መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

 

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜንፀ

• በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ዚምትገኙ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም ኢትዮጵውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!
እንደ ስሑትና ደካማ ሰብአዊ ባሕርያቜን ሳይሆን እንደ አባታዊ ቞ርነቱ ሁል ጊዜ በምሕሚቱ ዹሚጐበኘን አምላካቜን እግዚአብሔር እንኳን ለጟመ ኢዚሱስ አደሚሰንፀ አደሚሳቜሁ!
• “ንጹም ጟመ፣ ወናፍቅር ቢጞነ፣ እስመ ኹማሁ አዘዘነ፡- ጟምን እንጹም፣ ባልንጀራቜንንም እንውደድ፣ እንዲህ አዞናልና” (ቅዱስ ያሬድ)
እግዚአብሔር በዚህ ዓለም ስንኖር፣ እንድናደርገው ያዘዘን ዓቢይ ነገር ቢኖር ፍቅር ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍጥሚታትን ፈጥሮ እዚመገበ ዹሚገኘው በፍቅር ነው፡፡ እኛንም ኚፍዳ ኃጢአት ያዳነን በፍቅር ነው፡፡ ሕይወታቜንና ንብሚታቜን ተጠብቆ ዹሚኖሹው ፍቅር ሲኖር ነው፡፡
ግላዊና ማኅበራዊ ኑሮአቜን እንዲሁም ሃይማኖታዊ አምልኮአቜንና ዚተግባር እንቅስቃሎአቜን በሙሉ ውጀታማ ሊሆን ዚሚቜለው ፍቅር ሲኖር ነው፡፡
በፍቅር ውስጥ በሚኚት እንጂ ጉድለት ዚለምፀ በፍቅር ውስጥ ጀና እንጂ በሜታ ዚለምፀ በፍቅር ውስጥ ጜድቅ እንጂ ኃጢአት ዚለምፀ በፍቅር ውስጥ እግዚአብሔር እንጂ ዲያብሎስ ዚለም፡፡ ይህም በመሆኑ ቅዱስ መጾሐፍ ፍቅርን ‹‹ዚሁሉም ነገር ማሰሪያ ነቜ›› በማለት ይገልጻታል፡፡
ጌታቜን አምላካቜንና መድኃኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስም ኹሁሉም ዚምትበልጠው ታላቋ ትእዛዝ ‹‹ፍቅር›› እንደሆነቜ ኹመግለፁም በላይ ኊሪትና ነቢያት ሁሉ በእሷ እንደሚጠቃለሉ አስተምሮናል፡፡

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት!
ፍቅርን እንደ ዓይን ብሌን ስንጠብቃት በእጅጉ ዚምትጠቅመንን ያህል ጣል ጣል ስናደርጋት ደግሞ በእጅጉ ትጎዳናለቜ፡፡ በፍቅር እጊት ዹሚደርሰው ጉዳት በተወሰነ ነገር ብቻ ሳይሆን በነፍስም ሆነ በሥጋ፣ በምድርም ሆነ በሰማይ እጅግ በጣም ዹገዘፈና ዹሰፋ ነው፡፡ በሀገራቜን ዹሆነውና እዚሆነ ያለውም ይኾው ነው፡፡ ፍቅርን ባጣንባ቞ው ዓመታት ኚዚት ወዎት እንደደሚስን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዹሚገነዘበው ነው፡፡ ያተሚፍነው ነገርም ምን እንደሆነ ዹምናውቀው ነው፡፡  ይሁንና ዹፍቅር እጊት ምን ያህል እንደጎዳን ራሳቜን ተገንዝበን ወደ ሰላሙ መንገድ መመለሳቜን ዚተሻለ አማራጭ መሆኑን ሳንመሰክር አናልፍም፡፡ ዹተጀመሹው ዹፍቅርና ዹሰላም ጉዞም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ልባዊ ምኞታቜንና ጞሎታቜን ነው፡፡  ይህንን ሰላም እንዲመጣ ያደሚጉ ወገኖቜም ሁላቾውን ሳናመሰግን አናልፍም፡፡ ምክንያቱም በሰዎቜ መካኚል ፍቅርንና ሰላምን ዚሚያደርጉ ዚእግዚአብሔር ልጆቜ ይባላሉ ብሎ ጌታ እንደ አስተማሚን ብፅዕና ይገባ቞ዋልና ነው፡፡

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት!
ዚፍጹም ፍቅር መገኛ ዹሆነው ቅዱስ ወንጌል ዚሚያስተምሚው ፍቅር፣ ራስን ማፍቀር ወይም መውደድ ሳይሆን ራስን መጥላት ባልንጀራን ግን መውደድ ነው፡፡ ወንጌላዊ-ፍቅር ፍጹም ነው ዚሚያሰኘውም ቅሉ ይህ ነው፡፡ ለሁለት ሺሕ ዘመናት ያህል በቅዱስ ወንጌል አስተምህሮ ላይ ዚተገነባው ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ቅዱስ ባህልም ይህን ፍቅር ጠብቆ ዹሚጓዝ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ ዚኢትዮጵያ አበው መነኮሳት ኚነበራ቞ው ፍቅርና ትሕትና ዚተነሣ፣ ዚሹመት ሜሚያ አያውቁም ነበር፡፡ ኹዚህ አንጻር ትልቁን ሥልጣን ይቅርና ዚአንድ ገዳም መሪ ለመሆንም በእግር ብሚት ታስሚው በግድ ካልሆነ በቀር እሺ ብለው በፈቃደኝነት ሹመትን አይቀበሉም ነበር፡፡ ራሱን በራሱ መሟም ወይም እኔን ሹሙኝ ብሎ መናገርና ዹሌላን ድጋፍ መጠዹቅ ለኢትዮጵያውያን መነኮሳት ጭራሜ ነውርና ጞያፍም ነበር፡፡ ያም በመሆኑ ነው ኹዘመነ ብሉይ ጀምሮ ለሊስት ሺሕ ዘመናት ዹዘለቀው ሃይማኖታቜን ምንም ዓይነት መለያዚት ሳያጋጥመው አንድ ሆኖ ሊዘልቅ ዚቻለው፡፡ ይህ ዚቀተ ክርስቲያናቜን ጠንካራ አንድነት ለሕዝቡም በመትሚፉ ዚሀገሪቱን አንድነትና ነጻነት አስጠብቆ እስኚ ዘመናቜን ሊደርስ ቜሎአል፡፡ በዚህም ቀተ ክርስቲያናቜን ዚሕዝብንና ዹሀገርን አንድነትና ነጻነት ለማስጠበቅ ያደሚገቜውና ዚምታደርገው ጥሚት ሊያስመሰግናት እንጂ ሊያስወቅሳት አይገባም፡፡

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት!
ኚቅርብ ቀናት ወዲህ በቀተ ክርስቲያናቜን ተኚሥስቶ ዹነበሹውን ሕጋዊ ያልሆነ ድርጊት ዚቀተ ክርስቲያናቜንን ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና ባሕላዊ መርሕን ዚናደ፣ እንደዚሁም በኢትዮጵያ ይቅርና በዓለም ታሪክ ተደርጎ ዚማያውቅ ድርጊት እንደሆነ ቀተ ክርስቲያናቜን በአጜንዖት ስትገልጜ ቆይታለቜ፡፡ ይህንን ዚቀተ ክርስቲያን ድምፅ በመስማትና በመቀበል ሕዝበ ክርስቲያንና ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለእግዚአብሔር ባቀሚቡት ኃዘንና ጞሎት እንደዚሁም ባደሚጉት መጠነ ሰፊና ዙርያ መለስ ዹሆነ ዚድጋፍ ርብርብ ስሕተቱ ሊታሚም ቜሏል፡፡ ለተገኘው መንፈሳዊ ውጀትም ክቡር ጠቅላይ ሚንስትርና መንግሥታ቞ውን፣ ዚቀተ ክርስቲያን አንድነትና ሉዓላዊነት እንዲኚበር ኹፍተኛ መሥዋዕትነት ለኹፈለው መላው ሕዝበ ክርስቲያን እንዲሁም ይህ ስሕተት እንዲታሚም ኚቀተ ክርስቲያናቜን ጎን ተሰልፈው ድምፃ቞ውን ላሰሙ ኢትዮጵያውያንና ዹውጭ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በቀተ ክርስቲያናቜን ስም ኹፍ ያለ ምስጋና እናቀርብላ቞ዋለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ልጆቻቜን ግልፅ ማድሚግ ዹምንፈልገው ኚቀተ ክርስቲያናቜን ዶግማ፣ ቀኖና እና ሥርዓት መኹበር እንደዚሁም ኹሉዓላዊ አንድነቷ መጠበቅ በመለስ ያለው ጥያቄ ለማስናገድ ቀተ ክርስቲያናቜን ዝግጁ መሆኗን ነው፡፡ ቀተ ክርስቲያናቜን ሕዝቊቜ በቋንቋቾው ዚመማር፣ ዚማስተማርና ዹማምለክ እንዲሁም ዚመተዳደር መብትን ካሁን በፊትም፣ አሁንም፣ ካሁን በኋላም ዚምትነፍግበት መሠሚት እንደሌለም ሁሉም ሊያውቀው ይገባል፡፡ ይህም በመሆኑ በቋንቋ ዹመጠቀም መብት በሕገ ቀተ ክርስቲያናቜን ምዕራፍ 2 አንቀጜ 5 ኚቁጥር 1-3 ባለው አንቀጜ በሚገባ ተቀምጩ ይገኛል፡፡ ስለሆነም በቋንቋ ዹመጠቀም ጥያቄ በሕግ ደሹጃ ተመልሶ በተግባር እዚተሰራበት ዹሚገኝ መሆኑን ሁሉም ሊገነዘበው ይገባል፡፡

ዚተወዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናትፀ
ዛሬ ታላቁን ጟማቜን በፍቅር ሆነን ዚምንጟምበት ወቅት ነው፡፡ ሁላቜንም እንደምናውቀው ጟም ማለት ስጋዊ ፈቃድን በመግታት ኚእግዚአብሔር ጋር ጥብቅ ግንኙነት ለማድሚግ ዚሚካሄድ መንፈሳዊ ተጋድሎ ነው፡፡
በጌታቜን ጟም በተግባር እንዳዚነው ጟም ማለት ዲያብሎስ ዚሚሞነፍበት በአንጻሩ ደግሞ ዚእግዚአብሔር ሕዝብ አሞናፊዎቜ ዚሚሆኑበት ኃይል ነው፡፡
ስለሆነም ጟም ዚተጋድሎና ዚሙዓት ሜዳ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ዚምንታገለውም ልቡሰ ሥጋ ሰውን ሳይሆን ሹቂቅ ፍጡር ዹሆነው ሰይጣን በሰው አድሮ ዹሚነዛውን አጥፊ ሐሳቡንና ድርጊቱን ነው፡፡
ኹዚህም ጋር ሰውነታቜን ለዚህ ክፉ መንፈስ ታዛዥ እንዲሆን ዹሚገፋፉ ጥሉላት መባልዕትን መተውፀ ኃይለ ሥጋን መቈጣጠርፀ ኃይለ መንፈስን ደግሞ ማጎልበት ያስፈልጋል፡፡ በጟም ወቅት ዚተራቡትን ማጉሚስ ዚታሚዙትን ማልበስ ዚተበደሉትን መካስ፣ ፍትሕና ርትዕ በማኅበሹ ሰብ ውስጥ ማንገሥ ያስፈልጋል፡፡

በጟም ወቅት ኅሊናቜን ማሰላሰል ያለበት ሰው ምን አለ? ወይም ምን አደሹገ? በሚለው ሳይሆን እግዚአብሔር በፊቱ ምን ዓይነት ሰው እንድንሆንለት ይፈልጋል? በሚለው ላይ ነው፡፡
ስለዚህ ጟማቜን በዚህ መንፈስ ዹተቃኘ ፍቅሚ፣ እግዚአብሔርንና ፍቅሹ ቢጜን ማእኚል ያደሚገ፣ መጠራጠርንና አለመተመማንን ያስቀሚ፣ ዚተለያዩትን ያቀራሚበ፣ ዚተሳሳቱትን ያሚመ በአንጻሩ ደግሞ ሁላቜንን በሰላምና በፍቅር አንድ አድርጎ ያስተሳሰሚ ይሆን ዘንድ በዚህ መንፈስ ተነቃቅተን እንድንጟመው አባታዊ ጥሪያቜንን ለሕዝበ ክርስቲያኑ እናስተላልፋለን፡፡

በመጚሚሻምፀ
በሀገራቜን እዚታዚ ያለው ዹሰላም ጭላንጭልና ቜግሮቜን በውይይት ዚመፍታት ዝንባሌ በእጅጉ ጠቃሚና ለሁለንተና ልማታቜንና ለዕድገታቜን እንደዚሁም ለተሟላ አንድነታቜን ጠቃሚነቱ ዹጎላ ስለሆነ እግዚአብሔር ለዘለቄታው እንዲያሳካልን ኚልብ እንድናዝንና ወደ አምላካቜን በተመሥጊ እንድንጞልይ በአጜንዖት በማሳሰብ አባታዊ መልእክታቜንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
መልካም ዚጟም ወራት ያድርግልን!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቊቜዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስምወዕጚጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት
ዚካቲት ፲፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት አስተዳደር ጉባኀ በወቅታዊ ጉዳዮቜ ዙሪያ ተወያይቶ ልዩ ልዩ ውሳኔዎቜን አስተላለፈ ።


**********
ዚካቲት ፱ቀን ፳ ፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””””
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ

በብፁዕ ኚቡነ አብርሃም ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅና በባህር ዳር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዚሚመራው ዹጠቅላይ ቀተክህነት አስተዳደር ጉባዔ በወቅታዊ ዚቀተክርስቲያን ጉዳዮቜ ዙሪያ ዛሬ ዚካቲት ፱ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ባደሚገው መደበኛ ስብሰባ ልዩልዩ ውሳኔዎቜን አስተላለፈ።

ጉባኀው በቀተክርስቲያናቜን ዹተደሹሰውን ስምምነት አስመልኚቶ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ዹተሰጠውን ሰፊና ጥልቅ ማብራሪያ ካዳመጠ በኋላ በጉዳዩ ዙሪያ ሰፊ ውይይት በማድሚግ ዚሚኚተሉትን ውሳኔዎቜ አስተላልፏል።

፩ኛ በትላንትናው ዕለት በቅዱስ ሲኖዶስና ተወግዘው በተለዩት አባቶቜ መካኚል ዹተደሹሰውን ስምምነት በማድነቅ ተቀብሎታል። ለአፈጻጞሙም ዚሚጠበቅበትን ሁሉ ለማበሚሰኚት ቃል ገብቷል።

፪ኛ እርቀ ሰላሙ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ ኹፍተኛ አስተዋጜኊ ላበሚኚቱና ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያንን ወክለው ለተወያዩ ብፁዓን አባቶቜ፣ ተወግዘው ተለይተው ለነበሩ አባቶቜ ኹሁሉም በላይ ለቀተክርስቲያን አንድነት ቅድሚያ በመስጠት ለፈጞሙት ታሪካዊ ስምምነት አድናቆቱንና ምስጋናውን አቅርቧል።

፫ኛ ቅዱስ ሲኖዶስ፣ቅዱስ ፓትርያርኩ ፣ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና ብፁዕ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊው ዚቅድስት ቀተክርስቲያንን ሉአላዊ ክብርና ቀኖናዊ ሥርዓቱን ለማስጠበቅ ዚኚፈሉትን መስዋዕትነት በማድነቅ ስምምነቱ ዚቀተክርስቲያናቜንን መብት ባስኚበሚ መልኩኩ እንዲፈጞም በማድሚጋ቞ው ዹተሰማውን ልባዊ ደስታ ኚመግለጜ ጋር ስምምነቱን ተኚትሎ ለሚኹናወነው ተቋማዊ ዕድገት ዚበኩሉን አስተዋጜኊ ሁሉ በፍጺም ትጋት ለመፈጾም ዝግጁነቱን ገልጿል።።

፬ኛ ክቡር ዚኢፌዎሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አቢይ አህመድ ኹዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ሀገር ናት በማለት ዚሚገልጹትን ሀቅ በማጠናኹር እርቀ ሰላሙን ተኚትሎ “ሙሜራው ክርስቶስ እስኚሚመጣበት ድሚስ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን አንድነቷ ተጠብቆ ይኖራል።” በማለት እርቀ ሰላሙ ኚልብ እንዲኚናወን ያደሚጉትን ጥሚት በማድነቅ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልባዊ ምስጋናውን አቅርቧል።

፭ኛ ዚቀተክርስቲያን ቀኖና አይጣስም አንድነቷ አይናጋም በማለት ቅድስት ኊርቶዶክሳዊት ቀተክርስቲያንን ለማስኚበር ክቡር መስዋዕትነት ለኚፈላቜሁ ዹዘመኑ ሰማዕታት፣ለዕስርና ለእንግልት ዚተዳሚጋቜሁ ኊርቶዶክሳዊያን፣ለግርፋትና ለአካል ጉዳት ዚተዳሚጉ ልጆቻቜን ሁሉ ክብርና ምስጋና ይገባ቞ዋል ያለው ጉባኀው ለሰማዕታት መንግስተ ሰማያትን እንዲያወርስልን፣ዚአካልና ዚሥነ አእምሮ ጉዳት ለደሚሰባ቞ው ምሕሚትን ለልዑል እግዚአብሔር ይስጥልን ወዳጅ ዘዶቻ቞ውንም ያጜናናልን፣ዚታሰሩትንም ያስታልን በማለት ዚታሰሩ ዚቀተክርስቲያን ልጆቜን ለማስፈታት በሚደሹገው ጥሚት ዚሚጠበቅበትን ሁሉ ለማበርኚት ቃል ገብቷል።

፮ኛ በዚህ ፈታኝ ወቅት ዚቀተክርስቲያንን ሉዓላዊነትና ቀኖናዊ አንዎነትን ለማስኚበር በተደሹገው ተጋድሎ ኚቅድስት ቀተክርስቲያን ጎን በጜናት ዚቆማቜሁ በዹደሹጃው ዚምትገኙ ዹአህጉሹ ስብኚት ሥራ አስኪያጆቜና ዚጜሕፈት ቀት ሰራተኞቜ፣ዚቀተክርስቲያን አገልጋዮቜ፣ ማኅበራት፣ወጣት ልጆቻቜን ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዹመገናኛ ብዙሃን ድርጅት፣ዚቀተክርስቲያናቜን ዚሕዝብ ግንኙት መምሪያ፣ዚማኅበሚ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት በሚዲያው ዘርፍ ለተሰማሩሩ ልዩልዩ ዚሚዲያ ተቋማት አክቲቪስቶቜና ጞሐፊያን ሁሉ ቀተክርስቲያናቜን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለቜ።

፯ኛ ዚቀተክርስቲያናቜን ጉዳት ጉዳታቜን ነው ኚቀተክርስቲያናቜን ጎን በጜናት እንቆማለን ፀቜግሩን ዚቀተክርስቲያንን መብትና ጥቅም በሚያስኚብር መልኩ በሰላማዊ መንገድ እንፈታዋለን በማለት ሊገለጜ ዚማይቜል ተጋድሎና እልህ አስጚራሜ ፈተናዎቜን በጜናት አልፋቜሁ ይህን ዕርቀ ሰላም እውን ያደሚጋቜሁ ዚመፍትሔ አፈላላጊና ዚሜምግልና ሥራ ዚሰራቜሁ ባለሀብቶቜና አትሌቶቜ ልፋታቜሁ እንኳን ፍሬ አፍርቶ ለማዚት በቃቜሁ እንኳንም ደስ አላቜሁ። በማለት ልባዊ ምስጋናቜን እናቀርብላቜኋለን።

፰ኛ በዚህ ፈተና ጊዜ ቀተክርስቲያንን አናስደፍርም፣ ዚቀተክርስቲያንን ጥሪ ተቀብለን ቀተክርስቲያንን እናስኚብራለን በማለት ውድ ሕይወታ቞ውን በመስዋዕትነት ላቀሚቡ ሰማዕታት ቀተሰቊቜ፣ዚአካልና ዚሥነ አእምሮ ጉዳት ዚደሚሰባ቞ውን ወገኖቜን ለመደገፍና ዚቀተክርስቲያን ተቋማትን መልሶ ለመገንባት ዓለም አቀፍ ዚርዳታ አሰባሳቢ ኮሚ቎ በአስ቞ኳይ እንዲቋቋም ወስኗል።

፱ኛ ዹሚቋቋመው ዓለም አቀፍ ዚርዳታ አሰባሳቢ ኮሚ቎ በተቋም ደሹጃ በማዕኹላዊ ዚቀተክርስቲያናቜን አስተዳደር ዹሚቋቋም ብቻ እንዲሆን ይደሚጋል።ኚዚህ ውጪ በማኅበር፣በግልና በቡድን ዹሚቋቋም ዚርዳታ አሰባሳቢ ኮሚ቎ ፍጹም ተቀባይነት ዹሌለው መሆኑ ታውቆ ድጋፍ ማድሚግ ዹሚፈልጉ ወገኖቜ ሁሉ ዚቀተክርስቲያያቜን ማዕኹላዊ አስተዳደር
በሚያሳውቀው ሕጋዊ አካል ብቻ ድጋፍ እንዲያደርጉና መላው ኊርቶዶክሳዊያን ይህን ዹተቀደሰ ዓላማ ለማሳካት ርብርብ እንዲያደርጉ ጥሪ እያቀሚብን ለዚሁ ዓላማ ዹሚውል ዚባንክ ሒሳብ በአገር ውስጥና በውጪ ሀገራት ዚሚኚፈት ይሆናል።

፲ኛ በቀተክርስቲያናቜን ታሪክም ሆነ በዓለም አቀፍ ደሹጃ ይህን ዹመሰለ ፈተና ገጥሞ በማያውቅበት ጊዜ ኚቀተክርስቲያናቜን ጎን በመቆም ለቀኖናና ለአንድነታቜን መኹበር በጜናት ዚቆማቜሁ ዚእስልምናና ዚኘሮ቎ስታንት ዕምነት ተኚታይ ወንድሞቻቜን ሁሉ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ሀገር መሆኗን በተግባር በሚያሚጋግጥ ተጋድሎ በሀቅ ኚጎናቜን ስለቆማቜሁ ልባዊ ምስጋናቜንን በቅድስት ቀተክርስቲያናቜን ስም እናቀርብላቜኋለን።

፲ ፩ኛ በዚህ ፈታኝ ወቅት ጉዳት በደሚሰባ቞ው አካባቢዎቜ ዚስብኚተ ወንጌል ስምሪት ተደርጎ ተጎጂዎቜን ዚመጜናናት ፣ዚማስተማርና ዚመጎብኘት ሥራ በአስ቞ኳይ እንዲካሔድ ለዚሀህም አስፈላጊው ዚቅድመ ዝግጅት ሥራ እንዲኚናወን ወስኗል።

፲፪ኛ በዚህ ዚቀተክርስቲያንን መብትናጥቅም በማስኚበር ሒደት ውስጥ ዚመንግስትን ሥልጣን መኚታ በማድሚግ በህገ ወጥ መንገድ ግድያ ዚፈጞሙ፣ዚአካል ጉዳት ያደሚሱ፣ድብደባና ወኚባ ዹፈጾሙ አካላትን ለህግ ተጠያቂነት ማቅሚብ ለነገ ዚማይባል ተግባር በመሆኑ እነዚህን አካላት ለህግ ለማቅሚብ ዹሚደሹገውን ጥሚት በመደገፍ ምዕመናንና ምዕመናት እንዲሁም ወጣት ዚቀተክርስቲያያቜን ልጆቻቜን አስፈላጊውን ድጋፍ እንድተታደርጉ ጥሪአቜንን እያቀሚብን ዚቀተክርስቲያናቜን ዹሕግ አገልግሎት መምሪያና ጠበቆቻቜን ይህን ጉዳይ በልዩ ትኩሚት በመኚታተል ዹህግ ተጠያቂነትን ተግባራዊ እንዲያደርጉ ዚአስተዳደር ጉባኀው ዹወሰነ ሲሆን ውሳኔውም ለቋሚ ሲኖዶስ በመሾኛ እንዲላክ ብሏል።

፲፫ኛ ዹተጀመሹው ዹሰላም ሂደት ፍሬ አፍርቶ ተጚባጭ ውጀት እስኚሚገኝና ሁሉም ነገር ወደ ቊታው እስኚሚመለስ ድሚስ ኊርቶዶክሳዊያን ልቻቜን ሁሉ አስኚ ሁን ድሚስ ስተታደርጉት እንደቆያቜሁት ሁሉ ቀተክርስቲያናቜሁን በጜናት እንድትጠብቁ ጉባኀው አደራ ብሏል።

በመጚሚሻም ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጃቜን በዚህ ክፉ ወቅት በፍፁም ትጋት፣ብቃትን በተተተግባር ባመላኚተው ዚአመራር ቜሎታ቞ው በጥብአት ዚፈጞሙት ተጋድሎን ኚልብ ዹምናደንቅ ሲሆን ለቀጣይ ሥራ቞ው መሳካት ኚብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጃቜን ጎን በመቆም ሌት ተቀን ለመስራት ፍጹም ዝግጁ መሆናቜንን ስናሚጋግጥ በፍጹም ደስታና ትህትና መሆኑን እንገልጻለን በማለት ዚዕለቱን ስብሰባ በጞሎት አጠናቋል።

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያንና ተወግዘው በተለዩት አባቶቜ መካኚል በሜማግሌዎቜ አማካኝነት ዹተደሹገው ስምምነት ሰነድ።

ኹዚህ በሚት ያልሆኑ ሌሎቜ በጎቜ አሉኝ። እነርሱንም ማምጣት አለብኝ። እነርሱም ድምፄን ይሰማሉ። አንድ መንጋም ይሆናሉ። እሚኛውም አንድ ፀ ዚዮሐንስ ወንጌል 10፣ 16

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ በተክርስቲያን ተፈጥሮ ዹነበሹው ቜግር ብፁዓን አበው ዚቀተክርስቲያናቜንን ቀኖና መሠሚት አድርገው ባደሚጉት ውይይት ተፈታ።

ምሕሚትና እውነት ተገናኙ ጜቅድቅና ሰላም ተስማሙ – መዝ 855፣10

(ትግርኛ) ሰበር ዜና

. . . በዚ ሎሚ ዕለት ቅዱስ ሲኖዶስ ብዝሠዚሞ አቀራራቢን ናይ ይቅርታ ኮሚ቎ አማካኝነት ብቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ብዝኞፈቶ ናይ ይቅርታን ናይ ምሕሚትን አፍደገ መሠሚት፣ ናብ አደይ ቀተክርስቲያነይን ናይ መንፈስ ቅዱስ አቊታተይን ኚምኡ ውን ናብ ምእመናን ንይቅርታ ዝቀሚብኩ ስለዝኟነ ብመሠሚት ናይ ቋሚ ሲኖዶስን ምልዓተ ጉባኀን ውሳነ ነዚ ይቅርታይ ብአቊነት መንፈስ ንክቅበለኒ ብዓብይ ትሕትና ይሓትት።

ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ቅደስ ሲኖዶስ በቅድስት ቀተ ክርስቲያናቜን ወቅታዊ ጉዲይ ኚመንግሥት ጋር እዚተደሚገ ስላለውው ውይይት እና ዚካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በሀገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደሹጃ ሊደሹግ ስለታሰበው ሰላማዊ ሰልፍ አስመልክቶ ዹተሰጠ መግለጫ

ዚተኚበራቜሁ ውድ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜንፀ
ቅዱስ ሲኖዶስ በዚካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ዚጠራውን ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ ለተወሰኑ ጊዜ እንዲተላለፍ ያደሚገው ዹአቋም ለውጥ አድርጎ ሳይሆን አስቀድማ ቀተ ክርስቲያናቜን በሮቿን ለሰላም ክፍት በማድሚግ ባስተላለፈቜው ጥሪ እና በአስቀመጠቜው ቀነ ገደብ መሠሚት በመንግሥት በኩል ወዲያውኑ ቜግሩን ለመፍታት በመስማማቱና በመወሰኑ ምክንያት ብቻ መሆኑን ለመግለጜ እንወዳለን፡፡
ይህ ሂደት ትእግስት ዹሚጠይቅ በመሆኑ እስኚ አሁንም በፍጹም አንድነት እና መደማመጥ ዚቅዱስ ሲኖዶሱን ድምጜ እዚሰማቜሁ በአንድነት እና በሕብሚት እንደቆማቜሁት ሁሉ ወደፊትም ዚቅዱስ ሲኖዶስን ድምጜ በትጋት እንድትጠባበቁ እያሳሰብን በሕግ ዚተያዙት ጉዳዮቜም ዹሕግ ሂደታ቞ውን ተኚትለው ዚሚቀጥሉ መሆኑን እና እኛም በልዩ ሁኔታ ዚምናሳውቃቜሁ መሆኑን እንገልጻለን፡፡
መንግሥትም ዚቀተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብሎ ዚውይይት መድሚክ በማዘጋጀት ዚቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ በማክበር በውሳኔው መሠሚት ዹሚፈጾም መሆኑን ስላሚጋገጠልን ቅዱስ ሲኖዶስ ተግባራዊ ይሆናል ብሎ በማመን ተቀብሎታል፡፡
በተጚማሪም በዚህ ዹፈተና ወቅት በዹደሹጃው ዚምትገኙ በሀገር ውስጥ እና በመላው ዓለም ዚምትገኙ ዚቀተ ክርስቲያናቜን ዚሥራ ኃላፊዎቜፀ ሊቃውንተ ቀተ ክርስቲያንፀ መነኮሳትፀ አገልጋይ ካህናትፀ ዚሰንበት ትምህርት ቀት ወጣቶቜፀ ልዩ ልዩ ዚቀተ ክርስቲያናቜን መንፈሳዊ ማህበራት እና መላው ምእመናንና ምዕመናት እንዲሁም ኚቀተ ክርስቲያኗ ጎን ዚቆማቜሁ እና አጋርነታቜሁን ዚገለጻቜሁ ዚሃይማኖት ተቋማትፀ ዹሕግ ባለሙያዎቜፀ ግለሰቊቜፀ ዚማህበሚሰብ አንቂዎቜፀ ዚጥበብ ሰዎቜፀ ዚሰብዓዊ መብት ተቋማት እና በዚህ ሂደት ውስጥ ድጋፍ ስትሰጡ ዚነበራቜሁ ልዩ ልዩ አካላት ቀተ ክርስቲያን እያመሠገነቜ ወደፊትም ልዩ ዕውቅና ዚምትሰጥ መሆኑን እናሳውቃለን፡፡

ብፁዕ አቡነ ማ቎ዎስ በወቅታዊ ጉዳይ በጄኔቭ፣ ስዊትዘርላንድ ኹዓለም አብያተክርስቲያናት ምክር ቀት ጾሐፊ ቄስ ፕሮፌሰር ዶ/ር ጄሪ ፒሌ ጋር በወቅታዊ ዚቀተክርስቲያናቜን ጉደይ ውይይት አደሚጉ።

ብፁዕ አቡነ ማ቎ዎስ በወቅታዊ ጉዳይ በጄኔቭ፣ ስዊትዘርላንድ ኹዓለም አብያተክርስቲያናት ምክር ቀት ጾሐፊ ቄስ ፕሮፌሰር ዶ/ር ጄሪ ፒሌ ጋር በወቅታዊ ዚቀተክርስቲያናቜን ጉደይ ውይይት አደሚጉ።
++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++
ብፁዕ አቡነ ማ቎ዎስ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ዚቅዱስ ሲኖዶስ አባልና ዹመገናኛ ብዙኀን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት ዹበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ ጥር ፳፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም ጄኔቭ፣ ስዊትዘርላንድ በሚገኘው ዹዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቀት በመገኘት ኹዋና ጾሐፊው ቄስ ፕሮፌሰር ዶ/ር ጄሪ ፒሌ ጋር ውይይት አደሚጉ። ብፁዕነታ቞ው ዋና ጾሐፊው በቅርቡ ለዚህ ኹፍተኛ ሃላፊነት በመመሚጣቜው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት ስም ዚደስታ መልእክት አስተላልፈዋል። ቀተ ክርስቲያናቜን ዹምክር ቀቱ መስራቜና ንቁ አባል በመሆን ዚበኩልዋን ሚና እዚተወጣቜ መሆኑን አስታውሰው ይህ ግንኙነት ወደፊትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ያላ቞ውን ተስፋ ገልጞዋል።

ብፁዕነታ቞ው ቀተ ክርስቲያናቜን ዚገጠማትን ወቅታዊ ሁኔታ ያብራሩላ቞ው ሲሆን ዚቜግሩ ዋነኛ ምንጭ ዚቀተ ክርስቲያኒቱን ቀኖና እና ሕግጋት ዚጣሱ ጥቂት አፈንጋጭ አካላት ድርጊታ቞ው በቀተ ክርስቲያኒቱ ሕልውና ላይ ዚሚያስኚትለውን ታላቅ አደጋ በመገንዘብ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኀ ዹተወገዙና ዚተለዩ ቢሆንም መንግስት ዹሕግ ዚበላይነትንና ዚሕዝብን ሰላም ዹመጠበቅ ኃላፊነቱን ባለመወጣቱ በሕዝበ ክርስቲያኑ ላይ ኹፍተኛ ሃዘንና ጭንቀት ፈጥሯል። በዚህም ጳጳሳት እዚተሳደዱ፣ ካህናተ እዚታሰሩ፣ ምዕመናን እዚተደበደቡ ይገኛሉ። እንዲህም ሆኖ ሕግ ዚጣሱት አካላት በንስሐና በይቅርታ ቢመለሱ ቀተ ክርስቲያን በሯን ክፍት አድርጋ እዚጠበቀቜ ትገኛለቜ። ምክር ቀቱ ለቀተ ክርስቲያናቜን ተቋማዊ ልዕልና፣ ለሕግ ዚበላይነት፣ ለሰላምና ለፍትሕ አጋርነቱን እንዲገልጜ ብፁዕነታ቞ው ጠይቀዋል።

ዋና ጾሐፊው ለተደሚገላቜው ዝርዝር ማብራሪያ አመስግነው ይህቜ ጥንታዊትና ሐዋርያዊት ቀተ ክርስቲያን በወቅቱ ዚገጠማት ፈተና በእጅጉ አንደሚያሳስባ቞ውና ጉዳዩን በቅርበት መኚታተላ቞ውን እንደሚቀጥሉ ገልጞዋል። በመጚሚሻም በብጹዕነታ቞ው በኩል ለቅዱስ ፓትርያርካቜን ሰላምታና መልካም ምኞታ቞ውን ገልጞዋል። ኚብፁዕ አባታቜን ጋር መልአኹ ገነት ቆሞስ አባ ሃይለ ጊዮርጊስ በስዊትዘርላንድ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያን አስተዳዳሪና ዚጄኔቫ አጥቢያ ሰበካ ጉባኀ አመራር ተወካዮቜ በውይይቱ ተሳትፈዋል።

ውይይቱን ተኚትሎ ዋና ጾሀፊው በማግስቱ አጋርነታ቞ውን ዚሚያሳይ መግለጫ አውጥተዋል። በመግለጫ቞ው ምክር ቀቱ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን በዘመነ ሐዋርያት ዚተመሰሚተቜ፣ ሁልጊዜም ለአንድነትና ለሰላም ዹደም መስዋዕትነትም ጭምር ስትኚፍል ዚኖሚቜ ናት ብለዋል። አዲስ ሲኖዶስ ለመመስሚት በሚደሹገው ሙኚራ ማዘናቾውን አክለው ዚቀተ ክርስቲያኒቱ አንድነት እንዲጠበቅ በጞሎት እግዚአብሔርን ጠይቀዋል። ዚሚመለኚታ቞ው ዚፖለቲካ ሃይላት ሁሉ ሕጋዊ ሰውነት ያላት ቀተ ክርስቲያን ዚውስጥ ጉዳይዋን ባላት መንፈሳዊ ቀኖና እና ህግ ለመፍታት ብሎም ዹምዕመናኗን ሰላምና አንድነት ለማስጠበቅ ዚምታደርገውን ጥሚት እንዲደግፉ ጥሪ አቅርበዋል።

ዝርዝር መግለጫውን በዚህ ማስፈንጠሪያ ያንብቡ። https://www.oikoumene.org/news/wcc-expresses-solidarity-with-ethiopian-orthodox-tewahedo-church

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት፣ ዚሩስያን ፌዎሬሜን ዹፓርላማ አባል እና ዚሩስያ አምባሳደር በጜ/ቀታ቞ው ተቀብለው አነጋገሩ