መስከረም 1 ቀን 2017 ዓ.ም (ሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት)
======================

ርዕሰ አውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ ክብረ በዓሉ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ወልድያ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ተከብሯል። ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በበዓሉ ለተገኙ ምእመናን ዕለቱን አስመልክተው ትምህርትና ቃለ ምእዳን አስተላልፈዋል።

መጥምቀ ክርስቶስ ቅዱስ ዮሐንስ ከዘመነ ብሉይ ወደ ዘመነ ሐዲስ መሸጋገሪያ፣ ክርስቶስን ያስተዋወቀ የመጀመሪያ ሰባኪ፣ ለቤተ ክርስቲያን ምሥረታ መሠረት የጣለ ነቢይ፣ ካህን፣ ሰማዕት ነው ብለዋል ብፁዕነታቸው። ዛሬ የጀመርነው ዘመነ ማቴዎስ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ የምናፈራበት፣ ክፉ አመላችንን ትተን ወደእግዚአብሔር የምንቀርብበት እንዲሆን አባታዊ ምኞታቸውን ገልጸዋል። ዛሬ አንድ ብለን በጀመርነው ዘመነ ማቴዎስ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማስፋፋትና መደገፍ እንዲሁም ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማጠናከር ትኩረት እንዲደረግባቸው አሳስበዋል።

በልማድ ሳይሆን በእውቀት የሚያመልኩ ምእመናን ቁጥር ለማሳደግ የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማጠናከርና ሥርዓተ ትምህርቱን መተግበር የአዲሱ ዓመት የትኩረት ማዕከል እንዲሆን አባታዊ መመሪያ አስተላልፈዋል።