መስከረም ፬/፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት በመስቀልና ደመራ በዓል አከባበር ዙሪያ በመንበረ ጵጵስና በብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ክቡር መልአከ ኃይል አባ ተስፋዬ እማምሰው (ቆሞስ) የሀገረ ስብከቱ የልዩ ልዩ ክፍል የሥራ ኃላፊዎች የገዳማትና የአድባራት አስተዳዳሪዎች ጸሐፊዎችና ከሚመለከታች አካላት ጋር የመስቀልና የደመራ በዓል አከባበርንና አጠቃላይ የቤተክርቲያን መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳይ ላይ ሰፋ ያለ ውይይት ተደርጓል።

በውይይቱም ላይ ከአምናው በደመቀ ሁኔታ የዘንድሮውን የመስቀል ደመራን በዓል ለማክበር ተገቢውን ዝግጅት ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር መስራት እንደሚገባ ተመላክቷል በዓሉንም ምዕመናን በተለመደው ሰዓት ለበዓሉ ተስማሚ የሆኑ አልባሳትን ለብሰው እንዲገኙና ሃይማኖታዊ ግዴታቸውንም እንዲወጡ ማኅበረ ካህናቱም የሚጠበቅባቸው ድርሻ በንቃት እና በብቃት እንዲወጡ መመሪያ ተላልፏል።

በማጠቃለያውም ላይ ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ አዲሱን ዓመትና የመስቀል በዓል የፍቅር የበረከት የሰላምና የይቅርታ የመተሳሰብ እንዲሆን በመመኘት ቀጣይ አቅጣጫና የሥራ መመሪያ በማስቀመጥ በብፁዕነታቸው ቃለ ምዕዳን እና ቡራኬ ተሰጥቶ ተጠናቋል።

ዜናውን ያደረሰን የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ነው።