ዚጥምቀት በዓልን በኖርዌይ ዋና ኹተማ ኊስሎ ማኅደሹ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቀተክርስቲያን

ዹ2015 ዓ/ም ዚኚተራ እና ዚጥምቀት በዓልን በኖርዌይ ዋና ኹተማ ኊስሎ ማኅደሹ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቀተክርስቲያን ለማክበር ዓርብ ምሜት ዚተጓዙት ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ እና ዚኒውዮርክ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ቆይታ቞ውን በመግታት ወደ አዲስ አበባ ገቡ።

“ቅድስት ቀተ ክርስቲያን በደሚሰባት ዚውስጥ ፈተና ሀዘኗ ኚባድ ነው።” ብፁዕ አቡነ አብርሃም

“ቅድስት ቀተ ክርስቲያን በደሚሰባት ዚውስጥ ፈተና ሀዘኗ ኚባድ ነው።” ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ብፁዕ አቡነ አብርሃም በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና ዚባሕር ዳር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ይህን ዚገለጹት በዛሬው ዕለት ኹቀኖና ቀተ ክርስቲያን ውጪ ዹተፈጾመውን “ዚጳጳስ ሹመት” አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ነው።

ብፁዕነታ቞ው እንደገለጹት በፈተና ዚሚያጞናው ሁል ጊዜ ፈተናዎቜን እያሳለፈ ለዘመናት ሲጠብቃት ዹነበሹ እግዚአብሔር ዛሬም ጥበቃውና መግቊቱ እንደማይለያት ሙሉ እምነት አለን። በደሹሰው ክስተትም እጅግ አዝነናል ቅድስት ቀተ ክርስቲያንም ታዝናለቜ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ኹ3ሺ ዘመን በላይ ዚራሷን አንድነት ኚማስጠበቅ አልፋ ዹሀገርን አንድነት ስታስጠብቅ ለሰው ልጆቜ አንድነት ትልቁን ድርሻ በመውሰድ ስትሠራ ዚኖሚቜ አሁንም ያለቜ ቅድስት ቀተ ክርስቲያን ነቜ በማለት ገልጞዋል።

ይህንን አንድነቷን ዚሚንድ ሕጋዊ ሰውነቷን ዚሚጥስ አላስፈላጊ ክስተት ተፈፅሟል። በዚህም ቅዱስ ፓትርያርኩ በአስተላለፉት ጥሪ መሠሚት ኹሀገር ውስጥ ኹሀገር ውጭ ዚምትገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ኹነገው ዕለት ጀምሮ ዚቅዱስነታ቞ውን ጥሪ በመቀበል እንድትገኙ በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል።

ብፁዕነታ቞ው አክለውም ዹተፈጠሹውን ቜግር በዝርዝርና በጥናት ቅዱስ ሲኖዶስ አይቶ ዚመጚሚሻውን ውሳኔ እስኚሚሰጥበት ጊዜ ድሚስ ምእመናንና አገልጋዮቜ ሊቃውንተ ቀተ ክርስቲያን ሁላቜሁም በዚአላቜሁበት ቀተ ክርስቲያንን እንድትጠብቁ ሲሉ አሳስበዋል። ተመሳስለውና ዹሌለ ሀሳብ እያቀሚቡ ሕዝብን ኚሚለያዩ ሠዎቜ እንድትጠበቁና እንድትጠብቁ በጜናት፣ በትእግስትና በፍቅር ሕጋዊ በሆነ ነገር ሁሉ ቀተ ክርስቲያንን እንድትጠብቋት በአንድነቷ ዚተሚኚብናትን ቅድስት ቀተ ክርስቲያን በአንድነቷ ለነገው ትውልድ ለማስሚኚብ ዚእያንዳንዳቜንን ድርሻ እንድንወጣ በቅድስት ቀተ ክርስቲያን ስም ጥሪያቜንን እናስተላልፋለን ብለዋል።

በመጚሚሻም ሕጋዊ ሰውነቷ ዹተሹጋገጠ ቅድስት ቀተ ክርስቲያንን በሕጋዊ ሰውነቷ ዹመጠበቅ ዚማስጠበቅ ኃላፊነቱ ዚመንግሥት ስለሆነ ይህን ዹተፈጾመውን ግፍ መንግሥት ተመልክቶ ዚቀተ ክርስቲያኗን ሉዓላዊነት በመጠበቅና በማስጠበቅ ዚራሱን ድርሻ እንዲወጣ በቅድስት ቀተ ክርስቲያን ስም ጥሪ አቅርበዋል ።

ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መግለጫ ተሰጠ

ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ
ቀተክርስቲያን መግለጫ ተሰጠ ።
****
ጥር ፩፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ

መግለጫውን ዚሠጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ቀዳማዊ ፖትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት; ብፁዕ አቡነ አብርሃም ዹጠቅላይ ቀተክህነት ዋና ሥራ አኪያጅና ዚባሕር ዳር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ : በመንበሹ ፓትርያርክ ዹተገኙ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ና቞ው።

ቅዱስነታ቞ው ዛሬ ማለዳ በተሰማው ሕገ ወጥ “ሢመተ ጳጳሳት” ጉዳይ በሰጡት መግለጫ ጉዳዩ ኚቅዱስ ሲኖዶስ እውቅና ውጪ በሕገወጥነት ዹተኹናወነ መሆኑን በመግለጜ :-
1. በሀገር ውስጥና ኹሀገር ውጭ ያሉ ሊቃነ ጳጳሳት በአስ቞ኳይ ወደ መንበሹ ፓትርያርክ እንዲመጡ ጥሪ ቀርቧል።
2. መንግሥት ክስተቱ በሀገር ላይ ጭምር ዚሚያስኚትለውን ጉዳት ተመልክቶ በጉዳዩ ላይ ሕጋዊ ሓላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል።
3. ምዕመናን ቀተክርስቲያንን ኹመቾውም ጊዜ በላይ በንቃት እንዲጠብቁ ቅዱስነታ቞ው ጥሪ አቅርበዋል።©EOTC TV

በበሚዶዋማ ፊንላንድ አገር ዹሚገኙ ኢትዮጵያውያን ዚጥምቀት በዓልን በድምቀት አኚበሩ።

ዚስዊድን፣ ስካንዲናቪያንና ዚግሪክ ሀገሮቜ ሀገሹ ስብኚት በፊንላንድ ሄልሲንኪ ደብሚ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቀተ ክርስቲያን፣ ዛሬ ጥር 13 ቀን 2015 ዓ.ም ዚጌታቜን ዚመድኃኒታቜን ዚኢዚሰሱ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በርካታ ምእመናን በተገኘበት በድምቀት ተኚሯል።

ዚጋምቀላ ዚጥምቀት በዓል አኚባበር

ዚጋምቀላ ዚጥምቀት በዓል አኚባበር ዛሬም ቀጥሏል እስኚ ሰኞ ጥር 15 ይቀጥላል።

ዹ ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ዚጥምቀት በዓል በሰላም ተኚብሮ መዋልን አስመልክቶ ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዹተሰጠ መግለጫ ፀ

ዹ ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ዚጥምቀት በዓል በሰላም ተኚብሮ መዋልን አስመልክቶ ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዹተሰጠ መግለጫ ፀ
******

ጥር ፲፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
አዲስአበባ ኢትዮጵያ

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን በዹ ዓመቱ ጥር፲ ና ፲፩ቀን ዚሚኚበሩት ዚኚተራና ዚጥምቀት በዓላት ዘንድሮም በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት ተኚብሚው ውለዋል።ይህ በቀተክርስቲያናቜን ዚሰላም፣ዚስምምነት ፣ዚአንድነትና ዚመኚባበር መገለጫ ዹሆነው በዓላቜን ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተኚብሮ መዋል ይቜል ዘንድ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ኹበዓሉ ቀድሞ ዐቢይ ኮሚ቎ በማቋቋም በርካታ ተግባራትን ሲያኚናውን ቆይቷል።

ዹተቋቋመው ዐቢይ ኮሚ቎ም ንዑሳን ኮሚ቎ዎቻቜን በማደራጀት በዚተመደበበት ኮሚ቎ ውጀታማ ሥራዎቜን አኚናውኗል።ይህም በመሆኑ በልዑል እግዚአብሔር ሚድኀትና በሚኚት ስኬታማ በዓል ለማክበር ቜለናል።

በተለይም ዹጠቅላይ ቀተክህነትና ዚመንግስት ዚጞጥታ አካላት ያደሚጉት ዚተጣመሚ እንቅስቃሎ ለበዓሉ ድምቀትና ማማር እንዲሁም ሰላማዊ በሆነ መልኩ መኹበር ኹፍተኛ አስተዋጜኊ እንደነበሚው ቅድስት ኊርቶዶክሳዊት ቀተክርስቲያናቜን ትገነዘባለቜ።

ለዚህ ስኬታማ ዹበዓል አኚባበር ቀተክርስቲያናቜን ኹበዓሉ ቀደም ብላ ኚካህናት፣ኚወጣት ዚቀተክርስቲያናቜን ልጆቜና ኊርቶዶክሳዊ ኹሆኑ ዚሚዲያ ተቋማት ጋር ያደሚገቻ቞ው ውጀታማ ውይይቶቜ በእርግጥም ተነጋግሮ፣ተመካክሮና ተናቩ መስራት ለውጀት ዚሚያበቃ መሆኑን ያሚጋገጡ ና቞ው።ይህ አይነቱ ዚመመካኚር ፣ዚመወያዚትና ተናቩ ዚመስራት ተግባርም ለወደፊቱ ተጠናክሮ ዚሚቀጥል ይሆናል።

ሕዝበ ክርስቲያኑ በተለይም ደግሞ ወጣት ልጆቻቜን ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን በበዓል አኚባበሩ ዙሪያ በተደጋጋሚ በሚዲያዎቜ ያስተላለፈቻ቞ውን መልዕክቶቜ በመቀበል በዓሉ ዚቀተክርስቲያያቜንን ክብር በሚመጥን መልኩ ተኚብሮ እንዲውል በማድሚግ ሚገድ ያሳያቜሁት ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ጚዋነትን ዹተላበሰ ዹበዓል አኚባበር ሥርዓት ዹሚደነቅና ተጠናክሮ መቀጠል ዚሚገባው ነው።
በዚህም ቅድስት ኊርቶዶክሳዊት ቀተክርስቲያን ዚተሰማትን ደስታ ትገልጻለቜ።

በማዕኹል ደሹጃ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖትት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሚኒስትሮቜ፣ክብርት ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀና ኹፍተኛ ዚመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት በጃንሜዳ ባህሚ ጥምቀት ዹተኹበሹው በዓልም እጅግ ባማሚና በደመቀ መልኩ ተኚብሮ መዋል ይቜል ዘንድ ዚአዲስአበባ ኹተማ አስተዳደርና ክብርት ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀ ቅዱስነታ቞ው እና ዚክብር እንግዶቜ በዓሉን ያኚበሩበትን ስ቎ጅና ሳውንድ ሲስተም ኹነ ሙሉ ግበዓታ቞ው እንዲሁም ደሹጃቾውን ዹጠበቁ ድንኳኖቜን በማቅሚብ ለበዓላቜን ድምቀትና ማማር ትልቁን አስተዋጜኊ በማበርኚት ዚሚያስመሰግን ተግባር ፈጜመዋልፀለዚህም ቀተክርስቲያናቜን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለቜ።

በአጠቃላይ በዓላቜን በድምቀት ተኚብሮ መዋል እንዲቜል ዚደኚማቜሁ አካላት ሁሉ ልዑል እግዚአብሔር ዚድካማቜሁን ዋጋ እንዲኚፍላቜሁ ቅድስት ኊርቶዶክሳዊት ቀተክርስቲያናቜን ዚዘወትር ጞሎቷ ነው።

በተለይም በዓሉ ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተኚብሮ መዋል ይቜል ዘንድ ሌት ኹቀን ስትደክሙ ዚሰነበታቜሁ ዚጞጥታና ነደህንነት ዚጋራ ግብሚ ሃይል አባላት ድካምና ልፋታቜሁ ፍሬ አፍርቶ በዓሉ በሰላም ተኚብሮ በመዋሉ ቅድስት ኊሮቶዶሳዊት ቀተክርስቲያናቜን ዚተሰማትን ደስታ ኚታላቅ መንፈሳዊ ምስጋና ጋር እዚገለጞቜ እግዚአብሔር አምላክ ሥራቜሁን ሁሉ እንዲባርክና ዚዘወትር ጥበቃው እንዳይለያቜሁ አጥብቃ እንደምትጞልይላቜሁ ትገልጻለቜ።

ኹበዓሉ በፊት በዓሉን በተመለኹተ ዚቀተክርስቲያናቜንን መልዕክት በማስተላለፍ፣በበዓሉ ወቅትም ዹበዓል አኚባበር ሥርዓቱን ለመላው ዓለም በቀጥታና በዜና ሥርጭት በመዘገብ ላይ ለሰነበታቜሁ ዚሚዲያ ተቋማትና ጋዜጠኞቜም ቅድስት ቀተክርስቲያናቜን ልባዊ ምስጋናዋን እያቀሚበቜ ሥራቜሁ ሁሉ ዚተሳካና ውጀታማ እንዲሆንላቜሁ ልባዊ ምኞቷን ትገልጻለቜ።

በነገው እለት ወደዹ አብያተክርስቲያናቱ ዚሚገቡት ታቊታትም ልክ እንደዛሬው ዹበዓል አኚባበር ሥነሥርዓት ፍጹም ሰላማዊና ደማቅ በሆነ በመልኩ ይኚብሩ ዘንድ ሕዝበ ክርስቲያኑ በተለይም ወጣት ልጆቻቜን ታቊታቱ በሰላም ወደዹ መንበሹ ክብራ቞ው እንዲመለሱ ቀተክርቲያን ባስተማሚቻቜሁ ዚመተሳሰብ፣ዚመደጋገፍና ዚመኚባበር ሥርዓት መሰሚት ዚሚጠበቅባቜሁን ሃይማኖታዊ ግዎታ እንድትወጡ ቅድስት ኊርቶዶክሳዊት ቀተክርስቲያናቜን መልእክቷን ታስተላልፋለቜ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን
መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት

ጥር ፲፩ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
አዲስአበባ ኢትዮጵያ

ፎቶ ሪፖርታዥፊ ዚ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ዚጥምቀት በዓል አኚባበር

ፎቶ ሪፖርታዥፊ ዚ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ዚኚተራ በዓል አኚባበር

ዚኚተራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በተገኙበት በጃን ሜዳ በታላቅ ድምቀት ተኹበሹ

ጥር ፲ቀን ፳፻ ፲ወ፭ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“””””””””””””””””””””

ዚ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ዚኚተራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት በተገኙበት በጃንሜዳ ባህሚ ጥምቀት በታላቅ ሥነሥርዓት ተኚብሮ ውሏል።በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚኒዩወርክ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፣ክቡር ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን፣ዚጠቅላይ ቀተክህነት ዚመምሪያ ኃላፊዎቜ፣በተገኙበት ነው ዚተኚበሚው።

በጃን ሜዳ ባህሚ ጥምቀት ዚባለተራው ዚደብር ደብሚ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት ማርያም ቀተክርስቲያን ሊቃውንት መሪነት”ወሹደ ወልድ እምሰማያት”በቁም ዜማ በዝማሜና በጞናጜል ኚዘመሩ በኋላበፍስሐ ወበሰላም ዹሚለውን አመላለስ ለ፮ ደቂቃ ያህል አሞብሜበዋል።

በመቀጠልም ዚደብሚ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት ማርያም ቀተክርስቲያን ፍቁሹ እግዚእ ዚሰንበት ትምህርት ቀት ወጣቶቜ “ወነዋ ተወልደ ወነዋ ተጠምቀ መድሃኔ ዓለም። ፍሥሐ ለኚኲሉ ኲሉ ዘዹአምን”ዹሚለውን ለ፲፭ ደቂቃ ወሚብ አቅርበዋል ።

በመጚሚሻም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና ጾሎተ ቡራኬ ኚሰጡ በኋላ ታቊታቱ ወደ ተዘጋጀላቾው ድንኳን ገብተው ዹበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

እነሆ በውኃ እንዳልጠመቅ ዹሚኹለክለኝ ማን ነው?

ይህ ቃለ ሃይማኖት ኚኢትዮጵያዊው ጃንደሚባ አንደበት ዹተሰማ ድምፅ ነው (ግብ.ሐዋ. 8፥39)። ምሥራቅ አፍሪካዊቷ ሀገራቜን ቅድስት ኢትዮጵያ በኖሚቜባ቞ው ብዙ ሺህ ዓመታት ሁሉ መሠሚታዊ ታሪኳ ኚአምልኮተ እግዚአብሔር ጋር ዚተሳሰሚ ስለሆነ ሀገሹ እግዚአብሔር በመባል ትታወቃለቜ።

በቀዳማዊ ምኒልክ አማካኝነት በንጉሡ በዳዊት ልጅ በሰሎሞን ዘመን ጜላተ ሙሮን ኚነመስዋዕቱ፥ ሕገ ኊሪትን ኚነሥርዐቱ ተቀብላ ሀገራቜን ኢትዮጵያ አምልኮተ እግዚአብሔርን በዘመነ ብሉይ ስትፈጜም እንደነበር በቅዱስ መጜሐፍ ተመዝግቧል (1ነገ. 10፥9)። ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብኚቱ በዚህ ንስሓ በማይገባ ትውልድ ንግሥተ አዜብ ትፈርድበታለቜፀ ኚምድር ዳርቻ ዹሰሎሞንን ጥበብ ለማዚት መጥታለቜ ብሎ ሀገራቜንን ጠቅሷታል (ማቮ. 12፥40)።

ቀደምት ኢትዮጵያውያን አባቶቻቜንም ጣዖት ያላመለኩ፥ በሕገ ኊሪት በአምልኮተ እግዚአብሔር ዚኖሩ ስለነበር ኚኢትዮጵያ ወደ ኢዚሩሳሌም እዚሄዱ ይሰግዱ፥ ሥርዐተ ኊሪትን፥ ሕገ ኊሪትን ይፈጾሙ ነበር። በዚያም መሠሚት ነው «ወሖሚ ኢዚሩሳሌም ይስግድ ወእንዘ ይገብእ ነበሹ ዲበ ሠሹገላሁ ያነብብ መጜሐፍ ኢሳይያስ ነቢይ – ዚኢትዮጵያ ሰውም ሊሰግድ ወደ ኢዚሩሳሌም መጥቶ ነበርፀ ሲመለስም በሠሹገላ ተቀምጩ ዚነቢዩን ዚኢሳይያስን መጜሐፍ ያነብ ነበር። መንፈስ ቅዱስ ፊልጶስን ወደዚህ ሠሹገላ ቅሚብና ተገናኘው አለው» (ግብ.ሐዋ. 8፥28-32)።

ፊልጶስም መንፈስ ቅዱስ በነገሹው መሠሚት ወደ ሠሹገላው ሲቀርብ ኢትዮጵያዊውን መጜሐፈ ኢሳይያስን ጞሪቀ ሐዲስ በመባል ዚሚታወቀውን ምዕራፍ ሃምሳ ሊስትን ሲያነብ አገኘው። ፊልጶስም በውኑ ዚምታነበውን ታስተውለዋለህን አለው። ያለ መምህር እንዎት እሚዳዋለሁ፥ እባክህ ነቢዩ ስለምን እንደሚናገር አስሚዳኝ አለው። ፊልጶስም ለጃንደሚባው ኢትዮጵያዊ ወንጌል ሰበኚለት።

በመላው ዓለም ወንጌልን እንዲሰብኩ በጌታቜን በኢዚሱስ ክርስቶስ ዚታዘዙትን ሐዋርያት እኛን ኢትዮጵያውያንን ያገኙን ጣዖት እያመለክን አይደለምፀ ብሉይ ኪዳንን እያነበብን፥ እግዚአብሔርን እያመለክን እንጂ። በብሉይ ኪዳን በሕገ ኊሪት ዹለሰለሰ እርሻ ስለነበር ባለመቶ አድርጎ ዹወንጌልን ፍሬ ለማብቀል ጊዜ አልወሰደበትም። ኚፊልጶስ ጠቅላላ ነገሹ ክርስቶስን፥ ቅዱስ ወንጌልን ኹሰማና ኹተማሹ በኋላ «ውኃ ይኞውና፥ እንዳልጠመቅ ዹሚኹለክለኝ ምንድን ነው» ብሏል።

ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስም «ኚአመንክ ተፈቅዷል» አለው። ኢትዮጵያዊው ጃንደሚባም «ወይቀ አነ አአምን ኹመ ኢዚሱስ ክርስቶስ ወልዱ ለእግዚአብሔር — ኢዚሱስ ክርስቶስ ዚእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ» አለፀ ኚዚያም በኋላ ሠሹገላው እንዲቆም ሆነ። ወወሚዱ ኅቡሚ ኀበ ማይ ፊልጶስ ወውእቱ ኅጜው ወአጥመቆ እማይ ወእመንፈሰ እግዚአብሔር — ፊልጶስና ጃንደሚባውም ወደ ውኃው ወሚዱፀ አጠመቀውም።

ኢትዮጵያዊ ጃንደሚባ ዹተናገሹው ዚእምነት ቃል እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ነው። ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ሰው እኔን ማን ይለኛል ብሎ በተናገሹ ጊዜ፩ «ሌሎቜ ሙሮ ነህ፥ ኀልያስ ነህ፥ ዮሐንስ መጥምቅ ነህ፥ ወይም ኚነቢያት አንዱ ነህ» ይሉሃል አሉ። ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጎጥሮስ «አንተ ዚእግዚአብሔር ልጅ ነህ» ብሏል (ማቮ. 16፥16-20)። እንዲሁም ሐዋርያው ናትናኀል ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስን ኚበለስ ሥር አዚሁት ሲለው፥ አንተ ዚእግዚአብሔር ልጅ ነህ፥ ወልድ ነህ በማለት እምነቱን ገልጿል (ዹሐዋ.ሥራ 1፥48-53)። ሐዋርያው ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስም በወልድ ዚሚያምን ዹዘለዓለም ሕይወት አለው ብሏል።

ኢትዮጵያዊው ጃንደሚባ ኚፊልጶስ ቅዱስ ወንጌልን ተምሮ ሃይማኖቱን ሲገልጜፊ ኢዚሱስ ክርስቶስ ዚእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ ብሎ ሃይማኖቱን ተናግሮ፥ መስክሮ በሐዋርያው እጅ ተጠምቋል። ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን በደመ ክርስቶስ፥ በትምህርተ ሐዋርያት ዚተመሠሚተቜ ጥንታዊት፥ ሐዋርያዊት ናት ዚምትባለውም ስለዚህ ነው።

ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ኚሙታን ኚተነሣ በኋላ ወደ ሰማይ ኹማሹጉ በፊት «ሑሩ ወመሐሩ ኵሎ አሕዛበ ወእንዘ ታጠምቅዎሙ በሉ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ መሐርዎሙ ይዕቀቡ ኵሎ ዘአዘዝኩክሙ ወናሁ አነ እሄሎ ምስሌክሙ በኵሉ መዋዕለ እስኚ ሕልፈተ ዓለም — እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃቜሁ፥ ያዘዝኋቜሁን ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራቜሁ ደቀ መዛሙርት አድርጓ቞ውፀ እኔ እስኚ ዓለም ፍጻሜ ድሚስ ሁልጊዜ ኚእናንተ ጋር ነኝ» (ማቮ. 18፥19-20) ሲል መሠሚታዊውን ዚቀተ ክርስቲያን ተልዕኮና ሥራ ለደቀ መዛሙርቱ ተናግሯል።

በዚህ በጌታቜን በአምላካቜን በኢዚሱስ ክርስቶስ አምላካዊ ትእዛዝ መሠሚት ቅድስት ቀተ ክርስቲያን ዹምንጊዜም ሥራዋና ተልዕኮዋ ቅዱስ ወንጌልን ማስተማር፥ ማጥመቅ፥ ማቍሚብ ነው። ቀተ ክርስቲያን ሰፋቜ፥ ጠነኚሚቜ፥ ታነጞቜ ዚሚባለው ብዙ ቍጥር ያላ቞ው ሰዎቜ እያመኑ ተጠምቀው ዚክርስቶስ ተኚታዮቜ ሲሆኑ ነው።

ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ኚሙታን ተለይት በተነሣ በ40 ቀኑ ወደ ሰማይ ሲዐርግ እጆቹን በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ ዘርግቶ ባርኮ ሥልጣነ ክህነትን ለሐዋርያት ሰጥቷል (ሉቃ. 24፥50)። ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ያጠመቁት፥ ኚጌታ በምድር ዚሠራቜሁት በሰማይ ዚታሠሚ ነውፀ በምድር ዚፈታቜሁት በሰማይ ዚተፈታ ነው ተብሎ በተሰጣ቞ው ሥልጣነ ክህነት ነው። ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ኚጌታ ያገኙትን ሥልጣነ ክህነት በአንብሮተ እድ አስተላልፈዋል (ግብ.ሐዋ. 6፥1-6)። ይህም ቅድስት ቀተ ክርስቲያን ዚምትመራበት ሥልጣነ ክህነት ኚአበው ወደአበው ሲተላለፍ ይኖራል (1ጢሞ. 5፥22)።

እንግዲህ ኹላይ በተገለጾው መሠሚት ዚሥላሎን ልጅነት ኚሚያስገኘው ኹመርገመ ኀጢአት፥ ኚዲያብሎስ ቁራኝነት ዚሚያላቅቀው ዚክርስትና ጥምቀት ሥልጣነ ክህነት ባለው ካህን መፈጾም አለበት። ጥምቀተ ክርስትና ለአማኙ ዹሚፈጾመው በቅድስት ቀተ ክርስቲያን ብቻ ነው። ዹተጠመቀ ሰው በዕለቱ መቍሚብ አለበት። ስለ ጥምቀተ ክርስትና አፈጻጞም ፍትሐ ነገሥት አንቀጜ 3 ኹቍ. 20-30 እንዲህ ይላል፩

«ጥምቀትሰ ሥርዕ ላዕለ ዕደው ወአንስት ገውሶሙ ወዐቢዮሙ በእንተ ዘይቀ እግዚአብሔር ሎቱ ስብሐት ዘኢተወልደ እማይ ወእመንፈስ ቅዱስ ኢይሬእያ ለመንግሥተ እግዚአብሔር — ጥምቀትስ ለወንዶቜም ለሎቶቜም፥ ለትልቁም ለትንሹም ዚታዘዘ፥ ዚተገባ ነው። ክብር ይግባውና ጌታቜን በወንጌል ኹውኃና ኚመንፈስ ያልተወለደ ዚእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም ስለአለ» ይልናፀ አያይዞም ስለዚህ ይህ አንቀጜ አፈጻጞሙ ሲናገር «ኢያጥምቅ ዘእንበለ ኀጲስቆጶስ አው ቀሲስ ወዲያቆናት ይትልአኩ ምስሌሆሙ — ኚኀጲስ ቆጶስ ወይም ኚቄሱ በስተቀር ማንም አያጥምቅፀ ዲያቆናት ግን ኚእነርሱ ያገልግሉፀ ይላላኩ።» «ወለእመቊ ብእሲ ዘተወክፈ ጥምቀተ እምአላውያን ኢኮነ ውእቱ ምእመነ — ኹመናፍቃን ጥምቀትን ዹተቀበለ ሰው ቢኖር አማኝ ዚክርስቶስ ተኚታይ አይደለም ይላል»ፀ ይቀጥልናፊ ሎቶቜ ወንዶቜን ክርስትና አያንሱፀ ወንዶቜ ወንዶቜን፥ ሎቶቜ ሎቶቜን ያንሱ በማለት ያስሚዳል።

ወንጌላዊው ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ኚጌታ ጎን በፈሰሰው ማዹ ገቩ አማኞቜ ተጠምቀው ልጅነት እንደሚያገኙ በሀብተ መንፈስ ቅዱስ እንደሚኚብሩ ሲገልጜፊ

«አኮ በማይ ባሕቲቱ አላ በማይኒ ወለአምኒ ወበመንፈስ ውእቱ ዘስምዐ ይኹውን ኹመ መንፈሰ ጜድቅ፥ ሠለስቲሆሙ አሐዱ እሙንቱ — በውኃ ብቻ አይደለም ዚዕለት ጜንስ በመሆን በደማዊ አካል በመገለጜ ዚባሕርይ አምላክ እንደሆነ በሚመሰክር በመንፈስ ቅዱስም ነው እንጅ» (1ዮሐ. 5፥6-10)። ይህም ማለት ካህናት ዕለት ዕለት በስመ ሥላሎ በሚለውጡት ማዹ ገቊ፥ በሚያሰጡት ሀብተ መንፈስ ነው። በደምኒ ማለት በደመ ላሕም፥ በደመ በግዕ ሳይሆን በራሱ ክቡር ደም በደመ ገቊ፥ በመንፈሰ ሚድኀት ሳይሆን በመንፈሰ ልደት ነው።

ሠለስቲሆሙ አሐዱ ማለት ደግሞ ሊስቱ እንደ ሰው ይቀበልቾዋልና በአንድ ቄስ እጅ ሲሰጡ ይኖራሉ። አንድ ክብሚ መንግሥተ ሰማያትን ያስገኛሉ፥ በማለት ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ሊቃውንት ይተሚጒማሉ።

ታላቁ ሐዋርያ መምህሹ አሕዛብ ቅዱስ ጳውሎስ «ኚመ ትኩን አሐደ ሥጋ ወአሐደ መንፈስ በኹም ተጾዋዕክሙ ለአሐዱ ተስፋክሙ አሐዱ እግዚአብሔር ወአሐቲ ሃይማኖት ወአሐቲ ጥምቀት — በአንድ ተስፋ እንደተጠራቜሁ እንደ አካልና እንደ መንፈስ አለ አንድ ጌታ፥ አንዲት ሃይማኖት፥ አንዲት ጥምቀት»  (ኀፌ. 4፥4-6)። በዚህ ዚሐዋርያው ዚቅዱስ ጳውሎስ አስተምህሮ መሠሚት ጥምቀተ ክርስትና አንድ ጊዜ ብቻ ይፈጾማል እንጅ አይደገምምፀ ጥምቀት አንዲት ናትና። በአንዲት ጥምቀት እናምናለን ተብሎ ዚተጻፈውም ስለዚህ ነው። ሃይማኖትን መለወጥ ጥምቀትን ማርኚስ ለዘለዓለም ኚእግዚአብሔር ዹሚለይ ክፉ በደልና ክሕደት ነው።

በእግዚአብሔር አምኖ በስሙ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ሥልጣነ ክህነት ባለው ካህን እጅ መጠመቅ ዚመንግሥተ ሰማያት በር መግቢያ ቁልፍ መያዝ፥ ዹዘለዓለም ሕይወት ማግኘት ነው። ስለዚህም ነበር ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ልጅነትን ዚምታሰጥ፥ ዚኀጢአት ሥርዚት ብቻ ዚምትሆን ጥምቀት እያጠመቀ ፍጹም ለሆነ መርገመ ኀጢአት ለሚወገድበት፥ ዚሥላሎ ልጅነት ለሚገኝበት ጥምቀት ሲናገርፊ «ንስሐ ግቡፀ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለቜና» ብሎ ነበሹ (ማቮ. 3፥4)። ይህም ማለት መንግሥተ ሰማያት በልጅነት በሃይማኖት ልትሰጥ ቀርባለቜና እያለ ያስተማሚውን ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ዚትምህርቱ መጀመሪያ አድርጎታል። በዮሐንስ አድሮ ዹተናገሹ እርሱ ስለሆነ ነው። (ማቮ. 4፥17)

ቅዱሳን ሐዋርያትም በበዓለ ጰራቅሊጊስ ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ኚአስተማሩ በኋላ ትምህርታ቞ውን ዹተቀበሉ ሕዝብ ምን እናድርግ ሲሏ቞ውፊ ንስሐ ግቡ ኀጢአታቜሁ ይሰሹይ ዘንድ ልጅነትን እንድታገኙ ኚኀጢአት መርገም እንድትላቀቁ በኢዚሱስ ክርስቶስ ተጠመቁፀ ዚመንፈስ ቅዱስን ስጊታ ትቀበላላቜሁፀ ዚተስፋው ቃል ለእናንተና ለልጅ ልጆቻቜሁ ጌታ አምላካቜን ወደ እርሱ ለሚጠራ቞ው በሩቅ ላሉት ሁሉ ነውና (ግብ. ሐዋ. 2፥37-40)።

ዚቀተ ክርስቲያን ዚልደት ቀን በመባል በሚታወቀው በበዓለ ጰራቅሊጊስ ቅዱሳን አበው ሐዋርያት በሚድኀተ መንፈስ ቅዱስ ሲያስተምሩ በዚያቜ ቀን ብቻ ሊስት ሺህ ሰዎቜ አምነው ተጠምቀው ልጅነት ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለዋል።

ጥንታዊት ሐዋርያዊት ዚሆነቜው ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን በትምህርተ ሐዋርያት ዚተመሠሚተቜ በመሆኗ ዹምንጊዜም ዚዕለት ተዕለት ተልዕኮዋ ወንጌል ማስተማር በመዓርገ ክህነት ማጥመቅ፥ ማቍሚብ ነው። ቅድስት ዚሆነቜው ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ዚቅዱሳን አበው ሐዋርያት ትውፊትና ቀኖና፥ ሥርዐትና አስተምህሮ በመጠበቅ እስኚ ሕልፈተ ዓለም ትኖራለቜ።

 

ዚጌታቜን ዚኢዚሱስ ክርስቶስ ምሕሚትና ይቅርታ በሁላቜን ላይ ይሁን።

 

መጋቀ አእላፍ ኀፍሬም በዹነ

ዚልሣነ ተዋሕዶ መጜሔት ዋና አዘጋáŒ