ዚብፁዕ አቡነ ሰላማ ክቡር አስኚሚን ኚሀሌሉያ ሆስፒታል ወደ መንበሹ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ተጓዘ።

በሀሌሉያ ሆስፒታል ሕክምናቾውን ሲኚታተሉ ዚነበሩት ብፁዕ አቡነ ሰላማ በትላንትናው እለት ኹዚህዓለም ድካም ማሹፋቾውን ተኚትሎ በዛሬው እለት ክቡር አስኚሬና቞ው ወደበመንበሹ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ጾልተ ፍትሐት ሲደሚግበት እንዲያድር እና በነገው እለት ቅዳሎ ኹተቀደሰ በኋላ አስፈላጊው ሥርዓት ኚተፈጞመለት በኋላ ሥርዓተ ቀብሩ እንዲፈጞም ወደ መንበሹ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ተጉዟል።

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት ዚብፁዕ አቡነ ሰላማ ዚታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም እና ዹመንበሹ መንግሥት ቅዱስ ገብርኀል ገዳም ዹበላይ ጠባቂ ሊቀጳጳስ ዕሚፍትን በማስመልኚት ያስተላለፉት አባታዊ ዹሐዘን መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

«መኑ ሰብእ ዘዚሐዩ ወኢይሬእያ ለሞት: ሕያው ሆኖ ዹሚኖር ሞትንስ ዚማያይ ማን ነው?»
መዝሙር ፹፱፥፵፰

ዚትህትና፣ ዚጞሎት ሕይወት እና ዚመልካምነት ምሳሌ ዚነበሩት ብፁዕ አባ ሰላማ ሊቀ ጳጳስ ኹዚህ ዓለም ድካም ማሹፋቾውን ዹሰማነው በታላቅ ሐዘን ነው።

ያለንበትን ፈተና ዚበዛበት ዘመን በጞሎት ዚሚያሻግሩ አባቶቜን ማጣት ቀተ ክርስቲያንን ዚሚጎዳ ቢሆንም በቅዱስ መጜሐፍ ሞትን ሳያይ ሕያው ሆኖ መኖር ዚሚቜል ማን ነው? እንደተባለ ሰው በምድር ላይ ዚሚኖርበት ዘመን በእግዚአብሔር ዘንድ ዹተቆጠሹ እና ዚተለካ በመሆኑ ብፁዕነታ቞ው ሃይማኖትን ጠብቀውና መልካሙን ገድል ፈጜመው ወደ መንግሥተ እግዚአብሔር በክብር ተሞጋግሚዋል።

ብፁዕነታ቞ው በዕሹፍተ ሥጋ ኚእኛ በመለዚታ቞ው ጥልቅ ሐዘን ቢሰማንም በሰማይ ዚሚጠብቃ቞ውን ክብር እያሰብን እንጜናናለን።

ዚብፁዕነታ቞ውን ነፍስ በቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት አጠገብ ያሳርፍልን!
ለቅድስት ቀተ ክርስቲያን እና ለመንፈስ ቅዱስ ልጆቻ቞ውም መጜናናትን ያድልልን!
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቊቿን ይባርክ ይቀድስ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
አሜን!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም
ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት
መስኚሚም 18 ቀን 2016 ዓመተ ምሕሚት
ዋሜንግተን ዲሲ አሜሪካ

ዚብፁዕ አቡነ ሰላማ አጭር ዚሕይወት ታሪክ

ዜና ህይወቱ ለብፁዕ አቡነ ሰላማ (ዚብፁዕ አቡነ ሰላማ አጭር ዚሕይወት ታሪክ)

ብፁዕ አቡነ ሰላማ ኚአባታ቞ው ኚአቶ ገብሚ ሥላሎ ገ/መድኀንና ኚእናታ቞ው ኹወ/ሮ ብዙነሜ ወንድሙ በትግራይ ክፍለ ሀገር በመቀሌ ኹተማ ልዩ ስሙ በዓታ ለማርያም በተባለው ፲፱ፎ፬ ዓ/ም ተወለዱ።

ዕድሜያ቞ው ለትምህርት ሲደርስ በትውልድ ሀገራ቞ው ንባብና ዹቃል ትምህርት በሚገባ ዚተማሩ ሲሆን ለግብሚ ዲቁና ዚሚገባውንም ትምህርት ኚዚኔታ ክነፈ
ርግብ ተምሹዋል ፀ ዲቁና ኚብፁዕ አቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል።
ብፁዕነታ቞ው ለቀተክርስቲያንና ለመንፈሳዊ ዕውቀት ባላ቞ው ጥልቅ ፍቅር በተለያዩ አካባቢዎቜ በመዘዋወር ዚተለያዩ መንፈሳዊ ትምህርቶቜን ዚተማሩ ሲሆን

ዜማ፡- ኚዚኔታ ተክለ ማርቆስ ማዹ አንበሳ ገዳም (ተንቀን)
– ቅኔ፡- ኚዚኔታ ንጉሀ መነዌ ገዳም (ተንቀን)

– ቅኔ፡- ኚዚኔታ አክሊሉ ደበጋ (ጐንደር)
• ትርጓሜ መጻሕፍት- ኚዚኔታ ኃ/ማርያም ቀሹፃ ማርያም ኚምትሀባል ገዳም
ቅኔና ትርጓሜ መጻሕፍት፡- እንድባ ጊዮርጊስ ኚዚኔታ ልሳነ ወርቅ (ጐጃም)
● ቅኔ፡- ኚዚኔታ ዲበኩሉ (ጐጃም) በሚገባ ኚተማሩ በኋላ ለመምህር ነት በቅተዋል፡፡
ኹዚህ በኋላ በጐጃም ክ/ሀገር በፈሚስ ቀት ሚካኀል፣ በጅጋ ሚካ ኀል ወንበር ዘርግተው ለ፲፪ ዓመታት ቅኔ በማስተማር አያሌ ደቀ መዛሙርትን አፍርተዋል፡

መዝገበ ቅዳሎ ኚዚኔታ ልዑል (ቊሚራ ሚካኀል) ተምሚዋልፀ በወ ቅቱ ዹጐጃም ሊቀ ጳጳስ ኚነበሩት ኚብፁዕ አሱነ ማርቆስ ዚቅስናና ዚምንኵስና መዐርግ ተቀብለዋል።

ብፁዕ አቡነ ሰላማ በ ፲፱፻፷፬ ዓ.ም ወደ አርሲ ክፍለ ሀገር በመሄድ በወቅቱ ዹሀ/ስብኚቱ ሊቀ ጳጳስ በነበሩት በብፁዕ አቡነ ሉቃስ መልካም ፈቃድ በሀገሹ ስብኚቱ በማስተማር፣ ዚአውራጃ ሰባኬ ወንጌል በመሆን፣ ዚወሚዳ ሊቀ ካህናት በመ ሆን በተለያዩ ዚኃላፊነት ሥራዎቜ ተመድበው በመሥራት ሰፊ አገልግሎት አበርክተዋልፀ በርካታ ደቀ መዛሙርትንም አፍርተዋልፀ በዚሁ ሀገሹ ስብኚት ለ፳፪ ዓመታት በማስተማር ቆይተዋልፀ በዚህም ሰፊ ወቅት ብዙ ደቀ መዛሙርትን አውጥተው ለቀተ ክርስቲያን አበርክተዋል፡፡

ብፁዕነታ቞ው ኚአርሲ ሀገሹ ስብኚት በ፲፱፻፹፮ ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ኚመጡ በኋላ ውቅያኖስ በሆነው እውቀታ቞ውና በቅድስና቞ው ቀተ ክርስቲያንንም ሆነ ምእመናንን እንደሚጠቅሙ በማሰብ ኚዚያን ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት በቅዱሳን ፓትርያርኮቜ ፈቃድና ትእዛዝ እዚተሟሙፊ-
⇹ በቡራዩ ፄዎንያ ማርያም፣
⇹ በመተሐራ መድኃኔ ዓለም፣
-በቃሊቲ ቅዱስ ገብርኀልና ሳሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣
⇹ በሰዓሊተ ምሕሚት፣
⇹ በደብሚ አሚን ተክለ ሃይማኖት በአስተዳዳሪነት ተመድበው ለበር ካታ ዓመታት በማስተማር በሚያስመንነው ስብኚታ቞ው ብዙ አማ ንያንን አበርክተዋልፀ ለምናኔም አብቅተዋልፀ በተሰጣ቞ው ሀብተ ፈውስ በጞሎታ቞ው አያሌ ሕሙማንን ፈውሰዋል፧ ሰበካ ጉባኀን አጠናክሚዋልº ስብኚተ ወንጌልን አስፋፍተዋል፧ በተለይም በመንበሹ ጞባኊት ቅድስት ሥላሎ ካ቎ድራል ሊቀ ሥልጣናት ሆነው ለ ዓመታት ያህል በአስተዳደሩበት ጊዜ ኹፈጾሟቾው ተግባራት ዋና ዋናዎቹ ምእመናን በጣዕመ ስብኚታ቞ውና በቅድስና቞ው እዚተማሚኩ ለካ቎ድራሉ በሚያደርጉት ዚቊታና ዚገንዘብ ልግስና በርካታ ዹሆኑ ዚልማት ተግባራትን አኚናውነዋል።

❖ በዚህም መሠሚት በትምህርታ቞ው በጎ አድራጊዎቜንና ምእመናንን በማስተባበር በካ቎ድራሉ ስም ዹሁለተኛ ደሹጃ ት/ቀትና ኹፍተኛ ክሊኒክ አሠርተው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ሊቀ ጳጳስ አክ ሱም፣ ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት ተባርኮ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡

⇹ በመንበሹ ጞባኊት ቅድስት ሥላሎ ካ቎ድራል ለ፭ ዓመታት ካገለገሉ በኋላ በእን ጩጩ ሐመሚ ኖኅ ኪዳነ ምሕሚት ገዳም በአስተዳዳሪነት አገልግለዋል።

⇹ ብፁዕ አቡነ ሰላማ ሙሉ ዚቀተ ክርስቲያን ትምህርታ቞ውን አጠናቅቀው በቀተ ክርስቲያን አገልግሎት ኚተመደቡበት ጊዜ ጀምሮ ኚቊታ ወደ ቊታ በመዘዋወር በአብነት መምህርነታ቞ው በተለይም በቅኔ መምህርነታ቞ው በተለያዩ አህጉሹ ስብኚት ወንበር ዘርግተው በማስተማር እስኚ ጵጵስና ደሹጃ ዚደሚሱ አያሌ ምሁራንን አፍርተው ለቀተ ክርስቲያን ያስሚኚቡ፣ በልዩ ዚስብኚት ቜሎታ቞ው ዚታወቁ ሰባክያነ ወንጌልን ያፈሩና አማንያንን ያበዙ፣ ቅድስናን ኚሙያ ጋር አስተባብሚው ዚያዙ፣ ዚቅዱሳኑ፣ ዚፍጹማኑ ሚድኀት ያልተለያ቞ው፣ እንደ አባቶቻ቞ው ቅዱሳን ሐዋር ያት አጋንንትን ዚማስወጣትና ሌላውንም ደዌ ሁሉ ዚመፈወስ ሀብተ ፈውስ ዚተሰጣ቞ው፣ በጥላ቞ው ብቻ ሕሙማንን ዹሚፈ ውሱ፣ ዹበቁ (ፍጹም) አባት ነበሩ።

ብፁዕ አቡነ ሰላማ ኚፈጣሪያ቞ው ዚተሰጣ቞ው ተውህቩ ዹተወሰነ አይደለም ሀብተ ጾጋቾው ብዙ ነው! ጣዕመ ስብኚታ቞ው ካለ መጠገቡም በላይ በተመስጊ በአካለ ሥጋ ያሳርጋልI ቅኔያ቞ውም ልዩ ጣዕም አለው ኹማር ኚወተት ይጣ ፍጣል! ፈጣሪያ቞ውን ብቻ አይደ ለም ዚሚያኚብሩት፣ ሲበዛ ሰው አክባሪ ና቞ው‥ ምንም ይሁን ምን በአርአያ እግዚአብሔር ዹተፈጠሹውን ትልቁንም ትንሹንም ሁሉ በአክብሮት ዚሚወዱ አባት ነበሩ።

በአጠቃላይ ብፁዕ አቡነ ሰላማ ዚቀተ ክርስቲያናቜን ጾጋና በሚኚት ነበሩ።በዚህ ቅድስና ቞ው፣ በቀተ ክርስቲያን ትምህርት ሙሉ ቜሎታ቞ው፣ በአብነት መምህርነታ቞ው በርካታ ምሁራንን በማፍራታ቞ውና ለቅድስት ቀተ ክርስቲያና቞ው ባበሚኚቱት ሰፊ ዹሆነ መንፈሳዊ አገልግሎታ቞ው ተመዝነው ብቁና ፍጹም አባት ሆነው በመገኘታ቞ው ሐምሌ ፱ ቀን ፲፱፻፺፯ ዓ.ም በተደሹገው ዚጳጳሳት ምርጫ ኚሌሎቜ ዕጩ ቆሞሳት ጋር ተወዳድሚው ዚድምፅ ብልጫ ስለ አገኙ ዚአክሱምና ማዕኹላዊ ዞን ሃገሹ ስብኚት ኀጲስ ቆጶስ ሆነው ዚተመደቡ ሲሆን ኚታኅሣሥ ፱/ ፪ሺ፪ ዓ/ም ጀምሮ ዹሰሜን ምዕራብ ሜሬ እንዳሥላሎ ሀገሹ ስብኚትን ደርበው እዚሰሩ እስኚ ግንቊት ፳፰/፪ሺ፭ ዓ/ም ድሚስ ሐዋርያዊ ተግባራ቞ውን ሲፈጜሙ ቆይተዋል።

ግንቊት ፳፰ /፪ሺ፭ ዓ/ም ኚትግራይ ማዕኹላዊ ዞን አክሱም ሀገሹ ስብኚት ወደ አዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ተዛውሹው ዚታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም እና ዹመንበሹ መንግሥት ቅዱስ ገብርኀል ገዳም ዹበላይ ኃላፊ ሆነው ሲያገለግሉ ቆይተው በ ፪ሺ፮ ዓ/ም ዚምሥራቅ ሐሹርጌ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በመሆን ለ፮ ዓመታት በምሥራቅ ሐሹርጌ ሀገሹ ስብኚት ኹፍተኛ ሐዋርያዊ አገልግሎትን ፈጜመዋል።

ብፁዕ አቡነ ሰላማ ኚህዳር ፳፻ ፲፪ዓ/ም ጀምሮ በድጋሚ ዚታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም እና ዹመንበሹ መንግሥት ቅዱስ ገብርኀል ገዳም ዹበላይ ኃላፊ ሆነው በበአታ቞ው በመወሰን ሲያገለግሉ ቆይተው ባደሚባ቞ው ሕመም በህክምና ሲሚዱ ቆይተው መስኚሚም ፲፰ቀን፳፻ ፲ወ፮ ዓ/ም ይህን ዓለም በዕሹፍተ ሥጋ ተለይተው ወደ ሰማያዊው አባታ቞ው ተጉዘዋል።

በሚኚታ቞ው ይደርብን

ዚብፁዕነታ቞ው በሚኚት ይደርብን

ዜና እሚፍት – ብፁዕ አቡነ ሰላማ ኹዚህ ዓለም ድካም አሚፉ።

መስኚሚም ፲፰ቀን፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም
*****
ብፁዕ አቡነ ሰላማ ኹዚህ ዓለም ድካም አሚፉ።
*********

ጞሎተኛው፣ደጉ፣ርህሩሁና ታጋሹ አሹጋዊው አባት ብፁዕ አቡነ ሰላማ ዛሬ መስኚሚም ፲፰ቀን ፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም ኹዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል።ብፁዕ አባታቜን ባደሚባ቞ው ህመም ምክንያት በአዲስ አበባ ሀሌሉያ ሆስፒታል በህክምና ላይ እንዳሉ ነው ኹዚህ ዓለም ድካም ያሚፉት።ዚብፁዕነታ቞ውን ሜኝት መርሐ ግብር በተመለኹተ በቋሚ ሲኖዶስ እንደተወሰነ ዝርዝሩን ዚምናሳውቅ ይሆናል።

ዚብፁዕነታ቞ው በሚኚት ይደርብን

ዚ፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም ዚመስቀል ደመራ በዓል በድምቀት ተኚብሮ በመዋሉ ቅድስ ቀተክርስቲያን ምስጋናዋን ታቀርባለቜ።

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን በዚዓመቱ በታላቅ መንፈሳዊ ሥነሥርዓት ተኚብሮ ዹሚውለው ዚመስቀል ደመራ በዓል ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን በጠበቀ መልኩ ተኚብሮ መዋል ይቻል ዘንድ ፲፫ ንዑሳን ኮሚ቎ዎቜን በማደራጀት ስኬታማ ዚቅድመ ዝግጅት ሥራዎቜን ስታኚናውን መሰንበቷ ይታወሳል።

ዚ፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም ዚመስቀል ደመራ በዓል በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት በመኹበር ላይ ነው።

ዚ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም ዚመስቀል ደመራ በዓል በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት በመኹበር ላይ ነው።በበዓሉ ሊይ ብፁዕ አቡነ አብርሃም ዹጠቅላይ ቀተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና ዚባህር ዳር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ ዶ/ር ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚኒዩወርክ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ክቡር ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን ዹጠቅላይ ቀተክህነት ም/ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ዚጠቅላይ ቀተክህነት መምሪያ ኃላፊዎቜ፣ ኹፍተኛ ዚመንግሥት ባለሥልጣናት፣ዚኚተማቜን አስተዳደር ኚንቲባ አዳነቜ አቀቀ፣አምባሳደሮቜ ፣ጥሪ ዹተደሹገላቾው እንግዶቜ፣ካህናት፣ምዕመናንና ምዕመናት ተገኝተዋል።

ዚመስቀል ደመራ በዓል ዚአኚባበር ሥነ ሥርዓት ዝግጅት ተጠናቀቀ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ኚምታኚብራ቞ው ዚአደባባይ በዓላት መካኚል አንዱና በዓለም አቀፉ ዚትምህርት ሳይንስና ባህል ጅርጅት በማይዳሰስ ቅርስነት ዹተመዘገበው ዚመስቀል ደመራ በዓል በነገው ዕለት በመስቀል አደባባይ በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ይኚበራል ።

ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅና ብፁዕ ዶክተር ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊ ዹ2016 ዓ.ም ዚመስቀል ደመራ በዓል አስመልክቶ ዚሊቃውንት ወሚብ ጥናት ልምምድን ጎበኙ።

በአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ሥር ኹሚገኙ ገዳማትና አድባራት ዚተውጣጡ ብዛታ቞ው 800 ዚሚደርሱ ሊቃውንተ ቀተ ክርስቲያን በ2016 ዓ.ም ዹሚኹበሹውን ዚመስቀል ደመራ በዓል በተለዹ ድምቀት ለማክበር ኹነሐሮ 24 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ በጠቅላይ ቀተ ክህነትና በመንበሹ ፀባዖት ቅድስት ሥላሎ ካ቎ድራል ግቢ በዓሉን ዹተመለኹተ ዚወሚብ ጥናት ሲያደርጉ ዚቆዩ ሲሆን መስኚሚም 14 ቀን 2016 ዓ/ም በተደሹገው ዚወሚብ ጥናት መርሐ ግብር ወቅት ብፁዕ አቡነ አብርሃም ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና ዚባህር ዳር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ (ዶ/ር) ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊ እና ዚኒውዮርክና አካባቢው ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተው ለሠልጣኞቹ ዚማበሚታቻ ሐሳብና ቡራኬ ሰጥተዋል።

ዓለም በሚቀማበት ወቅት ጊዜውን፣እውቀቱን፣ገንዘቡን ለቀተ ክርስቲያን ዚሚሰጥ እንደእናንተ አይነት ልጆቜ ስላሉን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን

ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚኒዮርክና አካባቢው ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በማኅበሹ ቅዱሳን ዹ2016 ዓ.ም ዹ6 ወራት ዚሥራ አመራር ጠቅላላ ጉባኀ ማጠቃለያ ላይ ተገኝተው ቡራኬና ቃለ ምእዳን ሰጥተዋል።

ብፁዕ አቡነ አብርሃም ዹጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ዚባህር ዳር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በመስቀል አደባባይ ዹሚኹበሹውን ዚደመራ በዓልን አስመልክቶ መልእክት አስተላለፉ።

መስኚሚም ፲፪ ቀን ፳፻፲ወ፮ ዓም
*****
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“”””””””””””””””””””
ብፁዕነታ቞ው በመግቢያ቞ው ስለ ትግስት አስፈላጊነት እና ጠቀሜታ ትምህርት ዚሰጡ ሲሆን በበዓሉ ላይ ዚሚፈትኑ ጉዳዮቜ ሊገጥሙን ስለሚቜሉ በትዕግስት ማለፍ አለብን ብለዋለል። በማስኚተልም ዚዕለቱን መርሐ ግብር ያስተዋወቁ ሲሆን በይበልጥም ሰዓትን ማክበር ኹፍተኛ ትኩሚት እንደሚሰጠው አሳስበዋል። ብፁዕነታ቞ው ዚመግቢያ ባጅ እደላው በሕግና በሥርዓት ትኩሚት ተሰጥቶት ዹሚኹናወን መሆኑን ገልጞዋል።

ሰንደቅ ዓላማን በተመለኹተም ዚፌዎራል እና ዚቀተ ክርስቲያን አርማ ብቻ ይለበት መሆን እንደሚገባውና ርቜት መተኮስ ዚቀተ ክርስቲያን ሥርዐት ባለመሆኑ እንደማይፈቀድ ገልጞዋል። ዚቲሞርት አለባበስ በተመለኹተም ተንኳሜ መልእክት መጠቀም አይገባም ያሉት ብፁዕነታ቞ው በዚመንደሩና በዚአጥቢያው በሚኚበሩ በዓላት ላይም ጥንቃቄ ያስፈልጋል ብለዋል።
በበዓሉ ላይ ዚተፈቀደለት አስተናባሪ ብቻ ዚሚያስተናግድ ሲሆን ያልተፈቀደለት አካል ሲንቀሳቀስ ቢገኝ በወንጀል ያስጠይቃል ያሉት ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ መርሐ ግብር መሪዎቜ እና ተናጋሪዎቜ በተፈቀደላቾው ሰዓት እንዲጠቀሙ አሳስበዋል።።
በመጚሚሻም ለመርሐ ግብሩ መሳካት ሁሉም ዚበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ አባታዊ ጥሪ አስተላልፈዋል። በዕለቱ ዚሙስሊም ወገኖቻቜን ዚሚያኚብሩት በዓል ስላላ቞ው በመኚባበር እና በመተባበር በዓላቱን ማክበር ይገባል ሲሉም ጹምሹው አሳስበዋል።
እንደዚሁፊብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ ዶ/ር ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚኒውዮርክ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በዓሉን አስመልክተው መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን ብፁዕነታ቞ው በበኩላ቞ው በዓሉ መንፈሳዊ ስለሆን በመንፈሳዊነት ልናኚብሚው ይገባል እንደዚሁም በታዛዥነት እና በእምነት በበዓሉ ላይ ልንታደም ይገባል ብለዋል።