱ ቆመው አየ ፤ ባያቸውም ጊዜ ሊቀበላቸው ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ሮጠ፥ ወደ ምድርም ሰገደ፥ እንዲህም አለ። አቤቱ፥ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ሆነ ባሪያህን አትለፈኝ ብዬ እለምናለሁ ”(ዘፍ.18:1) የሚለውና “አንዱም ለአንዱ። ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤ ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች እያለ ይጮኽ ነበር” (ኢሳ. 6፡3) ተብሎ የተጻፈው ነው።

በባህረ ዮርዳኖስ የታየው ምሥጢረ ሥላሴ ግን ልዩ መገለጥ ነው፡፡ ይኽም ወልድ በተለየ አካሉ በእደ ዮሐንስ ሲጠመቅ ፤ አብ በደመና ሆኖ ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው›› ብሎ ሲናገር ፤ መንፈስ ቅዱስም በተለየ አካሉ በርግብ አምሳል በራሱ ላይ ሲቀመጥ መታየቱ ነው። “ወወረደ መንፈስ ቅዱስ ላዕሌሁ በሥጋ በርእየተ ርግብ…..መንፈስ ቅዱስም በአካል መልክ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ” (ሉቃ.3:22) እንደሚለው በተለየ አካል ፤ በተለየ ስም ፤ በተለየ ሥፍራ መገለጡ በጥምቀተ ክርስቶስ አንድነቱን በሦስትነት ፤ ሦስትነቱን በአንድነት የሚያሳይ ዕፁብ ድንቅ ምሥጢር ነው፡፡

ይኽ የሦስትነትና የአንድነት መገለጥ እስራኤል ዘሥጋ እንዲያውቁትና ከነርሱ ወገን ከሆነችው ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው ፤ በተዋሐደው ሥጋ መከራ መስቀልን ተቀብሎ የሰው ልጅን ከዲያብሎስ ግዞት ነጻ የሚያወጣው እርሱ እንደ ሆነ የአብን ምሥክርነት ሰምተው እንዲያምኑበት ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ለሊሁ ወረደ መንፈስ ቅዱስ ሠለስቲሆሙ እለ እሙንቱ እለ ይከውኑ ሰማእተ›› (ድጓ ዘጥምቀት) አንዲል፡፡

የሥላሴ ሦስትነትና አንድነት በምእመናን ሕይወት ጥልቅ ትርጉም አለው። ጥምቀተ ክርስቶስ እኛ ብዙዎች ስንሆን በእርሱ አንድ ሕዝብ መሆናችንን ፤ ልጅነት የምታሰጥና የአንድነታችን ምሥጢር የሆነችውን ጥምቀት በጥምቀቱ የመሠረተልን መሆኑን የምንማርበት ነው። “…ብዙዎች ስንሆን በክርስቶስ አንድ አካል ነን፥ እርስ በርሳችንም እያንዳንዳችን የሌላው ብልቶች ነን” (ሮሜ.12:5)። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ” (ዮሐ.17:23) በማለት በሥሉስ ቅዱስ ያለው አንድነት በክርስቲያኖችም ሕይወት የሚታይ መሆኑን አስተምሮናል።

 

2. የመለኮትና የትስብእት አንድነት በጥምቀት

በናዝሬት ተፀንሶ ፤ በቤተልሔም የተወለደውና በናዝሬት ያደገው የአብ ልጅ የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ፅንሰቱ በተአምር ፤ ልደቱና እድገቱ እንደ ማንኛውም የሰው ልጅ ሆኖ ለእናቱ ለቅድስት ድንግል ማርያምና ለጠባቂዋ ለጻድቁ ዮሴፍ እየታዘዘ ፤ በልጅነቱ ተአምራትን እያደረገ ማደጉን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሠክራሉ፡፡ ሠላሳ ዓመት ሲሆነው ለእስራኤል ይገለጥ ፤ ዘንድ ፤ የተቆጠረው ሱባኤና የተነገረው ትንቢትም እንዲፈጸም ራሱን ዝቅ አድርጎ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡ ‹አፍቂሮ ኪያነ መጽአ ኃቤነ ዘነቢያት ሰበኩ ለነ በዮርዳኖስ ተጠምቀ›› እንዲል። የክርስትና ሃይማኖት እውነተኝነትን ከሚያረጋግጡት መካከል ኢየሱስ ክርስቶስ ገና በማኅፀነ ማርያም ሳይፀነስ ከቅድስት ድንግል  በቤተልሔም አንደሚወለድና በዮርዳኖስ እንደሚጠመቅ አስቀድሞ በቅዱሳት መጻሕፍት መረጋገጡ ነው።

ስለዚህ ትንቢተ ነቢያት፤ የዘመናት ምኞትና የአበው ተስፋ ይፈጸም ዘንድ ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ተጠመቀ፡፡ የተጠመቀው ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ ሆኖ በተዋሕዶ ነው፡፡ የመለኮትና የትስብእት ተዋሕዶ ጥንተ ጠላት ዲያብሎስ ድል የተነሣበትና የሰው ልጅ የከበረበት ታላቅ ምሥጢር ነው፡፡ የክርስቶስ በፍጹም ተዋሕዶ መገለጥ የውሉደ ጥምቀትን አንድነት ፤ በኃጢአት ወድቆ በክርስቶስ ሞት የተነሣው ሰው በአግዚአብሔር ዘንድ ያለውን ሥፍራ ያሳየበት ነው። ቅዱስ ቄርሎስ “ወረደ ከመ ያዕርገነ ለነ ኀበ ሀገሩ አርያማዊ ኀበ ሀሎ አቡሁ’ ‘የባሕርይ አባቱ ካለበት ሰማያዊ ሀገሩ ያገባን ዘንድ እርሱ ወደ እኛ ወረደ” (ሃይ.አበው) እንዳለ የሰውን ልጅ ከወደቀበት ኃጢአት ለማንሳትና ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ እርሱ ወደ ምድር ወረደ። እኛን ሆኖ እኛን ለማዳን አካላዊ ቃል ሥጋን ገንዘብ አደረገ። ከቅድስተ ቅዱሳን ፤ ከንጽሕተ ንጹሐን ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን ፤ ከነፍስዋ ነፍስን ነስቶ በመወለዱ የሰው ልጅን አከበረ። “እንቲአሁ ለቃል ኮነ ለሥጋ ወእንቲአሁ ለሥጋ ኮነ ለቃል ፤ የቃል ገንዘብ ለሥጋ ሆነ የሥጋ ገንዘብ ለቃል ሆነ” ብሎ ቅዱስ ቄርሎስ እንደ ተናገረ። ቅዱስ ሉቃስም “…እንዘ ዘመዱ እንከ ንሕነ ለእግዚአብሔር…እንግዲህ የእግዚአብሔር ዘመዶች ከሆንን..” (የሐ.17:27-28) በማለት እግዚአብሔር አምላክ እኛን ከፈጠረበት ይልቅ እኛን ያዳነበት ምሥጢር እጅግ ታላቅ መሆኑን ያረጋግጥልናል።

 

3. የሕዝብና የአሕዛብ አንድነትበጥምቀት

በቅዱስ መጽሐፍ አስተምህሮ ሕዝብ የተባሉት እስራኤል ዘሥጋ ሲሆኑ እነዚህም ሱባኤን የቆጠሩ አበው ፤ ትንቢትን የተናገሩ ነቢያትና ሕዝበ እግዚአብሔርን የመሩ ነገሥታት ከመካከላቸው የተገኙ የአብርሐም ልጆች ናቸው። አሕዛብ የተባሉትም ከዚህ ታሪክ ውጭ ሆነው በአምልኮ ባዕድ ይኖሩ የነበሩት ናቸው። ሁለቱም በጥምቀት ዳግም ተወልደው የመንግሥተ ሰማያት ዜጎች ለመሆን በቅተዋል። “ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” (ዮሐ.3:3) ይላልና። በጥምቀተ ክርስቶስ የሁለቱም የዕዳ ዳብዳቤአቸው ተደምስሶላቸዋል። የሁለቱም የባርነት ታሪክ ተሽሮ በአዲስ ምዕራፍ በወልደ እግዚአብሔር በማመንና በአንዲት ጥምቀት በመጠመቅ የእግዚአብሔር ልጆች ሆነዋል። “ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው፤ ልዩነት የለምና” (ሮሜ.3:22) በማለት ከክርስትና በኋላ አንድነት እንጂ ልዩነት እንደሌለ አረጋግጦልናል።

በዘመነ አሪት ሕዝብና አሕዛብ የሚለዩበት ልዩ መታወቂያ “ግዝረት” ነበረ። “የቍልፈታችሁንም ሥጋ ትገረዛላችሁ፤ በእኔና በእናንተ መካከል ላለውም ቃል ኪዳን ምልክት ይሆናል” (ዘፍ.17:11)። በዘመነ ሐዲስ ግን ግዝረትን ተክቶ ለክርስቲያኖች መለያ ፤ ለመንግሥተ ሰማያት መግቢያ መሥፈርትና የመዳን ምልክት የሆነው “ጥምቀት” ነው። “ያመነ የተጠመቀም ይድናል” (ማር.16:16) እንዲል። ጥምቀት እንደ ግዝረት የአብርሐም ዘሮችን ብቻ ከአሕዛብ የሚለይ ድምበርና በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል የቆመ የቃል ኪዳን ምልክት ሳይሆን ሕዝብና አሕዛብን አንድ መንጋ አድርጎ ለእግዚአብሔር መንግሥት የመግቢያ ብቃት ሆኖ የሚያገለግል ነው። ይኽ በጥምቀተ ክርስቶስ ያገኘነው ጥምቀተ ክርስትና ከአለም መለያችን ብቻ ሳይሆን የአንድነታችን ማሳያ “አረቦን” ነው። “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና” (ገላ.3:27) ይላል።

የእግዚአብሔር ቃል የሚያረጋግጥልን ክርስቲያን ከየትኛውም ብሔር ፤ ነገድ ፤ ቋንቋ ፤ ልማድና ሥርዓት ይምጣ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቆ የመንግሥቱ ዜጋ ከሆነ በኋላ ባለቤት እንጂ ባዕድ አይደለም። የበላይነትም ሆነ የበታችነት ሥሜት አይኖረውም። አንዱን ዝቅ ሌላውን ከፍ አድርጎ የሚያይበት አለማዊ ዓይንም የለውም። ይልቁንም ለክርስቶስ አካሉ ለሆነችው ቤተ ክርስቲያን አንድ ክፍል ሆኖ የተገነባ ስለ ሆነ በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካሉት ሁሉ ጋር አንድ ነው። ስለዚህ በክርስቲያኖች መካከል ሊኖር የሚገባው አንድነትና የማይፈታ ምሥጢራዊ ትስስር በጥምቀት ዳግም ተወልደን የእግዚአብሔር ልጆች በመሆናችን ያገኘነው አምላካዊ ስጦታ እንጂ በጥቅምና በጊዜ የተገደበ ፤ በጥላቻና በፖለቲካ የሚዘወር ሕይወት አይደለም።

 

4. በክርስቶስ ሞት አንድነት በጥምቀት

ብርሃነ አሕዛብ ቅዱስ ጳውሎስ ስለ እኛ እኛን ሆኖ የእኛን ኃጢአት በእንጨት ላይ ተሸክሞ የእኛን ሞት ከሞተው ከክርስቶስ ሞት ጋር እንደምንተባበርና ስለ እኛ የሆነውን መከራ-መስቀል የእኛ የምናደርግበትን ምሥጢር እንዲህ ሲል ይናገራል። “ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን” (ሮሜ.6:4)። ሐዋርያው በዚህ ቃል የክርስቶስን ቤዛነት ለማሳየት “ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ” (1.ጢሞ.2:6) በማለት ጥምቀትና ሞትን በምሳሌነት ተጠቅሟል። በሞትና በጥምቀት ምሳሌም ክርስቲያኖች ስለሚያገኙት ድኅነትና ሰማያዊ በረከት አስተምሮናል። ይኽን እጅግ ጠቃሚና አስገራሚ ምሳሌ በጥቂቱ ዘርዘር አድርገን እንመልከት:-

4.1  የሞቱ ምሳሌ በጥምቀት

ጥምቀት ለክርስቶስ ሞትና መቃብር ምሳሌ ሆኖ መቅረቡ ሰው ሲጠመቅ ራቱቱን ሆኖ መጠመቁና ሲሞትም ራቁቱን ሆኖ መገነዙ ነው። ሰው ያለውን ሁሉ ትቶ ራቁቱን ወደዚህ ዓለም እንደ መጣ እንዲሁ ራቁቱን ወደ አለመኖር ይመለሳል። ከእግዚአብሔር ጸጋና ክብር የተራቆተውን የሰው ልጅ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ክርስቶስ ዕርቃኑን በመስቀል ላይ ዋለ። ወደ እርሱ  ክብር ሊያገባን በእኛ ሥፍራ እኛን ተክቶ እርሱ ተገኘ። “ዘዚአነ ሞተ ነሥአ ወእንቲአሁ ሕይወተ ወሀበነ” (ውዳሴ ማርያም ዘዓርብ) እንዳለ የእኛን ሞት እርሱ ሞቶ የእርሱን ዘለዓለማዊ ሕይወት ሰጠን። ይኽን ዘለዓለማዊ ሕይወት ለማግኘት የሰው ልጅ ሁሉ ክርስቶስን በማመን ፤  አምኖ በመጠመቅ የክርስቶስን ሞት የራሱ ማድረግ ነው። “ከሞቱ ጋር መተባበር” የሚለውም ክርስቶስ የከፈለለትን መከራ-መስቀል አምኖ መቀበልና በክርስቶስ ያለውን ሕይወት ወርሶ መኖር ማለት ነው። “ያን መንፈስም፥ በጸጋው ጸድቀን በዘላለም ሕይወት ተስፋ ወራሾች እንድንሆን፥ በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ አትርፎ አፈሰሰው” (ቲቶ.3:6)

4.2 የአዲስ ሕይወት ምዕራፍ በጥምቀት

ከሞት በኋላ ሌላ አዲስ ሕይወት አዲስ ዓለም አንዳለ ሁሉ ከጥምቀት በኋላ ሌላ አዲስ ሕይወት ፤ አዲስ ምዕራፍ ነው። ሐዋርያው ይኽን ሲያረጋግጥልን “እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን” ይላል። መጠመቅ ዳግም መወለድ የሆነውም ለዚህ ነው። “ወለደነ ዳግመ እማይ ወእመንፈስ ቅዱስ” እንዲል። ሰው አምኖ ሲጠመቅ አሮጌው ማንነቱን ትቶ ወደ አዲስ ማንነት ስለሚመጣ አዲስ ሕይወት ነው። ጥምቀት ኃጢአትን ስለምታስተሠርይ ኃጢአተኛው ከኃጢአት እሥራት ተፈቶ አሁን እንደ ተወለደ ሕጻን አዲስ ምዕራፍ የሚጀምርበት ነው። በመሆኑም ጥምቀት አዲስ ሕይወት ፤ የለውጥ ምዕራፍ ስለ ሆነ ስንጠመቅ አዲስ ስም ፤ አዲስ ዜግነት ይሰጠናል።

4.3 የማኅበረ ምእመናን አንድነት በጥምቀት

ጥምቀት ለአንድ ምእመን በእግዚአብሔር መንግሥት ፤ በክርስትና ሕይወት የመኖር ዋስትናና ሁለንተናዊ መገለጫው ነው። የክርስቶስን ሞት የራሱ ለማድረግና በክርስቶስ ሞት ምክንያትም በአዲስ ሕይወት ለመመላለስ በክርስቶስ አምኖ መጠመቅ የግድ በማስፈለጉ “ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል” (ዮሐ.3:7) ብሎ አስተምሮናል። ጥምቀት አንድን ምእመን በክርስቶስ ሞት በመተባበር ለአዲስ ሕይወት የምታበቃ ፤ የእግዚአብሔር መንግሥት የመግቢያ በር ቁልፍ ስትሆን በሌላ መልኩ የማኅበረ ምእመናንም የአባልነት/የአድነት መታወቂያ ፓስፖርት ናት። ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካሉ ፤ ክርስቶስም የቤተ ክርስቲያን ራስዋ ሲሆን እያንዳንዱ ምእመን የክርስቶስ አካል በሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገነባ አንዱ ክፍል ነው። ስለሆነም የተጠመቁት ሁሉ ከአንዱ መንፈስ ቅዱስ የተወለዱ በመሆናቸው የክርስቶስ ማኅበር ናቸው። “ማኅበራኒሁ ለክርስቶስ” እንዲል። ቅዱስ ዮሐንስ ስለዚህ ኅብረት ሲናገር “እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው” (ዮሐ.1:3) ይላል።

በዘመናችን ክርስቲያን ክርስቲያን ወንድሙን ሲያሳድድ ፤ የእርሱ ባልሆነው የአረማውያን ጠባይ ወገኑን አፈናቃይና ገዳይ ሆኖ መታየቱ እጅግ የሚያሳዝን ነው። በውኑ በዚህ ድርጊት የተሠማሩት ወገኖች በሃይማኖቱ ስም የሚጠሩ ወይስ በሃይማኖቱ የሚኖሩ? የሚለውን ጥያቄ ማንሳት ግድ ይሆናል። በሃይማኖት ስም መጠራትና ሃይማኖትን መኖር የተለያዩ ናቸውና። ሐዋርያው “በሃይማኖት ብትኖሩ ራሳችሁን መርምሩ” ይላል። የክርስትና ሃይማኖት የፍቅር ሃይማኖት እንጂ የመገፋፋት ፤ የመጠላላት ሃይማኖት አይደለም። የክርስትና ሃይማኖት መሠረቱ ክርስቶስ ፍቅር ስለሆነ የምንወደድበት ማንነት ሳይኖረን እርሱ እኛን ወዶ ወደ እኛ መጣ። ‹‹አፍቂሮ ኪያነ መጽአ ኃቤነ ዘነቢያት ሰበኩ ለነ በዮርዳኖስ ተጠምቀ›› ይላልና። በሃይማኖት የሚኖሩት ክርስቲያኖችም መታወቂያቸው ፍቅር እንደ ሆነ እርሱ ባለቤቱ አስተምሮናል። “እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፥ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ” (ዮሐ.13:35)።

 

2. ማንነትና እኩልነት በጥምቀት

ከጥምቀት ትሩፋት አንዱ ጥምቀት የማንነትና የእኩልነት ማረጋገጫ ማኅተም ሆኖ መሰጠቱ ነው። “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና። አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና”(ገላ.3:27-28) ይለናል። ውሉደ ጥምቀት በክርስቶስ የክርስትናን ማንነት የለበሱ የቀድሞ የዝቅታና የከፍታ ማንነታቸውን አስወግደው በእኩልነት የሚያምኑና በእኩልነት የሚያመልኩ ናቸው። አንዱ ሌላውን ባርያ ፤ ጨዋ ብሎ አያገለውም። ሁለቱም በክርስቶስ አካል ውስጥ ሥፍራ ተሰጥቶአቸው በክርስቶስ ክቡር ደም የከበሩ ስለሆኑ በእነርሱ ዘንድ የክብር ፤ የማንነት ጥያቄ አይነሳም። በክርስቶስ አካል ውስጥ ሆኖ የበታችነት ወይም የባዕድነት ሥሜት የሚሰማው ምእመንም እንዳይኖር ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ ይላል:- “እንግዲያስ ከእንግዲህ ወዲህ ከቅዱሳን ጋር ባላገሮችና የእግዚአብሔር ቤተ ሰዎች ናችሁ እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም” (ኤፌ.2:19)።

ይኽን የከበረና የታወቀ የክርስትና አስተምህሮን ገንዘብ ካደረግንና በሃይማኖት የምንኖረው ከሆነ ጥላቻን ፤ ግፍን ፤ መለያየትን ከመሐላችን ልናርቅ ይገባል። በክርስትና ሕይወት “አንድነት” ሲባል አንዱን በአንዱ መጨፍለቅና መዋጥ ሳይሆን “አንድነት” ማለት የእኩልነት መብት ፤ የማንነት ክብር የሚረጋገጥበት የጋራ ዋስትና የሆነ ሰንደቅ ዓላማ ነው። ይኽን “አንድነት” የነገድ ፤ የቋንቋ ፤ የጾታ ልዩነት አይገድበውም። የተጠራነው ከተለያየ ነገድና ቋንቋ ሲሆን ማንም በማንነቱ የተለየ ብልጫ ሳይኖረው በክብር ፤ በእኩልነት የሚታይበት ማኅበረ ክርስቶስ ነው። “…..ከነገድ ሁሉ ከቋንቋም ሁሉ ከወገንም ሁሉ ከሕዝብም ሁሉ ሰዎችን ዋጅተህ ለአምላካችን መንግሥትና ካህናት ይሆኑ ዘንድ አደረግሃቸው..” (ራዕ.5:10) ይላልና። ክርስቲያኖች ቋንቋንና ነገድን መሠረት ባደረገ ፖለቲካ መጠፋፋት ማለት የተዋጀንበትን የክርስቶስን ክቡር ደም ከንቱ ማድረግ ማለት ነው። አኮ በወርቅ ኃላፊ ዘተሳየጠነ አላ በደሙ ክቡር ቤዘወነ ወለደነ በጥምቀቱ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ የገዛን አይደለም፥ በከበረው ደሙ አዳነን እንጂ ቅድስት ለሆነች ቤተ ክርስቲያንም አካል እንሆን ዘንድ በጥምቀቱ ወለደን እንዳለ (ቅዱስ ያሬድ፤ 1.ጴጥ.1:18)።

 

ማጠቃለያ

“ጥምቀት በተዋሕዶ” በሚል ርእስ በመጠኑ ያየነው በጥምቀተ ክርስቶስ የተገለጠውን የሥሉስ ቅዱስ ሦስትነትና አንድነት ፤ የትስብእትና የመለኮት በተዋሕዶ መገለጥ ፤ የሕዝብና የአሕዛብ አንድነት እንዲሁም ጥምቀት የክርስቶስን ሞት መሞትና በአዲስ ሕይወት መመላለስ ፤ የማንነትና የእኩልነት መብት ማረጋገጫ ማኅተም መሆኑን ነው። ጥምቀተ ክርስቶስ ወደ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት ለምታስገባን ጥምቀተ ክርስቲያን መሠረት መሆኑንም በጥቂቱ ለመገንዘብ ሞክረናል። በአንዲት ሃይማኖት ፤ በአንዲት ጥምቀት አንድ እንሆን ዘንድ ስለ እኛ የተጠመቀው አምላክ በአንድነት ለአንድነት ጠርቶናል።

በእውነት ጸድቀን ፤ በሃይማኖትና በምግባር አብበን የጽድቅን ፍሬ እንድናፈራ ዐፀደ ወይኑ በሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተክሎናል ፤ የሕይወት ውኃ የሆነውን ቅዱስ ቃሉን እያጠጣን በዓለሙ የክፋትና የፈተና ሐሩር እንዳንጠወልግ ለዘለዓለማዊ መንግሥቱ ይጠብቀናል። ‹‹እግዚእ ክርስቶስ ለሊሁ ዘተከለነ ወሰቀየነ  በማይ መንፈሳዊ ማእከለ ተኩላት›› (ቅዱስ ዮሐንስ ፈወርቅ) እንዲል። ስለሆነም ራሳችንን ከዚህ ዓመጻና ሸንገላ ከሞላበት ዓለም ፤ መጠፋፋትን ጥበቡ ካደረገው ከዚህ ክፉ ትውልድ ለመዳን ፤ ዓለሙንም  ለማዳን እንድንችል ወልደ አብ ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ ይርዳን!