ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ለትግራይ ክልል ዹ20 ሚሊዹን ብር ድጋፍ አደሚገቜ

(ኀፍ ቢ ሲ) ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ለትግራይ ክልል ዚ፳ ሚሊዹን ብር ድጋፍ አደሚገቜ፡፡በድጋፍ ርክክብ መርሐ ግብሩ ዚትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጌታ቞ው ሚዳ፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት እና ልዑካን ቡድኑ ተገኝተዋል፡፡

በቅዱስ ፓትርያርኩ ዚሚመራ ልዑካን ቡድን ወደ ክልል ትግራይ ርዕሰ ኹተማ መቐለ ተጓዘ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ለክልል ትግራይ ዚሰብዐዊ ድጋፍ እንዲደሚግና ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በትግራይ ክልል ኹሚገኙ አባቶቜ ጋር ውይይት እንዲደሚጉ ውሳኔ አስተላልፏል።

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ዚማኅበራት ምዝገባና ክትትል መምሪያ ቀጣዩን ዚሥራ አተገባበር አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ።

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያ ዚማኅበራት ምዝገባና ክትትል መምሪያ በጥቅምት ወር ፳፻፲፭ ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኀ ስብሰባ ዕውቅና ኚተሰጠበት ጊዜ ጀምሮ ዚውስጥ አሠራሩን ሲያመቻቜ ዹቆዹ መሆኑን ዹሕግ ባለሙያው አቶ አያሌው ቢታኒ ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግሚዋል።

ዹሕግ ባለሙያው አቶ አያሌው ቢታኒ ኹዚሁ ጋር አያይዘው እንዳብራሩት ዚማኅበራት ምዝገባና ክትትል መምሪያ ዚመተዳደሪያ ደንብና ዚአፈጻጞም መመሪያ ተዘጋጅቶለታል።
ለተመዝጋቢ ማኅበራትም ሞዮል ዹሚሆን ቅጜ ተዘጋጅቷል ያሉት ዹሕግ ባለሙያው ወደ ምዝገባ ዚሚገቡ ማኅበራት ዹጠቅላላ አባላቱ ቁጥር ሰባት መቶ ሀምሣ እና ኚዚያ በላይ ዹሆኑ ፣ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን እምነት ተኚታይ መሆናቾው በማስሚጃ ዚተሚጋገጠላ቞ው፣ዚንስሐ አባት ዚያዙ፣ በትምህርተ ሃይማኖት በቂ ዕውቀት ያላ቞ው ይሆናሉ ብለዋል።

አቶ አያሌው ቢታኒ በሰጡት ማብራሪያ አክለው እንደገለጹትም በማኅበራት ምዝገባና ክትትል መምሪያ ኚሚካተቱት ዚማኅበራት ዘርፎቜ ኚስምንት ያላነሱ ሲሆን ኚእነዚህም መካኚል ዚማኅበራት አንድነት፣ዚሙያ ማኅበራት፣ዚበጎ አድራጎት ማኅበራት፣ዚሐዋርያት ማኅበራት ፣መንፈሳዊ አስጎብኚ ማኅበራት ይገኙባ቞ዋል።

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚደቡብ ትግራይ ማይጹው እና ደቡብ ምሥራቅ ትግራይ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስና በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዚማኅበራት ምዝገባና ክትትል መምሪያ ዹበላይ ሐላፊ ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልእክት ዚማኅበራት ምዝገባና ክትትል መምሪያ ዋና ዓላማው ልዩ ልዩ ፈተና በበዛበት በዚህ ዘመን ምእመናን አንድነታ቞ውን እያጠናኚሩ ባንድ ላይ በመቆም ዋስትና቞ውን ለማሚጋገጥ እንዲሚዳ቞ው ታስቊ ሲሆን ቅድስት ቀተ ክርስቲያንንም ባንድ ላይ ሆነን ለማሻገር እንድንቜል ነው ብለዋል።

ቅድስት ሥላሎ መንፈሳዊ ዩኒቚርሲቲ በተለያዩ ዚትምህርት ክፍሎቜ ትምህርታ቞ውን ያጠናቀቁ ደቀመዛሙርትን አስመሚቀ

ቅድስት ሥላሎ መንፈሳዊ ዩኒቚርሲቲ በሥሩ ባሉ ዚተለያዩ ኮሌጆቜና በተለያዩ ዚትምህርት ክፍሎቜ በመደበኛ፣ በተኚታታይ፣ በርቀትና በልዩ ዚካህናት ሥልጠና ትምህርታ቞ውን ተኚታትለው ያጠናቀቁ ፫፻፞፮ ደቀመዛሙርትን በድኅሚ ምሚቃ፣ በመጀመሪያ ዲግሪ፣ በዲፕሎማና በሰርተፊኬት ማዕሹግ ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ (ዶ/ር) ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊ እና ዹኒው ዮርክና አካባቢው ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ መልኚጌዎቅ ዚጉራጌ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስና ዚዩኒቚርሲቲው ዚሥራ አመራር ቊርድ ሰብሳቢ፣ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ዚደቡብ ኩሞ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስና ዚቅድስት ሥላሎ ዩኒቚርሲቲ ፕሬዚደንት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳት፣ ክቡር ሊቀ አእላፍ በላይ መኮንን ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ እንዲሁም በክብር ጥሪ ዹተደሹገላቾው እንግዶቜና ዚተመራቂ ቀተሰቊቜ በተገኙበት በደማቅ ሥነ ሥርዓት አስመሚቀ።

ቅዱስ ፓትርያርኩ አልሟምም ወደ ትግራይም ፀ አልሔድም አላሉም

ሰኔ ፳፱ ቀን ፳፻ ፲ ወ፭ ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””””
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
******

በአንዳንድ ማኅበራዊ ሜዲያዎቜ ቅዱስ ፓትርያርኩ በቅዱስ ሲኖዶስ “ዚተመሚጡትን መነኮሳት አልሟምምፀ ወደ ትግራይም አልሔድም”ብለዋል ተብሎ ዹተሰርጭው ዜና ፍጹም ሐሰት ነው። ዚተመሚጡትን አባቶቜንም አልሟምም አላሉም። በተያዘው መርሐ ግብር መሠሚትም ወደ ትግራይ ይጓዛሉ።

እንዲህ ዓይነቱ ሆን ተብሎ ዚሚሰራጭ ዚሐሰት ዘገባ ፀ ዚእርቅ ሂደቱን ዹማደናቀፍ እና ዚቅዱስ ፓትርያርኩን ስም በሐስት ዚማጠልሜት ዹተለመደና ቀጣይ ዚሐሰተኞቜና ስም አጥፊዎቜ ዘመቻ አካል መሆኑን እዚገለጜን ይህን አይነቱን ዚሐሰትና ዚፈጠራ ወሬ በቅድስት እርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቀተክርስቲያናቜን ላይ ዹሚነዙ አካላትም ኹዚህ ደርጊታ቞ው እንዲታቀቡ ቅድስት ቀተክርስቲያን በጥብቅ ታሳስባለቜ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን
ዚሕዝብ ግንኙነት መምሪያ

አዲስ በሚሟሙት ኀጲስቆጶሳት ዚአመራሚጥ አካሄድ ዙሪያ በአስመራጭ ኮሚ቎ አባላት ብፁዓን አባቶቜ ማብራሪያ ተሰጠ።

ሰኔ ፳፱ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም አዲስ አበባ

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዚግንቊት ርክበ ካህናት ምልአተ ጉባዔ ለ፯ ዚኊሮሚያ እና ለ፪ ዚደቡብ ክልል አህጉሹ ስብኚት በኀጲስቆጶስነት ዚሚሟሙ ቆሞሳትን መልምለው ለምልአተ ጉባዔ እንዲያቀርቡ ዚተመሚጡት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ባኚናወኑት ዹምልመላ ሂደት ዙሪያ ኚጋዜጠኞቜ ለቀሹበላቾው ጥያቄዎቜ ማብራሪያ ተሰጥተዋል።

በተሰጠው ማብራሪያ መሠሚት በእጩነት ዚቀሚቡት ቆሞሳት በመንፈሳዊ ትምህርት፣ በአገልግሎት፣ በግብሚገብነትና ዚሚመደቡበትን ሀገሹ ስብኚት ምእመናን በቋንቋቾው በማስተማር ሚገድ በቂ ዝግጅት ያላ቞ው ስለመሆና቞ው ጥቆማውን ካቀሚቡት አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ኚቀሚቡት ተያያዥ ሠነዶቜና ዚሕይወት ታሪኮቜ መሚዳት መቻላ቞ውንና ይህንንም ለምልአተ ጉባኀ ማቅሚባ቞ውን በዚህም መሠሚት ድምጜ ተሰጥቶ ተሿሚዎቜ መለዚታ቞ውን አብራርተዋል። ምንም እንኳ ለምልአተ ጉባኀ ዚቀሚቡት ቆሞሳት ቁጥር ፲፰ ቢሆኑም ቀድሞ በጥቆማ ዚቀሚቡት አባቶቜ ቁጥር ፞፭ እንደነበሩ በኮሚ቎ው ጾሐፊ በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ተገልጿል።

ጥቆማው፣ ግምገማውና ምርጫው ምእመናንና ካህናት አልተሳተፉበትም በሚል ለቀሹበላቾው ጥያቄም:- ምንም እንኳ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዚብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ዚካህናት እና ዚምእመናን ዚጋራ ዚአገልግሎት ቊታ ዚሰማያዊት ኢዚሩሳሌም አምሳል ስለመሆኗ ሁሉም ዚሚያምነው እውነት እንደሆነ ሁሉ ቀተክርስቲያናቜን ኚራሷ ልጆቜ ሊቃነ ጳጳሳትን መሟም ኚጀመሚቜበት ጊዜ አንስቶ ዚምርጫ ሂደት ዚሚካሄደው በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ ብቻ በመሆኑ ዚዛሬውም ኚቀድሞ አሠራር ዹተለዹ አይደለም ቢሆንም ግን ዚካህናትንና ዚምእመናንን ይሁንታ ለማወቅ በተለያዩ መንገዶቜ ተጠቋሚዎቹ አባቶቜ ካገለገሉባ቞ው አህጉሹ ስብኚት እና አጥቢያዎቜ መሹጃ ጠይቀናል ኹዚህም ባሻገር ሊቃውንትንና ምእመናንን ለማሳተፍ ዚተሠራ ሥርዓት ሳይሠራ ወደማሳተፍ ቢገባ ቜግር ሊያመጣ ይቜላል ዹሚል ስጋት ስለመጣ በነበሹው ዚአመራሚጥ ልማድ ተኹናውኗል ሲሉ ምላሜ ሰጥተዋል።

ጥር ፲፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም ኹቀኖና ቀተክርስቲያን ውጪ ኚተሟሙ አባቶቜ መካኚል ዚተወሰኑት ለምን ተካተቱ በሚል ለተነሳው ጥያቄም ምላሜ ዚሰጡት አበው ሊቃነ ጳጳሳት አስቀድሞ ዚቀተክርስቲያናቜንን ሰላምና መዋቅራዊ አንድነት ለመጠበቅ በተደሹገው ዹሰላም ስምምነት መሠሚት ውግዘቱ ሲነሣ ፍጹም ሰላም ስለመፈጠሩ ቅዱስ ሲኖዶስ እምነት ስላደሚበት ለሲመቱ ብቁ መሆናቾው ዚታመነባ቞ው ለንስሐ ዹበቁ አባቶቜን መግፋት አስፈላጊ ባለመሆኑ ዚተወሰኑት አባቶቜ በእጩነት ቀርበው በቅዱስ ሲኖዶስ ዚታመነባ቞ው መመሚጣ቞ውን እንዲሁም ቀድሞ በቜግሩ ወቅት በነበሹው ዚቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ በተደሹገው ውይይት በጓዳ ለመግባት ዹተደሹገውን ሙኚራ አወገዘ እንጂ በተደሹገው ጥናት ያለእውቀት በተለያዚ ወቅታዊ ስብኚትና ጫና ተታለው ዚገቡ መኖራ቞ው በመሚጋገጡ ሊመሚጡ ቜለዋል ሲሉ ገልጞዋል።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ሲያካሂድ ዹነበሹውን አስ቞ኳይ ስብሰባ በማጠናቀቅ ዹተሰጠ መግለጫ

ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዹተሰጠ መግለጫ

በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ዚሚመራ ዚልዑካን ቡድን ሐምሌ ፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ወደትግራይ ርዕሰ ኹተማ መቐለ ይጓዛል።

ሰኔ ፳፰ቀን ፳፻ ፲ ወ፭ ዓ.ም
*****
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
******

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ ባስ ተላለፈው ውሳኔ መሰሚት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት ዚሚመራ ዚልዑካን ቡድን ሐምሌ ፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ .ም ወደ ክልል ትግራይ ርዕሰ ኹተማ መቐለ ይጓዛል።

ልዑካን ቡድኑ ወደ መቐለ ዹሚጓዘው በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኀ ውሳኔ መሰሚት ለትግራይ ክልል እንዲሰጥ ዹተወሰነውን ሰብአዊ ድጋፍ ለማድሚስና በትግራይ ኹሚገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በሰላም ጉዳዮቜ ዙሪያ ለመነጋገር መሆኑ ታውቋል።ይህንን በተመለኹተም ኹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ጜሕፈት ቀት ለትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ጜሕፈት ቀት ዹተላኹው ደብዳቀ ለፕሬዝዳንቱ ጜሕፈት ቀት ዛሬ ማለዳ እንዲደርስ ተደርጓል።