ምሥራቅ ሐሹርጌ ሀገሹ ስብኚት ጜ/ቀት በእስር ላይ ለሚገኙ ዹሕግ ታራሚዎቜ ለአዲሱ ዓመት ፳፻፲፯ ዓ.ም መዋያ ዹሚሆን ዚበሬ ሥጊታ አበሚኚተ።

ጳጉሜን ፭ ፳፻፲፯ ዓ/ም

“ካለፈው ዓመት ስህተት ወደ አዲሱ ዓመት እንዳይሞጋገር ማድሚግ እና ለሁለንተናዊ ለውጥ ራስን ማዘጋጀት ይኖርብናል”። ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ሊቀ ጳጳስ

“ካለፈው ዓመት ስህተት ወደ አዲሱ ዓመት እንዳይሞጋገር ማድሚግ እና ለሁለንተናዊ ለውጥ ራስን ማዘጋጀት ይኖርብናል”።
ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ሊቀ ጳጳስ

ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ዚአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ” ዚዘመናት ባለቀት እግዚአ ሰማያት ወምድር ጌታቜን መድኃኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ እንኳን ለ 2017 ዘመነ ማ቎ዎስ ዚምሕሚት ዓመት በሰላምና በጀና አደሹሰን አደሚሳቜሁ” በማለት ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልእክት አስተላልፈዋል።

በመልእክታ቞ውም:-
” አዲስ ዓመትፀ ዚዓመታት፣ ዚወራት፣ዚሳምንታት እና ዚቀናት ለውጥና መፈራሚቅ ብቻ ሳይሆን ካለፈው ዓመት ስህተት ወደ አዲሱ ዓመት እንዳይሞጋገር ማድሚግ እና ለሁለንተናዊ ለውጥ ራስን ማዘጋጀት እንዲሁም ዚለውጥን ሂደት ለመጀመር ቁርጠኛ መሆንን ይጚምራል።

ለዚህም ነው መጜሐፍ ቅዱስ ቅን ልቡና፣ ቅን ሕሊና እሰጣቜኃለሁ በማለት ዚሚነግሚንፀ ዛሬ ላይ እንደ ደንጊያ ጜኑ እና ጚካኝ ዹሆነው ልባቜን ቀተ ክርስቲያንን እና ምእመናንን እዚጎዳ ይገኛል። ቅን ልቡና እና ዹተሰበሹ መንፈስ ጠፍቶ በጎቻቜንን በምድራዊ ሀሳብ እና በቁሳዊ ተራ እይታ መመልኚት ኹጀመርን ሰንብተናል።

በተለይም በአባቶቜ ደሹጃ ለተጠራንበት ተልዕኮ መሥራት ካቆምን፣ ልጆቻቜንን አስጚናቂ አገዛዝ ኚጫንባ቞ው እና ዚምንመራ቞ው ልጆቻቜን በምንኹተለው ኃላ ቀር ዚመሪነት ዘይቀ ተሰላቜተው ተስፋ ኚቆሚጡ ቆይተዋል። ለዚህ ድካማቜን መፍትሔውም ዚድንጋዩን ልብ ኚውስጣቜን አውጥተን ዚሥጋን ልብ ለማግኘት መሥራት እንጂ ለዘመናት በኖሹ መቋጠሪያ በሌለው ቜግሮቜ ውስጥ ሆነን በኛ ድክመት ዚፈታነውን ሕዝብ ልዩ ልዩ እንቆቅልሜ እዚፈጠርን ግራ ማጋባት ሊጠቅመው አይቜልም።

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን
ምእመናንና ምእመናት:-

አዲሱን ዓመት ስንቀበል በአሮጌው ዓመት ዚነበሩ ዚክፋት ሥራዎቻቜን፣ ዚልዩነት መንገዶቻቜን እና ዚጥፋት ዕቅዶቻቜን በአዲሱ መንፈስ ዚሚሻሩበትፀ ኹጹለማው አመለካኚታቜን ወጥተን ዚብርሃን መንገድን ልንኚተልፀ ያለፈውን ዚጥፋት ሥራ ያበዛንበትን ዓመት በአዲሱ ዓመት በንስሐ ታጥበን ለእውነት ልንሰራ ይገባናል።

በአሹጀ አቁማዳ አዲስ ዹወይን ጠጅ ዚሚያኖር ዚለምፀ ቢደሚግ ግን፥ አቁማዳው ይፈነዳል፥ ዹወይን ጠጁም ይፈሳል አቁማዳውም ይጠፋልፀ ነገር ግን አዲሱን ዹወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ያኖሚዋል፥ ሁለቱም ይጠባበቃሉ። እንዲል መጜሐፍ ቅዱስ በክፋት ባሚጀው ሰውነታቜን አዲስ ዘመንን መጹመር ኚኃጢአት ላይ ኃጢአትን መጹመር እና ዚኃጢአት ክምርን ማብዛት ስለሚሆን ምን ጊዜም አዲስ ዓመትን ስንቀበል በንስሐ እና በጎ ተግባርን በማብዛት ሊሆን ግድ ይለናል።

አዲሱን ዓመት ስንቀበልፀ ራሳቜንን ለለውጥ በማዘጋጀት፣ ሰላምን በመስበክ፣ ክርስቲያናዊ ተግባራትን በማብዛት፣ዚተራቡትን በማብላት፣ ዚተጠሙትን በማጠጣት ሊሆን እንደሚገባ እያሳሰብንፀአዲሱ ዓመት ዚፍቅር፣ዚሰላም፣ዚአንድነት እና ዚስምምነት እንዲሆን እንመኛለን ፀበማለት አስተላልፈዋል።

+ አባ ሄኖክ
በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን
ዚአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ

ጳጉሜን ፭ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዚደቡብ ምዕራብ ሜዋ፣ ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዚምስካዚ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ኃላፊ ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልእክት !

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዚደቡብ ምዕራብ ሜዋ፣ ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዚምስካዚ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ኃላፊ ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልእክት !

ወትባርክ አክሊለ አመተ ምሕሚትኚፀበ቞ርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ (መዝሙር 65-11)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ዚተኚበራቜሁ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ሊቃውንት ካህናት ዲያቆናት ዚመንፈስቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም መላው ኢትዮጵያውያን

እንኳን ኹዘመነ ዮሐንስ ወንጌላዊ ወደዘመነ ማ቎ዎስ ወንጌላዊ በሰላም እና በጀና አሞጋገራቜሁ
እንኳን አደሚሳቜሁ

ቀን እና ሌሊትን
ሳምንታትን እና ወራትን
አመታትን እና አዝማናትን እያፈራሚቀ በዕድሜያቜን ላይ ዕድሜን ጚምሮ ለአዲሱ ዘመን ያደሚሰን ኚዘመናት በፊት ዹነበሹ ዘመናትንም አሳልፎ ዹሚኖር ለህላዌው ዘመን ዚማይቆጠርለት ቞ሩ አምላካቜን መድኃኔዓለም ስለማይነገር ስጊታው እስኚዘለዓለም ዹተመሰገነ ይሁን

ዚተወደዳቜሁ ኢትዮጵያውያን
እግዚአብሔር ለፍጥሚታት ልዩ ልዩ ጞጋዎቜን አድሏል

እግዚአብሔር ለምድር እስኚዚህ ድሚስ ተብሎ ሊቆጠሩ ዚማይቜሉ አዝማናትን ሲሰጣት ለሰው ልጆቜ ደግሞ በአዝማናት ውስጥ ዚሚቆጠሩ ዕድሜያትን ይሰጣል

በእግዚአብሔር ቞ርነት ምድር ዘመንን ስትቀይር ዚምታገኛ቞ው ልዩ ልዩ ጞጋዎቜ አሏት
በሚቀዹሹው ዘመን ውስጥ ዚምድር ገጜታ ይለዋወጣል
ዹደሹቀው መሬት በዝናም ይርሳል
በዝናም ዚራሰው መሬት ቡቃያን ይይዛል
ቡቃያው ያፈራል
ቀላያት ሞልተው ይፈሳሉ
ተራሮቜ በአሹንጓዮ ይሞላሉ
ኹጊዜ በኋላ ዹለመለመው ሁሉ ሹግፎ ምድር ወደ ባዶነት ትቀዚራለቜ

ዹሰው ልጆቜ ዑደትም ይህን ይመስላል
እግዚአብሔር ለሰው ልጆቜ ዕድሜን ሲሰጥ
ሰዎቜ በተሰጣ቞ው ዕድሜ በኃጢአት ዹደሹቀ ሕይወታ቞ውን በቅድስና እንዲያለመልሙ
በኃጢአት ያደፈ ማንነታ቞ውን በንስሓ እንዲቀድሱ
ኚጥላቻ ሕይወት ወጥተው በፍቅር እንዲኖሩ
ኚጊርነት ወደ ሰላም እንዲመለሱ
በአጠቃላይ ህገ እግዚአብሔርን ጠብቀው ዚእግዚአብሔርን መንግስት እንዲወርሱ ነው

እግዚአብሔር ዘመንና ዕድሜን ለሰው ልጆቜ ሲሰጥ ባለፉት ዘመናት ዚሰራና቞ውን ክፉ ሥራዎቜ ይቅር ብሎ ኚነዚያ ክፉ ሥራዎቻቜን እንድንርቅ እና በንስሐ ወደ እርሱ እንመለስ ዘንድ ነው
ለዚሁም ሐዋርያው ቅዱስ ጎጥሮስ በመጀመርያው መልእክቱ ምዕራፍ 4-3 ላይ
“ዚአሕዛብን ፈቃድ ያደሚጋቜሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ ዚተመላለሳቜሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል።”
ብሎ ባለፈው ዘመን ኚኖርንበት ዚኃጢአት መንገድ እንድንመለስ ያስተምሚናል

ዚተወደዳቜሁ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት
ዘመን አልፎ ዘመን ሲመጣ በደመና ዹጠቆሹው ሰማይ ብርሃንን ይጎናጜፋል
ተራሮቜ ይለመልማሉ
ቆሻሻው በጎርፍ ታጥቊ ኚምድር ይሠወራል
ዹደፈሹሰው ውሀ ይጠራል
ምድር ፍሬን ትሰጣለቜ

ዹሰው ልጅ ግን ፊቱ በወንድሙ ላይ እንደጠቆሚ ነው
ሰውነቱ በጜድቅ ኹመለምለም ይልቅ በኃጢአት ደርቋል
ሰላምን ኚመስበክ ይልቅ ዚጊርነት ዜና ማስተጋባትን መርጧል
ለወንድሙ መድኃኒት ኹመሆን ይልቅ ዚወንድሙ ገዳይ ሆኗል

በእንደዚህ አይነት ሕይወት ውስጥ ሆኖ አዲስ ዘመንን መቀበል ዚእግዚአብሔርን ስጊታ ማቃለል ነው
ካለፈው መጥፎ ሕይወት ሳይመለሱ ዚዕድሜ ባለቀት መሆን በዕዳ ላይ ዕዳን መጹመር ነው

ስለዚህ ሁላቜን ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያውያት ኚሚያልፈው አሮጌ ዘመን ጋር አሮጌ አስተሳሰባቜንን በመጣል አዲሱን ዘመን እግዚአብሔርን ደስ በሚያሰኝ መልካም አስተሳሰብ ልንቀበለው ይገባል

ይህን ካደሚግን አምላካቜን እግዚአብሔር ዘመናቜንን ይባርክልናል
ምድራቜን ዹሰላም ምድር ትሆናለቜ
በሰዎቜ መካኚል ጥላቻ ጠፍቶ ፍቅር ይነግሳል
ኹሁሉም በላይ በሚያልፈው ዘመንና በምታልፈው ምድር ዚምንሰራው መልካም ሥራ ዚማያልፈውን ዚእግዚአብሔር መንግሥት እንድንወርስ ይሚዳናል

ዘመኑ ዹሰላም ዹፍቅር ዚአንድነት ዹዕርቅ ዚበሚኚት ዘመን ይሁንልን

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ
መልካም አዲስ ዓመት

አባ ሳዊሮስ
በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዚደቡብ ምዕራብ ሜዋ ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዚምስካዚ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም ኃላፊ

 

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጊስ በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ ማደራጃ መምሪያና ዹሰሜን ሾዋ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዹዘመን መለወጫን በዓል አስመልክተው ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልእክት አስተላለፉ።

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጊስ በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ ማደራጃ መምሪያና ዹሰሜን ሾዋ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዹዘመን መለወጫን በዓል አስመልክተው ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልእክት አስተላለፉ።

ዚብፁዕነታ቞ውን ሙሉ መልእክት እነሆ!!!
* * * * *

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

“ምድር ሠናይት እንተ ዘልፈ ይሔውጻ እግዚአብሔር አምላክኹ ፀ ወአዕይንቲሁ ለእግዚአብሔር አምላክኹ ላዕሌሃ እምርእሰ ዓመት እስኚ ማኅለቅተ ዓመት ”

“አምላክህ እግዚአብሔር ዚሚጎበኛት አገር ናት ፀ ኚዓመቱ መጀመሪያ እስኚ ዓመቱ መጚሚሻ ድሚስ ዚእግዚአብሔር ዓይን ሁልጊዜ በርሷ ላይ ነው”ዘዳ ፲፩ ÷ ፲፪

ዚተወደዳቜሁ እና ዚተኚበራቜሁ በቅድስት ሀገራቜን ኢትዮጵያ በመላው ዓለምም ዚምትገኙ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በሙሉ ዚዘመናት ባለቀት እግዚአብሔር 2016 ዓ.ም ዘመነ ዮሐንስን በሰላም እና በጀና አስፈጜሞ እንኳን ለ2017 ዓም ዘመነ ማ቎ዎስ በሰላም እና በጀና አደሹሰን! አደሚሳቜሁ!!!

ዚዘመናት ባለቀት እግዚአብሔር ዘመንን በዘመን እዚለወጠ ዓለም ኹተፈጠሹ ዘመን ኹተቆጠሹ 5500 ዓመተ ኲነኔ 2017 ዓመተ ምሕሚት በአጠቃላይ 7517 ዘመን ይሆናል ።

እስራኀል ዘሥጋ በግብፅ ባርነት በነበሩበት ዘመን ተወልዶ በፈርኩን ቀት ዹፈርኩን ልጅ መባልን በእምነት እንቢ በማለት ያደገው ክቡደ መዝራዕት ሙሮ ኹ4 መቶ 30 ዚግብፅ ባርነት ዘመን በኋላ እስራኀላውያንን ነጻ ለማውጣት በግብፅ እና በግብፃውያን ላይ ዘጠኝ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን አሥሚኛ ሞተ በኲርን አሥራ አደኛ ስጥመትን ፈጜሞ በርሱ መሪነት በመልአኩ ተራዳኢነት በእግዚአብሔር አሻጋሪነት ቀይ ባሕር ተኹፍሎላቾው በደሹቅ አልፈው ኚሞት ወደሕይወት ኚባርነት ወደነጻነት ኚውርደት ወደ ክብር ተሾጋግሹዋል ።

በመሆኑም ዚእግዚአብሔር ሰው ሙሮ በጞናቜ ዚእግዚአብሔር እጅ እስራኀል ዘሥጋን ኚግብፅ ዚባርነት ሕይወት ነጻ አውጥቶ ሊወርሷት ወደአለቜው ዚአባቶቻ቞ው ርስት ዚተስፋይቱ ምድር ኹነአን ለመግባት በሞአብ ሜዳ ላይ በጉዞ ለነበሩት ለእስራል አዲሱ ትውልድ ዚምትወርሷት ዚበሚኚት ምድር ኹነዓን ዝናብ እንደማይዘንብባት እንደ ግብፅ ምድር አይደለቜም።

ዹቃል ኪዳን ምድር ኹነዓን ዚዘሩባትን ዚምታበቅል ዚተኚሉባትን ዚምታጞድቅ እግዚአብሔር ዚሚጎበኛት ዚእግዚአብሔር ዓይን በሚድኀት ዚማይለያት መሆኑን በመግለጜ በውስጧ በሰላም ለመኖር ዚባርነት ቀንበራ቞ውን ሰብሮ መና ኹሰማይ አውርዶ እዚመገበ ውኃ ኚዓለት ላይ አፍልቆ እያጠጣ ያሻገራ቞ውን ዚእግዚአብሔርን ሕግ እና ሥርዓት ጠብቀው እንዲኖሩ በአጜንኊት ሲመክራ቞ው እናስተውላለን።

ዚተወደዳቜሁና ዚተኚበራቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን አባቶቻቜን በአጥንታ቞ው እና በደማቾው አጜንተው ያስሚኚቡን ቅድስት ሀገራቜን ኢትዮጵያ ስሟ በመጜሐፍ ቅዱስ ተደጋግሞ ዚተወሳ ልክ እንደተስፋይቱ ምድር ኹነዓን 3 መቶ 65 ቀናት ስመ እግዚአብሔር ዚሚጠራባት ሥርዓተ አምልኮ ዚሚፈጞምባት እግዚአብሔር ኚዓመቱ መጀመሪያ እስኚ ዓመቱ መጚሚሻ በምሕሚት ሀገሹ እግዚአብሔር በምሕሚት ዓይኑ ዚሚመለኚታት ፣ መዝበ ታሪክ ዓይኑ ዚሚመለኚታት ሀገሹ እግዚአብሔር ፣ መዝገበ ታሪክ ፣ ዚቅርስ ማዕኹል እና ዹሰው ዘር መገኛ መሆኗን እናስታወሳለን።

ይሁን እንጂ ኚቅርብ ዓመታት ወዲህ በተለዹ ሁኔታ ኚውስጥና ኚውጪ እዚደሚሰ ባለው ፈርጀብዙ ዚተፈጥሮ እና ዹሰው ሠራሜ ቜግር ምክንያት በአራቱም ማዕዘን በጊርነት ድምፅ እዚተናጠቜ ዹፈተናና ዚመኚራ ማዕበል እያንገላታት ትገኛለቜ።

በዚሁ ቜግር ምክንያት ዚተነሳ በርካታ ወገኖቻቜን መተኪያ ዚሌላት ውድ ሕይወታ቞ውን እያጡ ሲሆን ለዘመናት ዚደኚሙበት ሀብት ንብሚታ቞ው እዚጠፋ ይገኛል።

ኚቀት ቀያ቞ው ተፈናቅለው ለቀን ሀሩር ለሌሊት ቁር ተጋልጠዋል ፀ ሕፃናት ኚትምህርት ገበታ ተለይተው ዚለጋነት እድሜያ቞ውን በኚንቱ እያሳለፉት ይገኛሉ ፀ በአጠቃላይ በሀገራቜን እዚሆነ ያለውን ነገር ስንመለኚት ቜግሩ አሳሳቢ ደሹጃ ላይ መድሚሱን እንገነዘባለን።

በመሆኑም ኹዘመነ ዮሐንስ ወደዘመነ ማ቎ዎስ ስንሞጋገር እስራኀል ዘሥጋ ኚግብፅ ወደኹነዓን ሲሻገሩ ዚግብፅን ትብት በግብፅ ቀብሚው ኚሞት ወደሕይወት ኚባርነት ወደነጻነት እንደተሻገሩ እኛም እስራኀል ዘነፍስ ያሚጀውን ሰውነት ገፍተን አዲሱን ሰውነት በመልበስ አሮጌውን ዚኃጢኣት ርሟ አስወግደን አዲስን ዚጜድቅ ርሟ ገንዘብ በማድሚግ ጥላቻን አውልቀን ፍቅርን በመልበስ መለያዚትን ተጾይፈን አንድነትን በመጎናጾፍ ዚክርስቶስ መልክ መገለጫ ዹሆነውን ዹሰውን ልጅ በሰውነቱ ብቻ በማክበር በአዲስ ልብ በአዲስ አስተሳሰብ በአዲስ መንፈስ ልንሻገር ዚሚገባ መሆኑን በአጜንኊት ማሳሰብ እንፈልጋለን ።

ዘመነ ክሚምት አልፎ አዲሱ ዓመት ሲገባ መስኚሚም ሲጠባ ዹወንዝ ውኃዎቜ ይጠራሉ አበባዎቜ ይፈካሉ ዚእኛም ሕይወት በንስሓ ውኃ ሊጠራ በበጎ ነገር ሁሉ ሊፈካ በአዲሱ ዓመት አዲስ ማንነት ሊኖሹን ያስፈልጋል።

በመጚሚሻም ዹዘመን መለወጥ ለሰው ልጅ ሕይወት ትርጉሙ ኹፍ ያለ በመሆኑ በሕይወታቜን ተለውጠን ስለ ሀገራቜን እና ስለሕዝባቜን በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት በመጾለይ ዹሰላም ሰው ሆነን ለሰላም ዚልባቜንን በር በመክፈት እጃቜንን ለፍቅርና ለአንድነት በመዘርጋት በማሚሚያ ቀት ፣ በሆስፒታል እና በተለያዚ ቜግር ውስጥ ያሉ ወገኖቻቜንን በመጠዹቅ ፣ ያለንን ለሌላቾው ወገኖቻቜን በማካፈል በይቅርታ ልብ መጪውን አዲሱን ዓመት እንድንቀበለው በማለት መልእክታቜንን እናስተላልፋለን ።

መጪው አዲሱ ዘመን ዘመነ ማ቎ዎስ ሞት እና ጊርነት ዚሚቆምበት ዚጥይት ጩኞት ዚማንሰማበት ዚሀገራቜን ቜግር ዚሚፈታበት ዹሰላም ዹፍቅር እና ዚበሚኚት ዘመን እንዲሆንልን መልካም ምኞታቜንን በመጾለይ ጭምር እንገልጜላቜኋለን ።

ቅዱስ እግዚአብሔር ሀገራቜን ኢትዮጵያን እና ሕዝቊቿን ይባርክ!!!

አባ ቀሌምንጊስ
በኢ/ኩ/ተ/ቀ/በመ/ፓ/ጠ/ቀ/ክ ዚሰንበት ት/ቀቶቜ ማደራጃ መምሪያ እና ዹሰሜን ሾዋ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ!!!

ጳጒሜን ፭ ቀን ፲፫ ወር ፳፻ ፲፮ ዓም
ሺዋ ደብሚ ብርሃን ኢትዮጵያ!!!

“ይህ ዓመት ለሕዝባቜን፣ ለሀገራቜንና ለዓለማቜን ሰላም፣ ደስታና መንፈሳዊ እድገት እንዲያመጣ ዚዘወትር ምኞቮና ጾሎቮ ነው” ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ ሊቀ ጳጳስ

“ይህ ዓመት ለሕዝባቜን፣ ለሀገራቜንና ለዓለማቜን ሰላም፣ ደስታና መንፈሳዊ እድገት እንዲያመጣ ዚዘወትር ምኞቮና ጾሎቮ ነው” ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ ሊቀ ጳጳስ

ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ ዚዩኬ፣ አዚርላንድና ዚሩቅ ምሥራቅ ሀገራት ሊቀ ጳጳስ አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድሚግ መልእክት አስተላልፈዋል። ዚብፁዕነታ቞ው መልእክት ሙሉ ቃል ኹዚህ እንደሚኚተለው አቅርበነዋል።

‘‘ኚዓመቱ መጀመሪያ እስኚ ዓመቱ መጚሚሻ ድሚስ ዹአምላክህ ዚእግዚአብሔር ዓይን ሁልጊዜ በርስዋ ላይ ነው።’’
ኊሪት ዘዳግም ፲፩:፲፪

በዚህ ዚአዲሱ ዓመት ዚመጀመሪያ ዕለት ሰፊ በሆነው ምሕሚቱ ፣ ጥልቅ በሆነው ዚአባትነት ፍቅሩ ለሰኚንዶቜ በማይቋሹጠው ጥበቃውና እንክብካቀው ሳይለዚን ኹዘመነ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ቅዱስ ማ቎ዎስ አሞጋግሮ ለዚህ ቀን ላደሹሰን ሁሉን ቻይ ለሆነው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋናቜንን በፊቱ እናቀርባለን።

በኊሪት ዘዳግም ምዕራፍ 11 ቁጥር 12 ላይ ያሉት አምላካዊ ቃላት አልፋና ኩሜጋ ዹሆነው አምላቜን ልዑል እግዚአብሔር በዘመናት ውስጥ ሁሉ ለሕዝቡ ያለውን ፍቅር ዚሚያስገነዝብና በተለይም በኊርቶዶክሳዊው ቅዱስ ትውፊት ዚእግዚአብሔር መግቊትና እንክብካቀ በሕይወታቜን ዘመን ሙሉ እንደሚሰራና በፍጹም አባትነቱ እንደሚመራን ዚምንገነዘብበት ክፍል ነው።

በጥንታውያን ቅዱሳን አባቶቻቜን ትምህርትና ሕይወት ባማሚውና ባሞበሚቀው ዚቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜያቜን ይህ ክፍል እግዚአብሔር ፍጥሚታቱን ፈጥሮ ዹተወ ሳይሆን ይልቁንም ኚፍጥሚታቱ ያለተለዚ ዚፍጥሚታት ሁሉ መጋቢና ጠባቂ መሆኑን እንመለኚትበታለን።

አበው እንደተሚጎሙትም ‘‘ዚእግዚአብሔር ዓይን’’ ተብሎ በዚህ ዚመጜሐፍ ቅዱስ ክፍል ላይ ዚተጻፈልን ቃል እግዚአብሔር በፍጥሚታቱ ላይ ዚሚያፈሰውን ዚማያቋርጥ መግቊት፣ ጥበቃ፣ መሪነትና በሹኹተን ዚሚያሳይ ነው። ለዚህም ወደር ዚለሜ መለኮታዊ እንክብካቀ ዚማያቋርጥ ዚምስጋና እና ዚመታዘዝ ሕይወትን በመምራት ራሳቜንን በምላሹ ለእርሱ መስጠት ይገባናል።

ዹ ፳፻፲፯ ዓመተ እግዚእ አዲስ ዓመትን ስንጀምርም፣ ያለፈውን ዓመት እንዎት እንደተጓዝነውና እንዳሳለፍነው በማሰላሰል ልባቜንን ለመንፈሳዊ ዚሕይወት ለውጥና ዕድገት ዝግጁ ማድሚግ ይገባናል። ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ዚጊዜያቜንን አላፊ መሆንና ዹተሰጠንንም ጊዜ በጥበብ መጥቀም እንዳለብን ካስገነዘበ በኋላ በጥበብ መመላለስ እንደሚገባን ‘‘በልብ ጥበብን እንድማር ቀኝህን እንዲህ አስታውቀን’’ (፹፱:፲፪) በማለት ያስተምሚናል።

ጥበብን ማወቅ ማለት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ፣ ሀሳብና መንገድ መጓዟን ፣ ፍትሃዊ መሆንን ፣ ምሕሚት ማድሚግ መውደድንና ይልቁንም እንደ ጌታቜን መድኃኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ በትህትና በምድር ላይ መመላለስና መኖር መቻል ነው።

ኊርቶዶክሳዊት ቀተክርስቲያናቜን በእያንዳንዷ ቅጜበት እግዚአብሔርን በማሰብና ዚእርሱን ኚእኛ ጋር መሆኑን ማስተዋል እንደሚገባን ታስተምራለቜ። ዚሥርዓተ አምልኮ ማዕኹልም ኹተሰጠን ኚእስትንፋሳቜን ጀምሮ ለማያልቀው ኚእርሱ ለተቀበልነው ልዩ ልዩ ስጊታዎቹ ዚማያቋርጥ ምስጋናን ማቅሚብና ኚእርሱ ያልሆነ ምንም ነገር እንደሌለ ማስገንዘብ ነው።

ቅዱስ ዳዊት ‘‘በ቞ርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ ፣ ምድሚ በዳውም ስብን ይጠግባል’’ (፷፬፡፲፩) በማለት እንደዘመሚው ፈጣሬ ዓለማት ልዑል እግዚአብሔር ዘመናትን ዚበሚኚቱን አክሊል ያቀዳ቞ዋል። እኛም ልጆቹ በጞሎት፣ በመልካም ሥራና እርሱ ለመምሰል በሚደሹግ ክርስቲያናዊ ጉዞ እንድንጓዝ ተጠርተናል።

በመሆኑም አሮጌው አልፎ አዲሱን ዓመት ስንቀበል ቅዱስ ጳውሎስ በ ፪ኛ ቆሮንቶስ መልእክቱ ‘‘ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥሚት ነው’’ (፭:፲፯) በማለት ዚጻፈልንን ቃል ማሰብና እንደ ቃሉ መኖር ይገባናል።

ይህ ኚእግዚአብሔር ዹተሰጠን አዲስ ዓመት ምድራዊ ለውጥን ብቻ ሳይሆን ይልቁንም መንፈሳዊ ዚሕይወት ለውጥ እንድናመጣና ዕድገትንም እንድናሳይ ኚእግዚአብሔር ዘንድ ዹተሰጠን አዲስ ዚንስሐ ጊዜ እንደሆነ እናስብ። ይህ ዚመንፈሳዊ ሕይወት ለውጥም በቀተክርስቲያናቜን ውስጥ በጟም፣ በጞሎትና በቅዱሳት ምሥጢራት አማካኝነት በመንፈስ ቅዱስ ዹሚገኝ መሆኑን እናስተውል።

በዚህ አዲስ ዓመት በእነዚህ ኚእግዚአብሔር በተሰጡን ቅዱሳት ምሥጢራት አማካኝነት በኃጢአት ዹጎሰቆለውን አሮጌውን እኛነታቜንን ትተን በጌታቜን በኢዚሱስ ክርስቶስ በማያቋርጥ መንፈሳዊ ዕድገት ውስጥ መገኝት ይገባናል።

ዚተወደዳቜሁ አበው አባቶቻቜንና ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ፣

ይህንን አዲስ ዓመት ስንጀምር ወደ እግዚአብሔር በመቅሚብ፣ በጞሎት ሕይወታቜን በመበርታት፣ ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ባሳዚን ኚራስ ወዳድነት ነፃ በሆነ ፍቅር እርስ በእርሳቜን በመዋደድ ለቀተክርስቲያናቜን ፣ ለሀገራቜን ብሎም ለዓለማቜን ዹሰላም ምሳሌዎቜና ምንጮቜ እንሆን ዘንድ በልዑል እግዚአብሔር ስም እማጞናቜኋለሁ።

ይህ ዓመት ለሕዝባቜን፣ ለሀገራቜንና ለዓለማቜን ሰላም፣ ደስታ እና መንፈሳዊ ዕድገት እንዲያመጣ ዚዘወትር ምኞቮና ጾሎቮ ነው።

በዚህ አዲስ ዓመት ዘላለማዊ ዹሚሆን ዹሰማይ ቀታቜንን ብቻ መመልኚት እንቜል ዘንድ ዚእመቀታቜን ዚቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትና እና ዚቅዱሳን ሁሉ ምልጃ፣ ሚድኀትና በሚኚት ይደርብን ! ኹዚህ ዓመት መጀመሪያ ጀምሮ እስኚ መጚሚሻው ድሚስ ዚእግዚአብሔር በሚኚቱ፣ ፀጋው፣ ፍቅሩ እና ጥበቃው ኚእኛ ጋር ይሁን! አሜን።

‘‘ዚተስፋ አምላክም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በተስፋ እንድትበዙ በማመናቜሁ ደስታና ሰላምን ሁሉ ይሙላባቹሁ ’’ሮሜ ፲፭: ፲፫

አባ ያዕቆብ
ዚሩቅ ምሥራቅ፣ እንግሊዝ፣ አዚርላንድና
አካባቢው ሀገራት አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ

እንኳን ለ፳፻፲፯ ዐዲስ ዓመት በሰላም አደሚሳቜኹ

“…እርስ በእርሳቜኹ በሰላም ኑሩ።” ፩ኛ ተሰ. ፭፥፲፫
እግዚአብሔር ሀገራቜንና ቀተ ክርስቲያናቜንን በሰላም ይጠብቅልን።
በዓሉ ዚተቀደሰ፣ ዚሰላም፣ ዚደስታና ዚጀና እንዲኟንላቜኹ እመኛለኹ።
*ልዑል እግዚአብሔር ዹተቀደሰ ዐዲስ ዓመት ያድርግልን።*

አባ ዲዮናስዮስ
ዚምሥራቅ ጎጃም፣ እና ዹጀርመን አካባቢው
አኅጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ

ብፁዕ አቡነ ኀዎስጣ቎ዎስ ዶ/ር ዚሐይማኖት አባቶቜ ሠላም እንዲሰብኩ አሳሰቡ!

ዚኢሉ አባ ቩር ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ አባል ዚመቱ ፈለገ ሕይወት መንፈሳዊ ኮሌጅ ዹበላይ ጠባቂ ሊቀ ጳጳስ አዲሱን ዓመት አስመልክቶ ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልእክት አስተላለፉ።

”  በ቞ርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድሚ በዳውም ስብን ይጠግባል። ዚምድሚ በዳ ተራሮቜ ይሚካሉ፥ ኮሚብቶቜም በደስታ ይታጠቃሉ። መዝ.65:11 ዹሚለውን ዚቅዱስ ዳዊት ቃል መሠሚት አድርገው መልእክታ቞ውን አስተላለልፈዋል።

ፈጣሪ ዘመናትን አሳልፎ አዲሱን ዘመን ዚሚያሳዚን በመልካምነታቜን ሳይሆን በምህሚቱ ብዛት ነው ያሉት ብፁዕነታ቞ውፀሁሌም  ዓዲስ ዘመን ዹሚሰጠን ለሥራና ለለውጥ ነው ብለዋል።አዲሱን ዓመት ስንቀበል በሳለፍነው አሮጌ ዓመት ምን ዹጎደለን ነገር አለ?ብለን ራሳቜንን እንድንጠይቅና ምናልባታም ባጠፋነው ጥፋት ተጞጜተን ንሰሀ ገብተን እንመለስ ዘንድ አዲሱ ዘመን በ቞ርነቱ ተሰጥቶናል ብለዋል።

በሀገሪቷ ውስጥ በሁሉም ስፍራ ሠላም መጥፋቱ ዋና አጀንዳ ሆኗል ያሉት ብፁዕነታ቞ው ፀ በእኛ መሀል ሠላም ዹለም ፣ሁሌም መጣላት ዹሰርክ ተግባራቜን ሆኗልፀ በዚስፍራው ዹሚሰማው ዜና አሳዛኝ እዚሆነ መጥቷል፣ጊርነት ሀገሪቷን ወደ ኋላ እዚመለሳት ነው፣ ይህ ሁሉ ዚበደላቜን ውጀት ነውና በአዲሱ ዓመት ወደ ልባቜን ተመልሰን ልንለውጥ ይገባናል ብለው ዚሐይማኖት አባቶቜና ዹሀገር ሜማግሌዎቜ  ሠላምን አብዝተው በመስበክ በሕዝብ መሀል ስምምነትና መተማመን  እንዲኖር መስራት አለባ቞ው  ብለዋል።

ዹሰው ልጅ በቜሮታ ዹተሰጠውን ጊዜ ተጠቅሞ ካልተለወጠ ዹተለወጠ  ዘመን ማክበሩ ጥቅም ዹለውም ብለዋል። ብፁዕነታ቞ው አያይዘው  በርካትቶቻቜን በአዲሱ ዘመን አስበን ልብሳቜንን እንቀይራለን እንጂ ልባቜንን አንቀይርም ብለው በውስጣቜን ያለው  ዚድንጋይ ልብ አውጥተን ዚሥጋ ልብ ዚምህሚትና ዹፍቅር ልብ ሊኖሹን ይገባል በለዋል።

በአዲሱ ዘመን ጋራና ሞንተሚሩ አበባን ለብሰው ደምቀውና አምሹው ተቀይሹው ይታያሉ ያሉት ብፁዕነታ቞ው ዹሰው ልጅ ግን አይቀዹርም  ኚምድር አበባ አንሰናልናል በእውነት ወደ ፈጣሪያቜን መመለስ አለብን ብለው  ሰው ክቡር ሆኖ ሳለ እንደሚጠፋ እንስሳ  እዚሆነ መምጣቱ አሳሳቢ ነውና በተጹመሹልን ዓዲሱ ዘመን ልንመለስ ይገባል ብለዋል።

በመጚሚሻም ለመላው ዚሀገራቜን ሕዝቊቜ፣በተለይም ለኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመናን ለሀገሹ ስብኚታቜን ሕዝብ እንኳን ኹዘመነ ዮሐንስ ወንጌላዊ ወደ ዘመነ ማ቎ዎስ ወንጌላዊ በሠላምና በጀና  አሾጋገሹን አሞ፡ሀጋገራቜሁ ብለዋል!

ጳጉሜ 5/2016 ዓ. ም
ዚኢሉ አባ ቩር ሀገሹ ስብኚት ሚዲያ

ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ ዚድሬዳዋ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዹዘመን መለወጫን በዓል አስመልክተው አባታዊ ቃለ በሚኚት አስተላለፉ።

መስኚሚም ፩ቀን ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም ዚድሬዳዋ ሀገሹ ስብኚት ዚፌስቡክ ገጜ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

“ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕሚትኚፀወይጞግቡ ጠላተ ገዳም።”
“በ቞ርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ምድሚ በዳውም ስብን ይጠግባል።” መዝ ፷፬÷፲፩

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት

ኹሁሉ አስቀድሜ ልዑል እግዚአብሔር አምላካቜን ያለፈውን ዓመት በሰላምና በጀና በሕይወት ጠብቆ አሁን ላለንበት ጊዜና ሰዓት ያደሚሰን ፈጣሪ ስሙ ዹተመሰገነ ይሁን።

ውድ ዹሰላምና ዹፍቅር ተምሳሌት ዚሆነቜው ዹበሹሃዋ ንግስት ዚድሬዳዋ ኹተማና አካባቢው ነዋሪዎቜ እንዲሁም በሀገር ውስጥና በውጪው ዓለም ዚምትገኙ ውድ ኊርቶዶክሳውያን ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜንና መላው ዚሀገራቜን ሕዝቊቜ በሙሉ።

እንኳን ለ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም በሰላምና በጀና አደሚሳቜሁ አደሹሰን ዹሰላም አምላክ ዹፍቅር ጌታ ዚደስታ ሁሉ ባለቀት መጪውን ጊዜ ዘመነ ቅዱስ ማ቎ዎስ ጌታ እግዚአብሔር ለሀገራቜን ኢትዮጵያና ለቀተክርስቲያናቜን ሰላምና ፍቅር ሰጥቶን በጋራ ሀገራቜን ኢትዮጵያንና ቅድስት ቀተክርስቲያናቜንን ዚምናለማበትና ዚምናሳድግበት ዚተጣላን ዚምንታሚቅበት ኚድኅነት ኚቜግር ነፃ ዚምንወጣበት ዚበሚኚትና ዚይቅርታ ዓመት ያድርግልን። ውድ ኊርቶዶክሳውያን መላው ዚሀገራቜን ሕዝብ ሆይ እግዚአብሔር አምላክ በደላቜንን ይቅር እንዲለን ኚክፋት፣ኚተንኮል፣ኚሀሜት፣ኚዘሚኝነት ጞድተን በንጜህናና በቅድስና ሆነን ዘወትር ሁሉን ማድሚግ ወደሚቜለው አምላክ እንጞልይ ጌታ እግዚአብሔር ተአምራትን ያደርጋል ዓመቱን ዚሰላም፣ዚፍቅር፣ዚይቅርታ፣ዚአንድነት ያድርግልን አሜን።

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ !

አባ በርተሎሜዎስ
ዚድሬዳዋ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ
መስኚሚም ፩ቀን ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም
ድሬዳዋ ኢትዮጵያ

እግዚአብሔር አምላክ አገራቜን ኢትዮጵያን ይጠብቅልን።

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
“ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕሚትኚ፧ ወይጞግቡ ጠላተ ገዳሞፀ በ቞ርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድሚ በዳውም ስብን ይጠግባል።”መዝ. ፷፬÷፲፩

቞ርነትና ምሕሚት ዚባሕርይ ገንዘቡ ዚሆነለት አምላካቜን አግዚአበሔር ወሰን በሌለው አባታዊ ፍቅሩና መግቊቱ ሳይለዚን ጠብቆና አቆይቶ እንኳን ኹዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማ቎ዎስ ኚ፳፻፲፮ ዓ.ም ወደ ፳፻፲፯ ዓ.ም በሰላምና በጀና አሾጋገሹን
አዲሱ ዓመት ዚሰላም፣ ዚአንድነት፣ ዚሥራ፣ ዚመግባባትና ዹፍቅር ዓመት ይሁንልን።

እግዚአብሔር አምላክ አገራቜን ኢትዮጵያን ይጠብቅልን።
አባ ዲዮስቆሮስ
ዚደቡብና ዚደቡብ ምሥራቅ ትግራይ አህጉሹ ስብኚ፣ዚቀተ መጻሕፍት ወመዘክርና ዚማኅበራት ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን አስተዳደር ጉባኀ ዚአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ዹሰጠውን መግለጫ መነነሻ በማድሚግ በጉዳዩ ላይ ተወያይቶ ልዩልዩ ውሳኔዎቜን አስተላለፈ

ጷጉሜ ፭ ቀን ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም