ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሽዋ፣ የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ኃላፊ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት !

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሽዋ፣ የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ኃላፊ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት !

ወትባርክ አክሊለ አመተ ምሕረትከ፤በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ (መዝሙር 65-11)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

የተከበራችሁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት ካህናት ዲያቆናት የመንፈስቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም መላው ኢትዮጵያውያን

እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወንጌላዊ ወደዘመነ ማቴዎስ ወንጌላዊ በሰላም እና በጤና አሸጋገራችሁ
እንኳን አደረሳችሁ

ቀን እና ሌሊትን
ሳምንታትን እና ወራትን
አመታትን እና አዝማናትን እያፈራረቀ በዕድሜያችን ላይ ዕድሜን ጨምሮ ለአዲሱ ዘመን ያደረሰን ከዘመናት በፊት የነበረ ዘመናትንም አሳልፎ የሚኖር ለህላዌው ዘመን የማይቆጠርለት ቸሩ አምላካችን መድኃኔዓለም ስለማይነገር ስጦታው እስከዘለዓለም የተመሰገነ ይሁን

የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያን
እግዚአብሔር ለፍጥረታት ልዩ ልዩ ጸጋዎችን አድሏል

እግዚአብሔር ለምድር እስከዚህ ድረስ ተብሎ ሊቆጠሩ የማይችሉ አዝማናትን ሲሰጣት ለሰው ልጆች ደግሞ በአዝማናት ውስጥ የሚቆጠሩ ዕድሜያትን ይሰጣል

በእግዚአብሔር ቸርነት ምድር ዘመንን ስትቀይር የምታገኛቸው ልዩ ልዩ ጸጋዎች አሏት
በሚቀየረው ዘመን ውስጥ የምድር ገጽታ ይለዋወጣል
የደረቀው መሬት በዝናም ይርሳል
በዝናም የራሰው መሬት ቡቃያን ይይዛል
ቡቃያው ያፈራል
ቀላያት ሞልተው ይፈሳሉ
ተራሮች በአረንጓዴ ይሞላሉ
ከጊዜ በኋላ የለመለመው ሁሉ ረግፎ ምድር ወደ ባዶነት ትቀየራለች

የሰው ልጆች ዑደትም ይህን ይመስላል
እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ዕድሜን ሲሰጥ
ሰዎች በተሰጣቸው ዕድሜ በኃጢአት የደረቀ ሕይወታቸውን በቅድስና እንዲያለመልሙ
በኃጢአት ያደፈ ማንነታቸውን በንስሓ እንዲቀድሱ
ከጥላቻ ሕይወት ወጥተው በፍቅር እንዲኖሩ
ከጦርነት ወደ ሰላም እንዲመለሱ
በአጠቃላይ ህገ እግዚአብሔርን ጠብቀው የእግዚአብሔርን መንግስት እንዲወርሱ ነው

እግዚአብሔር ዘመንና ዕድሜን ለሰው ልጆች ሲሰጥ ባለፉት ዘመናት የሰራናቸውን ክፉ ሥራዎች ይቅር ብሎ ከነዚያ ክፉ ሥራዎቻችን እንድንርቅ እና በንስሐ ወደ እርሱ እንመለስ ዘንድ ነው
ለዚሁም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በመጀመርያው መልእክቱ ምዕራፍ 4-3 ላይ
“የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል።”
ብሎ ባለፈው ዘመን ከኖርንበት የኃጢአት መንገድ እንድንመለስ ያስተምረናል

የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት
ዘመን አልፎ ዘመን ሲመጣ በደመና የጠቆረው ሰማይ ብርሃንን ይጎናጽፋል
ተራሮች ይለመልማሉ
ቆሻሻው በጎርፍ ታጥቦ ከምድር ይሠወራል
የደፈረሰው ውሀ ይጠራል
ምድር ፍሬን ትሰጣለች

የሰው ልጅ ግን ፊቱ በወንድሙ ላይ እንደጠቆረ ነው
ሰውነቱ በጽድቅ ከመለምለም ይልቅ በኃጢአት ደርቋል
ሰላምን ከመስበክ ይልቅ የጦርነት ዜና ማስተጋባትን መርጧል
ለወንድሙ መድኃኒት ከመሆን ይልቅ የወንድሙ ገዳይ ሆኗል

በእንደዚህ አይነት ሕይወት ውስጥ ሆኖ አዲስ ዘመንን መቀበል የእግዚአብሔርን ስጦታ ማቃለል ነው
ካለፈው መጥፎ ሕይወት ሳይመለሱ የዕድሜ ባለቤት መሆን በዕዳ ላይ ዕዳን መጨመር ነው

ስለዚህ ሁላችን ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያውያት ከሚያልፈው አሮጌ ዘመን ጋር አሮጌ አስተሳሰባችንን በመጣል አዲሱን ዘመን እግዚአብሔርን ደስ በሚያሰኝ መልካም አስተሳሰብ ልንቀበለው ይገባል

ይህን ካደረግን አምላካችን እግዚአብሔር ዘመናችንን ይባርክልናል
ምድራችን የሰላም ምድር ትሆናለች
በሰዎች መካከል ጥላቻ ጠፍቶ ፍቅር ይነግሳል
ከሁሉም በላይ በሚያልፈው ዘመንና በምታልፈው ምድር የምንሰራው መልካም ሥራ የማያልፈውን የእግዚአብሔር መንግሥት እንድንወርስ ይረዳናል

ዘመኑ የሰላም የፍቅር የአንድነት የዕርቅ የበረከት ዘመን ይሁንልን

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ
መልካም አዲስ ዓመት

አባ ሳዊሮስ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የደቡብ ምዕራብ ሽዋ የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ኃላፊ