የጥምቀት በዓልን በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን

የ2015 ዓ/ም የከተራ እና የጥምቀት በዓልን በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን ለማክበር ዓርብ ምሽት የተጓዙት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ እና የኒውዮርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቆይታቸውን በመግታት ወደ አዲስ አበባ ገቡ።

“ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በደረሰባት የውስጥ ፈተና ሀዘኗ ከባድ ነው።” ብፁዕ አቡነ አብርሃም

“ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በደረሰባት የውስጥ ፈተና ሀዘኗ ከባድ ነው።” ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ብፁዕ አቡነ አብርሃም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህን የገለጹት በዛሬው ዕለት ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጪ የተፈጸመውን “የጳጳስ ሹመት” አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ነው።

ብፁዕነታቸው እንደገለጹት በፈተና የሚያጸናው ሁል ጊዜ ፈተናዎችን እያሳለፈ ለዘመናት ሲጠብቃት የነበረ እግዚአብሔር ዛሬም ጥበቃውና መግቦቱ እንደማይለያት ሙሉ እምነት አለን። በደረሰው ክስተትም እጅግ አዝነናል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ታዝናለች።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከ3ሺ ዘመን በላይ የራሷን አንድነት ከማስጠበቅ አልፋ የሀገርን አንድነት ስታስጠብቅ ለሰው ልጆች አንድነት ትልቁን ድርሻ በመውሰድ ስትሠራ የኖረች አሁንም ያለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነች በማለት ገልጸዋል።

ይህንን አንድነቷን የሚንድ ሕጋዊ ሰውነቷን የሚጥስ አላስፈላጊ ክስተት ተፈፅሟል። በዚህም ቅዱስ ፓትርያርኩ በአስተላለፉት ጥሪ መሠረት ከሀገር ውስጥ ከሀገር ውጭ የምትገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከነገው ዕለት ጀምሮ የቅዱስነታቸውን ጥሪ በመቀበል እንድትገኙ በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል።

ብፁዕነታቸው አክለውም የተፈጠረውን ችግር በዝርዝርና በጥናት ቅዱስ ሲኖዶስ አይቶ የመጨረሻውን ውሳኔ እስከሚሰጥበት ጊዜ ድረስ ምእመናንና አገልጋዮች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሁላችሁም በየአላችሁበት ቤተ ክርስቲያንን እንድትጠብቁ ሲሉ አሳስበዋል። ተመሳስለውና የሌለ ሀሳብ እያቀረቡ ሕዝብን ከሚለያዩ ሠዎች እንድትጠበቁና እንድትጠብቁ በጽናት፣ በትእግስትና በፍቅር ሕጋዊ በሆነ ነገር ሁሉ ቤተ ክርስቲያንን እንድትጠብቋት በአንድነቷ የተረከብናትን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአንድነቷ ለነገው ትውልድ ለማስረከብ የእያንዳንዳችንን ድርሻ እንድንወጣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ብለዋል።

በመጨረሻም ሕጋዊ ሰውነቷ የተረጋገጠ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሕጋዊ ሰውነቷ የመጠበቅ የማስጠበቅ ኃላፊነቱ የመንግሥት ስለሆነ ይህን የተፈጸመውን ግፍ መንግሥት ተመልክቶ የቤተ ክርስቲያኗን ሉዓላዊነት በመጠበቅና በማስጠበቅ የራሱን ድርሻ እንዲወጣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪ አቅርበዋል ።

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መግለጫ ተሰጠ

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ
ቤተክርስቲያን መግለጫ ተሰጠ ።
****
ጥር ፩፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ

መግለጫውን የሠጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ቀዳማዊ ፖትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት; ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አኪያጅና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ : በመንበረ ፓትርያርክ የተገኙ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ናቸው።

ቅዱስነታቸው ዛሬ ማለዳ በተሰማው ሕገ ወጥ “ሢመተ ጳጳሳት” ጉዳይ በሰጡት መግለጫ ጉዳዩ ከቅዱስ ሲኖዶስ እውቅና ውጪ በሕገወጥነት የተከናወነ መሆኑን በመግለጽ :-
1. በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ያሉ ሊቃነ ጳጳሳት በአስቸኳይ ወደ መንበረ ፓትርያርክ እንዲመጡ ጥሪ ቀርቧል።
2. መንግሥት ክስተቱ በሀገር ላይ ጭምር የሚያስከትለውን ጉዳት ተመልክቶ በጉዳዩ ላይ ሕጋዊ ሓላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል።
3. ምዕመናን ቤተክርስቲያንን ከመቸውም ጊዜ በላይ በንቃት እንዲጠብቁ ቅዱስነታቸው ጥሪ አቅርበዋል።©EOTC TV

በበረዶዋማ ፊንላንድ አገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የጥምቀት በዓልን በድምቀት አከበሩ።

የስዊድን፣ ስካንዲናቪያንና የግሪክ ሀገሮች ሀገረ ስብከት በፊንላንድ ሄልሲንኪ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን፣ ዛሬ ጥር 13 ቀን 2015 ዓ.ም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሰሱ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በርካታ ምእመናን በተገኘበት በድምቀት ተከሯል።

የጋምቤላ የጥምቀት በዓል አከባበር

የጋምቤላ የጥምቀት በዓል አከባበር ዛሬም ቀጥሏል እስከ ሰኞ ጥር 15 ይቀጥላል።

የ ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የጥምቀት በዓል በሰላም ተከብሮ መዋልን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የተሰጠ መግለጫ ፤

የ ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የጥምቀት በዓል በሰላም ተከብሮ መዋልን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የተሰጠ መግለጫ ፤
******

ጥር ፲፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
አዲስአበባ ኢትዮጵያ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በየ ዓመቱ ጥር፲ ና ፲፩ቀን የሚከበሩት የከተራና የጥምቀት በዓላት ዘንድሮም በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት ተከብረው ውለዋል።ይህ በቤተክርስቲያናችን የሰላም፣የስምምነት ፣የአንድነትና የመከባበር መገለጫ የሆነው በዓላችን ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ከበዓሉ ቀድሞ ዐቢይ ኮሚቴ በማቋቋም በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ቆይቷል።

የተቋቋመው ዐቢይ ኮሚቴም ንዑሳን ኮሚቴዎቻችን በማደራጀት በየተመደበበት ኮሚቴ ውጤታማ ሥራዎችን አከናውኗል።ይህም በመሆኑ በልዑል እግዚአብሔር ረድኤትና በረከት ስኬታማ በዓል ለማክበር ችለናል።

በተለይም የጠቅላይ ቤተክህነትና የመንግስት የጸጥታ አካላት ያደረጉት የተጣመረ እንቅስቃሴ ለበዓሉ ድምቀትና ማማር እንዲሁም ሰላማዊ በሆነ መልኩ መከበር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደነበረው ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን ትገነዘባለች።

ለዚህ ስኬታማ የበዓል አከባበር ቤተክርስቲያናችን ከበዓሉ ቀደም ብላ ከካህናት፣ከወጣት የቤተክርስቲያናችን ልጆችና ኦርቶዶክሳዊ ከሆኑ የሚዲያ ተቋማት ጋር ያደረገቻቸው ውጤታማ ውይይቶች በእርግጥም ተነጋግሮ፣ተመካክሮና ተናቦ መስራት ለውጤት የሚያበቃ መሆኑን ያረጋገጡ ናቸው።ይህ አይነቱ የመመካከር ፣የመወያየትና ተናቦ የመስራት ተግባርም ለወደፊቱ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል።

ሕዝበ ክርስቲያኑ በተለይም ደግሞ ወጣት ልጆቻችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በበዓል አከባበሩ ዙሪያ በተደጋጋሚ በሚዲያዎች ያስተላለፈቻቸውን መልዕክቶች በመቀበል በዓሉ የቤተክርስቲያያችንን ክብር በሚመጥን መልኩ ተከብሮ እንዲውል በማድረግ ረገድ ያሳያችሁት ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ጨዋነትን የተላበሰ የበዓል አከባበር ሥርዓት የሚደነቅና ተጠናክሮ መቀጠል የሚገባው ነው።
በዚህም ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን የተሰማትን ደስታ ትገልጻለች።

በማዕከል ደረጃ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖትት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሚኒስትሮች፣ክብርት ከንቲባ አዳነች አቤቤና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት በጃንሜዳ ባህረ ጥምቀት የተከበረው በዓልም እጅግ ባማረና በደመቀ መልኩ ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ የአዲስአበባ ከተማ አስተዳደርና ክብርት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ቅዱስነታቸው እና የክብር እንግዶች በዓሉን ያከበሩበትን ስቴጅና ሳውንድ ሲስተም ከነ ሙሉ ግበዓታቸው እንዲሁም ደረጃቸውን የጠበቁ ድንኳኖችን በማቅረብ ለበዓላችን ድምቀትና ማማር ትልቁን አስተዋጽኦ በማበርከት የሚያስመሰግን ተግባር ፈጽመዋል፤ለዚህም ቤተክርስቲያናችን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለች።

በአጠቃላይ በዓላችን በድምቀት ተከብሮ መዋል እንዲችል የደከማችሁ አካላት ሁሉ ልዑል እግዚአብሔር የድካማችሁን ዋጋ እንዲከፍላችሁ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን የዘወትር ጸሎቷ ነው።

በተለይም በዓሉ ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተከብሮ መዋል ይችል ዘንድ ሌት ከቀን ስትደክሙ የሰነበታችሁ የጸጥታና ነደህንነት የጋራ ግብረ ሃይል አባላት ድካምና ልፋታችሁ ፍሬ አፍርቶ በዓሉ በሰላም ተከብሮ በመዋሉ ቅድስት ኦሮቶዶሳዊት ቤተክርስቲያናችን የተሰማትን ደስታ ከታላቅ መንፈሳዊ ምስጋና ጋር እየገለጸች እግዚአብሔር አምላክ ሥራችሁን ሁሉ እንዲባርክና የዘወትር ጥበቃው እንዳይለያችሁ አጥብቃ እንደምትጸልይላችሁ ትገልጻለች።

ከበዓሉ በፊት በዓሉን በተመለከተ የቤተክርስቲያናችንን መልዕክት በማስተላለፍ፣በበዓሉ ወቅትም የበዓል አከባበር ሥርዓቱን ለመላው ዓለም በቀጥታና በዜና ሥርጭት በመዘገብ ላይ ለሰነበታችሁ የሚዲያ ተቋማትና ጋዜጠኞችም ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ልባዊ ምስጋናዋን እያቀረበች ሥራችሁ ሁሉ የተሳካና ውጤታማ እንዲሆንላችሁ ልባዊ ምኞቷን ትገልጻለች።

በነገው እለት ወደየ አብያተክርስቲያናቱ የሚገቡት ታቦታትም ልክ እንደዛሬው የበዓል አከባበር ሥነሥርዓት ፍጹም ሰላማዊና ደማቅ በሆነ በመልኩ ይከብሩ ዘንድ ሕዝበ ክርስቲያኑ በተለይም ወጣት ልጆቻችን ታቦታቱ በሰላም ወደየ መንበረ ክብራቸው እንዲመለሱ ቤተክርቲያን ባስተማረቻችሁ የመተሳሰብ፣የመደጋገፍና የመከባበር ሥርዓት መሰረት የሚጠበቅባችሁን ሃይማኖታዊ ግዴታ እንድትወጡ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን መልእክቷን ታስተላልፋለች።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት

ጥር ፲፩ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
አዲስአበባ ኢትዮጵያ

የከተራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በተገኙበት በጃን ሜዳ በታላቅ ድምቀት ተከበረ

ጥር ፲ቀን ፳፻ ፲ወ፭ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“””””””””””””””””””””

የ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የከተራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በተገኙበት በጃንሜዳ ባህረ ጥምቀት በታላቅ ሥነሥርዓት ተከብሮ ውሏል።በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒዩወርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፣ክቡር ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን፣የጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች፣በተገኙበት ነው የተከበረው።

በጃን ሜዳ ባህረ ጥምቀት የባለተራው የደብር ደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ሊቃውንት መሪነት”ወረደ ወልድ እምሰማያት”በቁም ዜማ በዝማሜና በጸናጽል ከዘመሩ በኋላበፍስሐ ወበሰላም የሚለውን አመላለስ ለ፴ ደቂቃ ያህል አሸብሽበዋል።

በመቀጠልም የደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ፍቁረ እግዚእ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች “ወነዋ ተወልደ ወነዋ ተጠምቀ መድሃኔ ዓለም። ፍሥሐ ለከኲሉ ኲሉ ዘየአምን”የሚለውን ለ፲፭ ደቂቃ ወረብ አቅርበዋል ።

በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ታቦታቱ ወደ ተዘጋጀላቸው ድንኳን ገብተው የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

እነሆ በውኃ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ማን ነው?

ይህ ቃለ ሃይማኖት ከኢትዮጵያዊው ጃንደረባ አንደበት የተሰማ ድምፅ ነው (ግብ.ሐዋ. 8፥39)። ምሥራቅ አፍሪካዊቷ ሀገራችን ቅድስት ኢትዮጵያ በኖረችባቸው ብዙ ሺህ ዓመታት ሁሉ መሠረታዊ ታሪኳ ከአምልኮተ እግዚአብሔር ጋር የተሳሰረ ስለሆነ ሀገረ እግዚአብሔር በመባል ትታወቃለች።

በቀዳማዊ ምኒልክ አማካኝነት በንጉሡ በዳዊት ልጅ በሰሎሞን ዘመን ጽላተ ሙሴን ከነመስዋዕቱ፥ ሕገ ኦሪትን ከነሥርዐቱ ተቀብላ ሀገራችን ኢትዮጵያ አምልኮተ እግዚአብሔርን በዘመነ ብሉይ ስትፈጽም እንደነበር በቅዱስ መጽሐፍ ተመዝግቧል (1ነገ. 10፥9)። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ በዚህ ንስሓ በማይገባ ትውልድ ንግሥተ አዜብ ትፈርድበታለች፤ ከምድር ዳርቻ የሰሎሞንን ጥበብ ለማየት መጥታለች ብሎ ሀገራችንን ጠቅሷታል (ማቴ. 12፥40)።

ቀደምት ኢትዮጵያውያን አባቶቻችንም ጣዖት ያላመለኩ፥ በሕገ ኦሪት በአምልኮተ እግዚአብሔር የኖሩ ስለነበር ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም እየሄዱ ይሰግዱ፥ ሥርዐተ ኦሪትን፥ ሕገ ኦሪትን ይፈጸሙ ነበር። በዚያም መሠረት ነው «ወሖረ ኢየሩሳሌም ይስግድ ወእንዘ ይገብእ ነበረ ዲበ ሠረገላሁ ያነብብ መጽሐፍ ኢሳይያስ ነቢይ – የኢትዮጵያ ሰውም ሊሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር፤ ሲመለስም በሠረገላ ተቀምጦ የነቢዩን የኢሳይያስን መጽሐፍ ያነብ ነበር። መንፈስ ቅዱስ ፊልጶስን ወደዚህ ሠረገላ ቅረብና ተገናኘው አለው» (ግብ.ሐዋ. 8፥28-32)።

ፊልጶስም መንፈስ ቅዱስ በነገረው መሠረት ወደ ሠረገላው ሲቀርብ ኢትዮጵያዊውን መጽሐፈ ኢሳይያስን ጸሪቀ ሐዲስ በመባል የሚታወቀውን ምዕራፍ ሃምሳ ሦስትን ሲያነብ አገኘው። ፊልጶስም በውኑ የምታነበውን ታስተውለዋለህን አለው። ያለ መምህር እንዴት እረዳዋለሁ፥ እባክህ ነቢዩ ስለምን እንደሚናገር አስረዳኝ አለው። ፊልጶስም ለጃንደረባው ኢትዮጵያዊ ወንጌል ሰበከለት።

በመላው ዓለም ወንጌልን እንዲሰብኩ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የታዘዙትን ሐዋርያት እኛን ኢትዮጵያውያንን ያገኙን ጣዖት እያመለክን አይደለም፤ ብሉይ ኪዳንን እያነበብን፥ እግዚአብሔርን እያመለክን እንጂ። በብሉይ ኪዳን በሕገ ኦሪት የለሰለሰ እርሻ ስለነበር ባለመቶ አድርጎ የወንጌልን ፍሬ ለማብቀል ጊዜ አልወሰደበትም። ከፊልጶስ ጠቅላላ ነገረ ክርስቶስን፥ ቅዱስ ወንጌልን ከሰማና ከተማረ በኋላ «ውኃ ይኸውና፥ እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምንድን ነው» ብሏል።

ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስም «ከአመንክ ተፈቅዷል» አለው። ኢትዮጵያዊው ጃንደረባም «ወይቤ አነ አአምን ከመ ኢየሱስ ክርስቶስ ወልዱ ለእግዚአብሔር — ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ» አለ፤ ከዚያም በኋላ ሠረገላው እንዲቆም ሆነ። ወወረዱ ኅቡረ ኀበ ማይ ፊልጶስ ወውእቱ ኅጽው ወአጥመቆ እማይ ወእመንፈሰ እግዚአብሔር — ፊልጶስና ጃንደረባውም ወደ ውኃው ወረዱ፤ አጠመቀውም።

ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ የተናገረው የእምነት ቃል እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው እኔን ማን ይለኛል ብሎ በተናገረ ጊዜ፦ «ሌሎች ሙሴ ነህ፥ ኤልያስ ነህ፥ ዮሐንስ መጥምቅ ነህ፥ ወይም ከነቢያት አንዱ ነህ» ይሉሃል አሉ። ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ «አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ» ብሏል (ማቴ. 16፥16-20)። እንዲሁም ሐዋርያው ናትናኤል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከበለስ ሥር አየሁት ሲለው፥ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፥ ወልድ ነህ በማለት እምነቱን ገልጿል (የሐዋ.ሥራ 1፥48-53)። ሐዋርያው ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስም በወልድ የሚያምን የዘለዓለም ሕይወት አለው ብሏል።

ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ከፊልጶስ ቅዱስ ወንጌልን ተምሮ ሃይማኖቱን ሲገልጽ፦ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ ብሎ ሃይማኖቱን ተናግሮ፥ መስክሮ በሐዋርያው እጅ ተጠምቋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደመ ክርስቶስ፥ በትምህርተ ሐዋርያት የተመሠረተች ጥንታዊት፥ ሐዋርያዊት ናት የምትባለውም ስለዚህ ነው።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት «ሑሩ ወመሐሩ ኵሎ አሕዛበ ወእንዘ ታጠምቅዎሙ በሉ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ መሐርዎሙ ይዕቀቡ ኵሎ ዘአዘዝኩክሙ ወናሁ አነ እሄሎ ምስሌክሙ በኵሉ መዋዕለ እስከ ሕልፈተ ዓለም — እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ፥ ያዘዝኋችሁን ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችሁ ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ» (ማቴ. 18፥19-20) ሲል መሠረታዊውን የቤተ ክርስቲያን ተልዕኮና ሥራ ለደቀ መዛሙርቱ ተናግሯል።

በዚህ በጌታችን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ ትእዛዝ መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምንጊዜም ሥራዋና ተልዕኮዋ ቅዱስ ወንጌልን ማስተማር፥ ማጥመቅ፥ ማቍረብ ነው። ቤተ ክርስቲያን ሰፋች፥ ጠነከረች፥ ታነጸች የሚባለው ብዙ ቍጥር ያላቸው ሰዎች እያመኑ ተጠምቀው የክርስቶስ ተከታዮች ሲሆኑ ነው።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይት በተነሣ በ40 ቀኑ ወደ ሰማይ ሲዐርግ እጆቹን በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ ዘርግቶ ባርኮ ሥልጣነ ክህነትን ለሐዋርያት ሰጥቷል (ሉቃ. 24፥50)። ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ያጠመቁት፥ ከጌታ በምድር የሠራችሁት በሰማይ የታሠረ ነው፤ በምድር የፈታችሁት በሰማይ የተፈታ ነው ተብሎ በተሰጣቸው ሥልጣነ ክህነት ነው። ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ከጌታ ያገኙትን ሥልጣነ ክህነት በአንብሮተ እድ አስተላልፈዋል (ግብ.ሐዋ. 6፥1-6)። ይህም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትመራበት ሥልጣነ ክህነት ከአበው ወደአበው ሲተላለፍ ይኖራል (1ጢሞ. 5፥22)።

እንግዲህ ከላይ በተገለጸው መሠረት የሥላሴን ልጅነት ከሚያስገኘው ከመርገመ ኀጢአት፥ ከዲያብሎስ ቁራኝነት የሚያላቅቀው የክርስትና ጥምቀት ሥልጣነ ክህነት ባለው ካህን መፈጸም አለበት። ጥምቀተ ክርስትና ለአማኙ የሚፈጸመው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ብቻ ነው። የተጠመቀ ሰው በዕለቱ መቍረብ አለበት። ስለ ጥምቀተ ክርስትና አፈጻጸም ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 3 ከቍ. 20-30 እንዲህ ይላል፦

«ጥምቀትሰ ሥርዕ ላዕለ ዕደው ወአንስት ገውሶሙ ወዐቢዮሙ በእንተ ዘይቤ እግዚአብሔር ሎቱ ስብሐት ዘኢተወልደ እማይ ወእመንፈስ ቅዱስ ኢይሬእያ ለመንግሥተ እግዚአብሔር — ጥምቀትስ ለወንዶችም ለሴቶችም፥ ለትልቁም ለትንሹም የታዘዘ፥ የተገባ ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን በወንጌል ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም ስለአለ» ይልና፤ አያይዞም ስለዚህ ይህ አንቀጽ አፈጻጸሙ ሲናገር «ኢያጥምቅ ዘእንበለ ኤጲስቆጶስ አው ቀሲስ ወዲያቆናት ይትልአኩ ምስሌሆሙ — ከኤጲስ ቆጶስ ወይም ከቄሱ በስተቀር ማንም አያጥምቅ፤ ዲያቆናት ግን ከእነርሱ ያገልግሉ፤ ይላላኩ።» «ወለእመቦ ብእሲ ዘተወክፈ ጥምቀተ እምአላውያን ኢኮነ ውእቱ ምእመነ — ከመናፍቃን ጥምቀትን የተቀበለ ሰው ቢኖር አማኝ የክርስቶስ ተከታይ አይደለም ይላል»፤ ይቀጥልና፦ ሴቶች ወንዶችን ክርስትና አያንሱ፤ ወንዶች ወንዶችን፥ ሴቶች ሴቶችን ያንሱ በማለት ያስረዳል።

ወንጌላዊው ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ከጌታ ጎን በፈሰሰው ማየ ገቦ አማኞች ተጠምቀው ልጅነት እንደሚያገኙ በሀብተ መንፈስ ቅዱስ እንደሚከብሩ ሲገልጽ፦

«አኮ በማይ ባሕቲቱ አላ በማይኒ ወለአምኒ ወበመንፈስ ውእቱ ዘስምዐ ይከውን ከመ መንፈሰ ጽድቅ፥ ሠለስቲሆሙ አሐዱ እሙንቱ — በውኃ ብቻ አይደለም የዕለት ጽንስ በመሆን በደማዊ አካል በመገለጽ የባሕርይ አምላክ እንደሆነ በሚመሰክር በመንፈስ ቅዱስም ነው እንጅ» (1ዮሐ. 5፥6-10)። ይህም ማለት ካህናት ዕለት ዕለት በስመ ሥላሴ በሚለውጡት ማየ ገቦ፥ በሚያሰጡት ሀብተ መንፈስ ነው። በደምኒ ማለት በደመ ላሕም፥ በደመ በግዕ ሳይሆን በራሱ ክቡር ደም በደመ ገቦ፥ በመንፈሰ ረድኤት ሳይሆን በመንፈሰ ልደት ነው።

ሠለስቲሆሙ አሐዱ ማለት ደግሞ ሦስቱ እንደ ሰው ይቀበልቸዋልና በአንድ ቄስ እጅ ሲሰጡ ይኖራሉ። አንድ ክብረ መንግሥተ ሰማያትን ያስገኛሉ፥ በማለት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ይተረጒማሉ።

ታላቁ ሐዋርያ መምህረ አሕዛብ ቅዱስ ጳውሎስ «ከመ ትኩን አሐደ ሥጋ ወአሐደ መንፈስ በከም ተጸዋዕክሙ ለአሐዱ ተስፋክሙ አሐዱ እግዚአብሔር ወአሐቲ ሃይማኖት ወአሐቲ ጥምቀት — በአንድ ተስፋ እንደተጠራችሁ እንደ አካልና እንደ መንፈስ አለ አንድ ጌታ፥ አንዲት ሃይማኖት፥ አንዲት ጥምቀት»  (ኤፌ. 4፥4-6)። በዚህ የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ አስተምህሮ መሠረት ጥምቀተ ክርስትና አንድ ጊዜ ብቻ ይፈጸማል እንጅ አይደገምም፤ ጥምቀት አንዲት ናትና። በአንዲት ጥምቀት እናምናለን ተብሎ የተጻፈውም ስለዚህ ነው። ሃይማኖትን መለወጥ ጥምቀትን ማርከስ ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር የሚለይ ክፉ በደልና ክሕደት ነው።

በእግዚአብሔር አምኖ በስሙ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ሥልጣነ ክህነት ባለው ካህን እጅ መጠመቅ የመንግሥተ ሰማያት በር መግቢያ ቁልፍ መያዝ፥ የዘለዓለም ሕይወት ማግኘት ነው። ስለዚህም ነበር ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ልጅነትን የምታሰጥ፥ የኀጢአት ሥርየት ብቻ የምትሆን ጥምቀት እያጠመቀ ፍጹም ለሆነ መርገመ ኀጢአት ለሚወገድበት፥ የሥላሴ ልጅነት ለሚገኝበት ጥምቀት ሲናገር፦ «ንስሐ ግቡ፤ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና» ብሎ ነበረ (ማቴ. 3፥4)። ይህም ማለት መንግሥተ ሰማያት በልጅነት በሃይማኖት ልትሰጥ ቀርባለችና እያለ ያስተማረውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትምህርቱ መጀመሪያ አድርጎታል። በዮሐንስ አድሮ የተናገረ እርሱ ስለሆነ ነው። (ማቴ. 4፥17)

ቅዱሳን ሐዋርያትም በበዓለ ጰራቅሊጦስ ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ከአስተማሩ በኋላ ትምህርታቸውን የተቀበሉ ሕዝብ ምን እናድርግ ሲሏቸው፦ ንስሐ ግቡ ኀጢአታችሁ ይሰረይ ዘንድ ልጅነትን እንድታገኙ ከኀጢአት መርገም እንድትላቀቁ በኢየሱስ ክርስቶስ ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ ትቀበላላችሁ፤ የተስፋው ቃል ለእናንተና ለልጅ ልጆቻችሁ ጌታ አምላካችን ወደ እርሱ ለሚጠራቸው በሩቅ ላሉት ሁሉ ነውና (ግብ. ሐዋ. 2፥37-40)።

የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን በመባል በሚታወቀው በበዓለ ጰራቅሊጦስ ቅዱሳን አበው ሐዋርያት በረድኤተ መንፈስ ቅዱስ ሲያስተምሩ በዚያች ቀን ብቻ ሦስት ሺህ ሰዎች አምነው ተጠምቀው ልጅነት ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ተቀብለዋል።

ጥንታዊት ሐዋርያዊት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በትምህርተ ሐዋርያት የተመሠረተች በመሆኗ የምንጊዜም የዕለት ተዕለት ተልዕኮዋ ወንጌል ማስተማር በመዓርገ ክህነት ማጥመቅ፥ ማቍረብ ነው። ቅድስት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን አበው ሐዋርያት ትውፊትና ቀኖና፥ ሥርዐትና አስተምህሮ በመጠበቅ እስከ ሕልፈተ ዓለም ትኖራለች።

 

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሕረትና ይቅርታ በሁላችን ላይ ይሁን።

 

መጋቤ አእላፍ ኤፍሬም በየነ

የልሣነ ተዋሕዶ መጽሔት ዋና አዘጋጅ