አሥሩን ነጥቦች ያለመሸራረፍ ለመተግበር እነ አቡነ ሳዊሮስ ተስማሙ።ወቅታዊ መግለጫ

******
የካቲት ፲፩ቀን፳፻ ፲ወ፭ዓ.ም
“””””””””””””””””””””””””””
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
******

ጥር ፰ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አቢይ አህመድ በተገኙበት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሦስት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና እነ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በተገኙበት በተደረገው ውይይት ፲ የስምምነት ነጥቦች ተቀምጠው በነጥቦቹ ላይ የጋራ መግባባት ከተደረሰ በኋላ የጋራ መግለጫ በመስጠት ስምምነቱ መጽደቁ ይታወሳል።

ይህን ተከትሎም ስምምነቱን ሙሉ ለማድረግና ዕርቁን ተቋማዊ ለማድረግ በማሰብ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ እነ አቡነ ሳዊሮስን በመያዝ ወደ መንበረ ፓትርያርክ በማምጣት ከቅዱስነታቸው ጋር እንዲገናኙ ማድረጋቸው ይታወሳል።

ዛሬ የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን በመወከል በስምምነቱ ላይ የተሳተፉት ብፁዓን አባቶችና እነ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ ተገናኝተው ሰፊ ውይይት ካደረጉ በኋላ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት የተደረሰውን ስምምነት በምንም መልኩ መጣስ እንደሌለበት በመተማመን በዛሬው ዕለት መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫውም “በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት ክቡር ጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር አብይ አሕመድ በተገኙበት የካቲት ፰ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ/ም በተደረገው ውይይት የተስማማንባቸውን (፲) ዐሥር ነጥቦች ያለመሸራረፍ ለመፈጸም እንዲሁም ቀጣዩን ተግባር በተመለከተ በቅዱስ ሲኖዶስ አማካኝነት ለማከናወን ተስማምተናል። በማለት ይፋዊ መግለጫ ሰጥተዋል። ከመግለጫው በኋላም ወደ ማረፊያ ቤታቸው ገብተዋል።

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤትም የአባቶችን መመለስ ተከትሎ የጸጥታ ሥራው አስተማማኝ መሆን ይችል ዘንድ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በሕጋዊ መልኩ ጥበቃ ሊደረግለት እንደሚገባ በማመንና ጸጥታውን አስተማማኝ ለማድረግ እንዲሁም የጥበቃ ሥራውን ተቋማዊ በሆነ መልኩ የሚያከናውኑ የፌደራል ፓሊስ አባላት እንዲመደቡለት ያቀረበው ጥያቄ ተቀባይነት ስላገኘ ከፌደራል ፓሊስ ኮሚሽን የፓሊስ አባላት ተመድበው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን የጥበቃ ሥራ እያከናወኑ ይገኛሉ።

በአጠቃላይ በትላንትናው ዕለት የነበረው ሁኔታ ከፍ ሲል በተጠቀሰው አግባብ የተስተካከለ መሆኑን እየገለጽን የተጀመረው የሰላም ሂደት ግቡን ይመታ ዘንድ ምዕመናንና ምዕመናት በወርሃ ጾሙ ወደ ልዑል እግዚአብሔር አጥብቀው በመጸለይ እንዲተጉ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን ጥሪዋን ታስተላልፋለች።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ

በቀድሞ ስማቸው እነ አቡነ ሣዊሮስ ስምምነቱን ሳይሸራረፍ እንደሚቀበሉና ተግባራዊ እንደሚያደርጉ በቅዱስ ሲኖዶስ በመገኘት ቃላቸውን ሰጥተው አረጋግጠዋል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት ክቡር ጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር አብይ አሕመድ በተገኙበት የካቲት 8 ቀን 2015 ዓ/ም በተደረገው ውይይት የተስማማንባቸውን (10) ዐሥር ነጥቦች ያለመሸራረፍ ለመፈጸም እንዲሁም ቀጣዩን ተግባር በተመለከተ በቅዱስ ሲኖዶስ አማካኝነት ለማከናወን ተስማምተናል። የካቲት 11 ቀን 2015 ዓ/ም

በሸገር ሲቲ በፉሪ ክ/ከተማ04 ፓሊስ ጣቢያ ታስረው ከነበሩ እስረኞች መካከል ከአንድ መቶ በላይ የሚሆኑት መፈታታቸውን ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ዶ/ር ገለጹ።

*******
የካቲት 10 ቀን 2015ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
******
ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ዶ/ር በሸገር ሲቲ በ ፉሪ ከ/ከተማ 04 ፖሊስ ጣብያ የሚገኙ እስረኞችን ጠነቁ።ብፁነታቸው በፓሊስ ጣቢያው የሚገኙ ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በእስር ቤቱ በመገኘት ከጠየቁና ካጽናኑ በኋላ ከሚመለከታ ቸው የአቃቤ ሕግና የፖሊስ ጣቢያው ኋላፊዎች ጋር ውይይት አድርገዋል ። ከውይይቱ በኋላም ከአንድ መቶ ሃምሳ በላይ እስረኞች ተፈተዋል። ሲሉ ብፁዕነታቸው ገልጸውልናል።

ብፁዕነታቸው በጉብኝታቸው ወቅት ከአቃቤ ሕጉና ከፓሊስ ኃላፊዎች ለተደረገላቸው ግሩም የሆነ መስተንግዶና አቀባበል የተሰማቸውን ደስታ በመግለጽ ምስጋናቸውን በቅድስት ቤተክርስቲያን ስም አቅርበዋል።የቀሩትና በፓሊስ ጣቢያው ውስጥ የሚገኙ እስረኞችም በአጭር ቀናት ውስጥ እንደሚፈቱ ከአቃቤ ህጉና ከፓሊስ ኃላፊዎቹ ማረጋገጫ እንደተሰጣቸው ብፁዕነታቸው ጨምረው ገልጸዋል።

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

 

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፤

• በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም ኢትዮጵውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!
እንደ ስሑትና ደካማ ሰብአዊ ባሕርያችን ሳይሆን እንደ አባታዊ ቸርነቱ ሁል ጊዜ በምሕረቱ የሚጐበኘን አምላካችን እግዚአብሔር እንኳን ለጾመ ኢየሱስ አደረሰን፤ አደረሳችሁ!
• “ንጹም ጾመ፣ ወናፍቅር ቢጸነ፣ እስመ ከማሁ አዘዘነ፡- ጾምን እንጹም፣ ባልንጀራችንንም እንውደድ፣ እንዲህ አዞናልና” (ቅዱስ ያሬድ)
እግዚአብሔር በዚህ ዓለም ስንኖር፣ እንድናደርገው ያዘዘን ዓቢይ ነገር ቢኖር ፍቅር ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረታትን ፈጥሮ እየመገበ የሚገኘው በፍቅር ነው፡፡ እኛንም ከፍዳ ኃጢአት ያዳነን በፍቅር ነው፡፡ ሕይወታችንና ንብረታችን ተጠብቆ የሚኖረው ፍቅር ሲኖር ነው፡፡
ግላዊና ማኅበራዊ ኑሮአችን እንዲሁም ሃይማኖታዊ አምልኮአችንና የተግባር እንቅስቃሴአችን በሙሉ ውጤታማ ሊሆን የሚችለው ፍቅር ሲኖር ነው፡፡
በፍቅር ውስጥ በረከት እንጂ ጉድለት የለም፤ በፍቅር ውስጥ ጤና እንጂ በሽታ የለም፤ በፍቅር ውስጥ ጽድቅ እንጂ ኃጢአት የለም፤ በፍቅር ውስጥ እግዚአብሔር እንጂ ዲያብሎስ የለም፡፡ ይህም በመሆኑ ቅዱስ መጸሐፍ ፍቅርን ‹‹የሁሉም ነገር ማሰሪያ ነች›› በማለት ይገልጻታል፡፡
ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከሁሉም የምትበልጠው ታላቋ ትእዛዝ ‹‹ፍቅር›› እንደሆነች ከመግለፁም በላይ ኦሪትና ነቢያት ሁሉ በእሷ እንደሚጠቃለሉ አስተምሮናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
ፍቅርን እንደ ዓይን ብሌን ስንጠብቃት በእጅጉ የምትጠቅመንን ያህል ጣል ጣል ስናደርጋት ደግሞ በእጅጉ ትጎዳናለች፡፡ በፍቅር እጦት የሚደርሰው ጉዳት በተወሰነ ነገር ብቻ ሳይሆን በነፍስም ሆነ በሥጋ፣ በምድርም ሆነ በሰማይ እጅግ በጣም የገዘፈና የሰፋ ነው፡፡ በሀገራችን የሆነውና እየሆነ ያለውም ይኸው ነው፡፡ ፍቅርን ባጣንባቸው ዓመታት ከየት ወዴት እንደደረስን ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚገነዘበው ነው፡፡ ያተረፍነው ነገርም ምን እንደሆነ የምናውቀው ነው፡፡  ይሁንና የፍቅር እጦት ምን ያህል እንደጎዳን ራሳችን ተገንዝበን ወደ ሰላሙ መንገድ መመለሳችን የተሻለ አማራጭ መሆኑን ሳንመሰክር አናልፍም፡፡ የተጀመረው የፍቅርና የሰላም ጉዞም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ልባዊ ምኞታችንና ጸሎታችን ነው፡፡  ይህንን ሰላም እንዲመጣ ያደረጉ ወገኖችም ሁላቸውን ሳናመሰግን አናልፍም፡፡ ምክንያቱም በሰዎች መካከል ፍቅርንና ሰላምን የሚያደርጉ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉ ብሎ ጌታ እንደ አስተማረን ብፅዕና ይገባቸዋልና ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
የፍጹም ፍቅር መገኛ የሆነው ቅዱስ ወንጌል የሚያስተምረው ፍቅር፣ ራስን ማፍቀር ወይም መውደድ ሳይሆን ራስን መጥላት ባልንጀራን ግን መውደድ ነው፡፡ ወንጌላዊ-ፍቅር ፍጹም ነው የሚያሰኘውም ቅሉ ይህ ነው፡፡ ለሁለት ሺሕ ዘመናት ያህል በቅዱስ ወንጌል አስተምህሮ ላይ የተገነባው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ባህልም ይህን ፍቅር ጠብቆ የሚጓዝ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ የኢትዮጵያ አበው መነኮሳት ከነበራቸው ፍቅርና ትሕትና የተነሣ፣ የሹመት ሽሚያ አያውቁም ነበር፡፡ ከዚህ አንጻር ትልቁን ሥልጣን ይቅርና የአንድ ገዳም መሪ ለመሆንም በእግር ብረት ታስረው በግድ ካልሆነ በቀር እሺ ብለው በፈቃደኝነት ሹመትን አይቀበሉም ነበር፡፡ ራሱን በራሱ መሾም ወይም እኔን ሹሙኝ ብሎ መናገርና የሌላን ድጋፍ መጠየቅ ለኢትዮጵያውያን መነኮሳት ጭራሽ ነውርና ጸያፍም ነበር፡፡ ያም በመሆኑ ነው ከዘመነ ብሉይ ጀምሮ ለሦስት ሺሕ ዘመናት የዘለቀው ሃይማኖታችን ምንም ዓይነት መለያየት ሳያጋጥመው አንድ ሆኖ ሊዘልቅ የቻለው፡፡ ይህ የቤተ ክርስቲያናችን ጠንካራ አንድነት ለሕዝቡም በመትረፉ የሀገሪቱን አንድነትና ነጻነት አስጠብቆ እስከ ዘመናችን ሊደርስ ችሎአል፡፡ በዚህም ቤተ ክርስቲያናችን የሕዝብንና የሀገርን አንድነትና ነጻነት ለማስጠበቅ ያደረገችውና የምታደርገው ጥረት ሊያስመሰግናት እንጂ ሊያስወቅሳት አይገባም፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
ከቅርብ ቀናት ወዲህ በቤተ ክርስቲያናችን ተከሥስቶ የነበረውን ሕጋዊ ያልሆነ ድርጊት የቤተ ክርስቲያናችንን ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና ባሕላዊ መርሕን የናደ፣ እንደዚሁም በኢትዮጵያ ይቅርና በዓለም ታሪክ ተደርጎ የማያውቅ ድርጊት እንደሆነ ቤተ ክርስቲያናችን በአጽንዖት ስትገልጽ ቆይታለች፡፡ ይህንን የቤተ ክርስቲያን ድምፅ በመስማትና በመቀበል ሕዝበ ክርስቲያንና ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለእግዚአብሔር ባቀረቡት ኃዘንና ጸሎት እንደዚሁም ባደረጉት መጠነ ሰፊና ዙርያ መለስ የሆነ የድጋፍ ርብርብ ስሕተቱ ሊታረም ችሏል፡፡ ለተገኘው መንፈሳዊ ውጤትም ክቡር ጠቅላይ ሚንስትርና መንግሥታቸውን፣ የቤተ ክርስቲያን አንድነትና ሉዓላዊነት እንዲከበር ከፍተኛ መሥዋዕትነት ለከፈለው መላው ሕዝበ ክርስቲያን እንዲሁም ይህ ስሕተት እንዲታረም ከቤተ ክርስቲያናችን ጎን ተሰልፈው ድምፃቸውን ላሰሙ ኢትዮጵያውያንና የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በቤተ ክርስቲያናችን ስም ከፍ ያለ ምስጋና እናቀርብላቸዋለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን ግልፅ ማድረግ የምንፈልገው ከቤተ ክርስቲያናችን ዶግማ፣ ቀኖና እና ሥርዓት መከበር እንደዚሁም ከሉዓላዊ አንድነቷ መጠበቅ በመለስ ያለው ጥያቄ ለማስናገድ ቤተ ክርስቲያናችን ዝግጁ መሆኗን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ሕዝቦች በቋንቋቸው የመማር፣ የማስተማርና የማምለክ እንዲሁም የመተዳደር መብትን ካሁን በፊትም፣ አሁንም፣ ካሁን በኋላም የምትነፍግበት መሠረት እንደሌለም ሁሉም ሊያውቀው ይገባል፡፡ ይህም በመሆኑ በቋንቋ የመጠቀም መብት በሕገ ቤተ ክርስቲያናችን ምዕራፍ 2 አንቀጽ 5 ከቁጥር 1-3 ባለው አንቀጽ በሚገባ ተቀምጦ ይገኛል፡፡ ስለሆነም በቋንቋ የመጠቀም ጥያቄ በሕግ ደረጃ ተመልሶ በተግባር እየተሰራበት የሚገኝ መሆኑን ሁሉም ሊገነዘበው ይገባል፡፡

የተወዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤
ዛሬ ታላቁን ጾማችን በፍቅር ሆነን የምንጾምበት ወቅት ነው፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው ጾም ማለት ስጋዊ ፈቃድን በመግታት ከእግዚአብሔር ጋር ጥብቅ ግንኙነት ለማድረግ የሚካሄድ መንፈሳዊ ተጋድሎ ነው፡፡
በጌታችን ጾም በተግባር እንዳየነው ጾም ማለት ዲያብሎስ የሚሸነፍበት በአንጻሩ ደግሞ የእግዚአብሔር ሕዝብ አሸናፊዎች የሚሆኑበት ኃይል ነው፡፡
ስለሆነም ጾም የተጋድሎና የሙዓት ሜዳ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የምንታገለውም ልቡሰ ሥጋ ሰውን ሳይሆን ረቂቅ ፍጡር የሆነው ሰይጣን በሰው አድሮ የሚነዛውን አጥፊ ሐሳቡንና ድርጊቱን ነው፡፡
ከዚህም ጋር ሰውነታችን ለዚህ ክፉ መንፈስ ታዛዥ እንዲሆን የሚገፋፉ ጥሉላት መባልዕትን መተው፤ ኃይለ ሥጋን መቈጣጠር፤ ኃይለ መንፈስን ደግሞ ማጎልበት ያስፈልጋል፡፡ በጾም ወቅት የተራቡትን ማጉረስ የታረዙትን ማልበስ የተበደሉትን መካስ፣ ፍትሕና ርትዕ በማኅበረ ሰብ ውስጥ ማንገሥ ያስፈልጋል፡፡

በጾም ወቅት ኅሊናችን ማሰላሰል ያለበት ሰው ምን አለ? ወይም ምን አደረገ? በሚለው ሳይሆን እግዚአብሔር በፊቱ ምን ዓይነት ሰው እንድንሆንለት ይፈልጋል? በሚለው ላይ ነው፡፡
ስለዚህ ጾማችን በዚህ መንፈስ የተቃኘ ፍቅረ፣ እግዚአብሔርንና ፍቅረ ቢጽን ማእከል ያደረገ፣ መጠራጠርንና አለመተመማንን ያስቀረ፣ የተለያዩትን ያቀራረበ፣ የተሳሳቱትን ያረመ በአንጻሩ ደግሞ ሁላችንን በሰላምና በፍቅር አንድ አድርጎ ያስተሳሰረ ይሆን ዘንድ በዚህ መንፈስ ተነቃቅተን እንድንጾመው አባታዊ ጥሪያችንን ለሕዝበ ክርስቲያኑ እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም፤
በሀገራችን እየታየ ያለው የሰላም ጭላንጭልና ችግሮችን በውይይት የመፍታት ዝንባሌ በእጅጉ ጠቃሚና ለሁለንተና ልማታችንና ለዕድገታችን እንደዚሁም ለተሟላ አንድነታችን ጠቃሚነቱ የጎላ ስለሆነ እግዚአብሔር ለዘለቄታው እንዲያሳካልን ከልብ እንድናዝንና ወደ አምላካችን በተመሥጦ እንድንጸልይ በአጽንዖት በማሳሰብ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
መልካም የጾም ወራት ያድርግልን!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስምወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
የካቲት ፲፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት አስተዳደር ጉባኤ በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይቶ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን አስተላለፈ ።


**********
የካቲት ፱ቀን ፳ ፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
“”””””””””””””””””””””””””
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ

በብፁዕ ከቡነ አብርሃም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅና በባህር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሚመራው የጠቅላይ ቤተክህነት አስተዳደር ጉባዔ በወቅታዊ የቤተክርስቲያን ጉዳዮች ዙሪያ ዛሬ የካቲት ፱ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ባደረገው መደበኛ ስብሰባ ልዩልዩ ውሳኔዎችን አስተላለፈ።

ጉባኤው በቤተክርስቲያናችን የተደረሰውን ስምምነት አስመልከቶ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ የተሰጠውን ሰፊና ጥልቅ ማብራሪያ ካዳመጠ በኋላ በጉዳዩ ዙሪያ ሰፊ ውይይት በማድረግ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አስተላልፏል።

፩ኛ በትላንትናው ዕለት በቅዱስ ሲኖዶስና ተወግዘው በተለዩት አባቶች መካከል የተደረሰውን ስምምነት በማድነቅ ተቀብሎታል። ለአፈጻጸሙም የሚጠበቅበትን ሁሉ ለማበረሰከት ቃል ገብቷል።

፪ኛ እርቀ ሰላሙ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ወክለው ለተወያዩ ብፁዓን አባቶች፣ ተወግዘው ተለይተው ለነበሩ አባቶች ከሁሉም በላይ ለቤተክርስቲያን አንድነት ቅድሚያ በመስጠት ለፈጸሙት ታሪካዊ ስምምነት አድናቆቱንና ምስጋናውን አቅርቧል።

፫ኛ ቅዱስ ሲኖዶስ፣ቅዱስ ፓትርያርኩ ፣ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የቅድስት ቤተክርስቲያንን ሉአላዊ ክብርና ቀኖናዊ ሥርዓቱን ለማስጠበቅ የከፈሉትን መስዋዕትነት በማድነቅ ስምምነቱ የቤተክርስቲያናችንን መብት ባስከበረ መልኩኩ እንዲፈጸም በማድረጋቸው የተሰማውን ልባዊ ደስታ ከመግለጽ ጋር ስምምነቱን ተከትሎ ለሚከናወነው ተቋማዊ ዕድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ ሁሉ በፍጺም ትጋት ለመፈጸም ዝግጁነቱን ገልጿል።።

፬ኛ ክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አቢይ አህመድ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሀገር ናት በማለት የሚገልጹትን ሀቅ በማጠናከር እርቀ ሰላሙን ተከትሎ “ሙሽራው ክርስቶስ እስከሚመጣበት ድረስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አንድነቷ ተጠብቆ ይኖራል።” በማለት እርቀ ሰላሙ ከልብ እንዲከናወን ያደረጉትን ጥረት በማድነቅ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልባዊ ምስጋናውን አቅርቧል።

፭ኛ የቤተክርስቲያን ቀኖና አይጣስም አንድነቷ አይናጋም በማለት ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንን ለማስከበር ክቡር መስዋዕትነት ለከፈላችሁ የዘመኑ ሰማዕታት፣ለዕስርና ለእንግልት የተዳረጋችሁ ኦርቶዶክሳዊያን፣ለግርፋትና ለአካል ጉዳት የተዳረጉ ልጆቻችን ሁሉ ክብርና ምስጋና ይገባቸዋል ያለው ጉባኤው ለሰማዕታት መንግስተ ሰማያትን እንዲያወርስልን፣የአካልና የሥነ አእምሮ ጉዳት ለደረሰባቸው ምሕረትን ለልዑል እግዚአብሔር ይስጥልን ወዳጅ ዘዶቻቸውንም ያጽናናልን፣የታሰሩትንም ያስታልን በማለት የታሰሩ የቤተክርስቲያን ልጆችን ለማስፈታት በሚደረገው ጥረት የሚጠበቅበትን ሁሉ ለማበርከት ቃል ገብቷል።

፮ኛ በዚህ ፈታኝ ወቅት የቤተክርስቲያንን ሉዓላዊነትና ቀኖናዊ አንዴነትን ለማስከበር በተደረገው ተጋድሎ ከቅድስት ቤተክርስቲያን ጎን በጽናት የቆማችሁ በየደረጃው የምትገኙ የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና የጽሕፈት ቤት ሰራተኞች፣የቤተክርስቲያን አገልጋዮች፣ ማኅበራት፣ወጣት ልጆቻችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የመገናኛ ብዙሃን ድርጅት፣የቤተክርስቲያናችን የሕዝብ ግንኙት መምሪያ፣የማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት በሚዲያው ዘርፍ ለተሰማሩሩ ልዩልዩ የሚዲያ ተቋማት አክቲቪስቶችና ጸሐፊያን ሁሉ ቤተክርስቲያናችን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለች።

፯ኛ የቤተክርስቲያናችን ጉዳት ጉዳታችን ነው ከቤተክርስቲያናችን ጎን በጽናት እንቆማለን ፤ችግሩን የቤተክርስቲያንን መብትና ጥቅም በሚያስከብር መልኩ በሰላማዊ መንገድ እንፈታዋለን በማለት ሊገለጽ የማይችል ተጋድሎና እልህ አስጨራሽ ፈተናዎችን በጽናት አልፋችሁ ይህን ዕርቀ ሰላም እውን ያደረጋችሁ የመፍትሔ አፈላላጊና የሽምግልና ሥራ የሰራችሁ ባለሀብቶችና አትሌቶች ልፋታችሁ እንኳን ፍሬ አፍርቶ ለማየት በቃችሁ እንኳንም ደስ አላችሁ። በማለት ልባዊ ምስጋናችን እናቀርብላችኋለን።

፰ኛ በዚህ ፈተና ጊዜ ቤተክርስቲያንን አናስደፍርም፣ የቤተክርስቲያንን ጥሪ ተቀብለን ቤተክርስቲያንን እናስከብራለን በማለት ውድ ሕይወታቸውን በመስዋዕትነት ላቀረቡ ሰማዕታት ቤተሰቦች፣የአካልና የሥነ አእምሮ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖችን ለመደገፍና የቤተክርስቲያን ተቋማትን መልሶ ለመገንባት ዓለም አቀፍ የርዳታ አሰባሳቢ ኮሚቴ በአስቸኳይ እንዲቋቋም ወስኗል።

፱ኛ የሚቋቋመው ዓለም አቀፍ የርዳታ አሰባሳቢ ኮሚቴ በተቋም ደረጃ በማዕከላዊ የቤተክርስቲያናችን አስተዳደር የሚቋቋም ብቻ እንዲሆን ይደረጋል።ከዚህ ውጪ በማኅበር፣በግልና በቡድን የሚቋቋም የርዳታ አሰባሳቢ ኮሚቴ ፍጹም ተቀባይነት የሌለው መሆኑ ታውቆ ድጋፍ ማድረግ የሚፈልጉ ወገኖች ሁሉ የቤተክርስቲያያችን ማዕከላዊ አስተዳደር
በሚያሳውቀው ሕጋዊ አካል ብቻ ድጋፍ እንዲያደርጉና መላው ኦርቶዶክሳዊያን ይህን የተቀደሰ ዓላማ ለማሳካት ርብርብ እንዲያደርጉ ጥሪ እያቀረብን ለዚሁ ዓላማ የሚውል የባንክ ሒሳብ በአገር ውስጥና በውጪ ሀገራት የሚከፈት ይሆናል።

፲ኛ በቤተክርስቲያናችን ታሪክም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ይህን የመሰለ ፈተና ገጥሞ በማያውቅበት ጊዜ ከቤተክርስቲያናችን ጎን በመቆም ለቀኖናና ለአንድነታችን መከበር በጽናት የቆማችሁ የእስልምናና የኘሮቴስታንት ዕምነት ተከታይ ወንድሞቻችን ሁሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሀገር መሆኗን በተግባር በሚያረጋግጥ ተጋድሎ በሀቅ ከጎናችን ስለቆማችሁ ልባዊ ምስጋናችንን በቅድስት ቤተክርስቲያናችን ስም እናቀርብላችኋለን።

፲ ፩ኛ በዚህ ፈታኝ ወቅት ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች የስብከተ ወንጌል ስምሪት ተደርጎ ተጎጂዎችን የመጽናናት ፣የማስተማርና የመጎብኘት ሥራ በአስቸኳይ እንዲካሔድ ለዚሀህም አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ እንዲከናወን ወስኗል።

፲፪ኛ በዚህ የቤተክርስቲያንን መብትናጥቅም በማስከበር ሒደት ውስጥ የመንግስትን ሥልጣን መከታ በማድረግ በህገ ወጥ መንገድ ግድያ የፈጸሙ፣የአካል ጉዳት ያደረሱ፣ድብደባና ወከባ የፈጸሙ አካላትን ለህግ ተጠያቂነት ማቅረብ ለነገ የማይባል ተግባር በመሆኑ እነዚህን አካላት ለህግ ለማቅረብ የሚደረገውን ጥረት በመደገፍ ምዕመናንና ምዕመናት እንዲሁም ወጣት የቤተክርስቲያያችን ልጆቻችን አስፈላጊውን ድጋፍ እንድተታደርጉ ጥሪአችንን እያቀረብን የቤተክርስቲያናችን የሕግ አገልግሎት መምሪያና ጠበቆቻችን ይህን ጉዳይ በልዩ ትኩረት በመከታተል የህግ ተጠያቂነትን ተግባራዊ እንዲያደርጉ የአስተዳደር ጉባኤው የወሰነ ሲሆን ውሳኔውም ለቋሚ ሲኖዶስ በመሸኛ እንዲላክ ብሏል።

፲፫ኛ የተጀመረው የሰላም ሂደት ፍሬ አፍርቶ ተጨባጭ ውጤት እስከሚገኝና ሁሉም ነገር ወደ ቦታው እስከሚመለስ ድረስ ኦርቶዶክሳዊያን ልቻችን ሁሉ አስከ ሁን ድረስ ስተታደርጉት እንደቆያችሁት ሁሉ ቤተክርስቲያናችሁን በጽናት እንድትጠብቁ ጉባኤው አደራ ብሏል።

በመጨረሻም ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጃችን በዚህ ክፉ ወቅት በፍፁም ትጋት፣ብቃትን በተተተግባር ባመላከተው የአመራር ችሎታቸው በጥብአት የፈጸሙት ተጋድሎን ከልብ የምናደንቅ ሲሆን ለቀጣይ ሥራቸው መሳካት ከብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጃችን ጎን በመቆም ሌት ተቀን ለመስራት ፍጹም ዝግጁ መሆናችንን ስናረጋግጥ በፍጹም ደስታና ትህትና መሆኑን እንገልጻለን በማለት የዕለቱን ስብሰባ በጸሎት አጠናቋል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንና ተወግዘው በተለዩት አባቶች መካከል በሽማግሌዎች አማካኝነት የተደረገው ስምምነት ሰነድ።

ከዚህ በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ። እነርሱንም ማምጣት አለብኝ። እነርሱም ድምፄን ይሰማሉ። አንድ መንጋም ይሆናሉ። እረኛውም አንድ ፤ የዮሐንስ ወንጌል 10፣ 16

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በተክርስቲያን ተፈጥሮ የነበረው ችግር ብፁዓን አበው የቤተክርስቲያናችንን ቀኖና መሠረት አድርገው ባደረጉት ውይይት ተፈታ።

ምሕረትና እውነት ተገናኙ ጽቅድቅና ሰላም ተስማሙ – መዝ 855፣10

Odduu Ammee

Warreen Seera Alaan Muudam Ephis Qophoosummaa “muudaman” jedhaman Keessaa tokko kan turan Abbaa Niwaye Sillaasee Akliiluu
Mana Kiristaanaafi Qulqulluu Sinoodoosii dhiifama gaafachuun Deebi’anii jiru.

Breaking News

Aba NewayeSelassie Aklilu, one of the the monks who are said ordinated by the law breaker group returned back to his mother Church.

(ትግርኛ) ሰበር ዜና

. . . በዚ ሎሚ ዕለት ቅዱስ ሲኖዶስ ብዝሠየሞ አቀራራቢን ናይ ይቅርታ ኮሚቴ አማካኝነት ብቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ብዝኸፈቶ ናይ ይቅርታን ናይ ምሕረትን አፍደገ መሠረት፣ ናብ አደይ ቤተክርስቲያነይን ናይ መንፈስ ቅዱስ አቦታተይን ከምኡ ውን ናብ ምእመናን ንይቅርታ ዝቀረብኩ ስለዝኾነ ብመሠረት ናይ ቋሚ ሲኖዶስን ምልዓተ ጉባኤን ውሳነ ነዚ ይቅርታይ ብአቦነት መንፈስ ንክቅበለኒ ብዓብይ ትሕትና ይሓትት።