በመቅደላ ጊርነት ወቅት በእንግሊዝ ወታደሮቜ ኹተዘሹፉ ዚብራና መጻሕፍትና ልዩ ልዩ ንዋዹ ቅድሳት መካኚል እንደሆነ ዚሚገመት አንድ ጜላት እና ዚተለያዩ ቅርሶቜ በበጐ አድራጊዎቜ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ዚርክክብ ሥነ ሥርዓት በታላቋ ብሪታንያ ለንደን ኹተማ ተኚናወነ።

በዩኒቚርሲቲ ኮሌጅ ለንደን (UCL) መምህር ዚሆኑትና ለሹጅም ጊዜ በኢትዮጵያና በኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀክርስቲያን ጉዳይ ላይ ተመራማሪ ዚሆኑት ዶ/ር ጃኮፖ ግኒስኪ በመቅደላ ጊርነት ዘመን ኹአገር እንደወጣ ዚሚገመትና በእርሳ቞ው እጅ ዹነበሹ ጜላት ወደ ሀገሩና ወደ መንበሹ ክብሩ እንዲመለስ ኹፍተኛውን አስተዋጜዖ እንዳበሚኚቱ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያንን በመወኹል ጜላቱን ዚተሚኚቡት ዚልዑካን ቡድኑ ተወካይ ቀሲስ ዶ/ር አባተ ጐበና ምስጋና቞ውን በልዑካኑ ስም ኹፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል።

ብፁዕ አቡነ ሩፋኀል በዶምቢዶሎ ሎና በቄለም ወለጋ ልዩልዩ ዚልማት ሥራዎቜን አኹናወኑ ለቜግሚኛ ተማሪዎቜም ዚመማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ አዚሚጉ።

ብፁዕ አቡነ ሩፋኀል ዚጋምቀላ፣ዚአስሳ፣ዚቄለም ወለጋና ዚደቡብ ሱዳን አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በደምቢዶሎ ኹተማ በሚያደርጉት ሐዋርያዊ አገልግሎት በደምቢዶሎ ኹተማ ቀበሌ03 በአርባ ቀናት ተሰርቶ ዹተጠናቀቀውን ዚቅዱስ አማኑኀል ቀተክርስቲያን መስኚሚም 6ቀን 2016ዓ.ም ቅዳሎ ቀቱን ማክበራ቞ውን ዹሀገሹ ስብኚቱ ጜሕፈት ቀት ሕዝብ ግንኙነት ክፍል በላኹልን ዘገባ ገልጿል።

ዚጥቅምት ዚቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ ጥሪ ተላለፈ።

መስኚሚም ፲ ቀን ፳፻፲፮ ዓ/ም
አዲስ አበባ

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ ኚሚያደርጋ቞ው ዹምልአተ ጉባኀ ስብሰባዎቜ አንዱ ዹሆነው ዚጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ ስብሰባ መሆኑ ይታወቃል።
ዚቅዱስ ሲኖዶስ ጜ/ቀት ዚዘንድሮው ዚጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ ስብሰባ ኚጥቅምት ፲፪ ቀን ፳፻፲፮ ዓ/ም ጀምሮ እንደሚካሄድ በመግለጜ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ጳጳሳት ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፲፮ ዓ/ም በጜርሐ መንበሹ ፓትርያርክ እንዲገኙ መንፈሳዊ ጥሪውን አስተላልፏል።
ኚጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ ስብሰባ በፊት ባሉት ዕለታት አጠቃላይ ዚሰበካ መንፈሳዊ ጉባኀ ስብሰባ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና ጳጳሳት፣ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ዚመምሪያና ዚድርጅት ኃላፊዎቜ፣ዚአህጉሚ ስብኚት ዚሥራ ኃላፊዎቜ፣ ዚሰበካ ጉባኀያት ምክትል ሊቃነ መናብርትና ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ ተወካዮቜ በተገኙበት ይኚናወናል።

በውጭ አገር ለምትገኙ አህጉሹ ስብኚት ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዹተላለፈ መልዕክት

ለሁለተኛ ጊዜ በውጭ አገር ለሚገኙ አህጉሹ ስብኚት ጥሪ ተላልፏል።ስለሆነም በተላለፈው ጥሪ መሰሚት ዝርዝራቜሁ ኹዚህ ደብዳቀ ጋር ዹተለጠፈው አህጉሹ ስብኚት በአስ቞ኳይ ሪፖርታቜሁን እንድታቀርቡና በገጉባኀው ላይ እንድትሳተፉ መልዕክታቜንን እናስተላልፋለን ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን
ዚሰበካ ጉባኀ ማደራጃ መምሪያ
መስኚሚም ፲ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ


ዚመስቀል ደመራ በዓል ዚቅድመ ዝግጅት ሥራ በአምስት ማዕኚላት በመኹናወን ላይ ይገኛል።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ ማደራጃ መምሪያ ዚ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም ዚመስቀል ደመራ በዓል ዚቅድመ ዝግጅት ሥራውን እያኚናወነ ነው።

በዝቋላ አቡነ ገብሚ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ዹደሹሰውን ዝርፊያ በተመለኹተ አሰፈላጊው ክትትል እዚተደሚገ ነው።

መስኚሚም ፮ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
*****
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
“”””””””””””””””””””
በምሥራቅ ሾዋ ሀገሹ ስብኚት ዹሚገኘው ዹዝቋላ አቡነ ገብሚ መንፈስ ቅዱስ ገዳም በትላንትናው እለት ማንነታ቞ው ባልታወቁ ዘራፊዎቜ ዚደሚሰበትን ዝርፊያ በተመለኹተ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሚፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት አስፈላጊውን ክትትልና ማጣራት በማድሚግ ላይ ዚምትገኝ ሲሆን በጉዳዩ ዙሪያም ኚሚመለኚታ቞ው ዚመንግሥት ዚጞጥታ አካላት ጋር እዚተነጋገሚቜበት ነው።

በገዳሙ በተካሔደው ዝርፊያም ኚገዳሙ ጥንታዊያን ቅርሶቜ ጋር በተያያዘ ዹደሹሰ ምንም ዓይነት ጉዳት ዹሌለ መሆኑን ጠቅላይ ጜሕፈት ቀቱ ባደሚገው ማጣራት አሚጋግጧል።

በገዳሙ ኚዝርፊያው ጋር በተያያዘ ዹደሹሰውን ጉዳት በተመለኹተ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀቱ ኚገዳሙ፣ኚሀገሚ ስብኚቱና ኚሚመለኚታ቞ው አካላት ጋር በመሆን ተገቢውን ማጣራት እያደሚገ ሲሆን ዝርዝር ሁኔታውን በተመለኹተ በቅርቡ በመገናኛ ብዙሃን ዚምናሳውቅ መሆኑን እዚገለጜን ሕዝበ ክርስቲያኑ ኚቀተክርስቲያናቜን ማዕኹላዊ አስተዳደር ዹሚሰጠውን ማብራሪያ በትዕግስት እንዲጠባበቅ በቅድስት ቀተ ክርስቲያናቜን ስም መልእክታቜንን እናስተላልፋለን።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን
መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት

ዚቅድስት ልደታ ጀና ኮሌጅ በተኚታታይ ዓመታት ያስተማራ቞ውን ተማሪዎቜ አስመሚቀ።

ዚቅድስት ልደታ ጀና ኮሌጅ በተኚታታይ ዓመታት ያስተማራ቞ውን ተማሪዎቜ ብፁዕ አቡነ ጎጥሮስ (ዶ/ር) ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊ በተገኙበት አስመሚቀ።

በኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዚ፳፻ ፲ወ፮ዓ.ም ዚመስቀል ደመራ በዓል አኚባበር ዚዝግጅት ሥራ ግምገማ ተካሔደ ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት በ፳፻፲፭ ዓ/ም ዚሥራ ዓመት በነበሹው ዚሥራና ዚአገልግሎት አፈጻጞም ዙሪያ አጠቃላይ ዹጠቅላይ ጜ/ቀቱ ሠራተኞቜ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አሥኪያጁ በብፁዕ አቡነ አብርሃም መሪነት በጜርሐ ተዋሕዶ አዳራሜ ሠፊ ውይይት አደሚጉ።

ቃለ በሚኚት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአኲስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖትፀ ዘተናገሹ በበዓለ ርእሰ ዓውደ ዓመት ዘዕስራ ምእት ዐሠርቱ ወስድስቱ ዓመተ ምሕሚት

ጳጉሜን ፭ ቀን ፳፻ ፲ወ፭ ዓ.ም
*******
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“””””””””””””””””””””
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !!

👉 በሀገራቜን በኢትዮጵያ በገጠርና በኹተማ ዚምትኖሩፀ

👉 ኹሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር ዚምትገኙፀ

👉 ዚሀገራቜንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስኚበር በዹጠሹፉ ዚቆማቜሁፀ

👉በሕመም ምክንያት በዹፀበሉና በዚሆስፒታሉ ያላቜሁፀ
እንዲሁም ዹሕግ ታራሚዎቜ ሆናቜሁ በዚማሚሚያ ቀት ዚምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፡፡

ዘመንን በዘመን እዚተካ ፍጥሚቱን ዚሚመግብና ዚሚመራ እግዚአብሔር አምላካቜን እንኳን ኹዘመነ ሉቃስ ወደ ዘመነ ዮሐንስ በሰላም አደሹሰን አደሚሳቜሁ !

“ወኀለይኩ መዋዕለ ትካትፀ ተዘኚርኩ ዓመተ ዓለም ወአንበብኩፀ ዚድሮውን ዘመን አሰብሁፀ ዓመተ ዓለምን አስታወስሁፀ አነበብሁም” (መዝ.፞፮ ፥ ፩)ፀ

አዝማናትና ዓመታት ዚሚሚሱ ሳይሆኑ ሲታወሱ ዚሚኖሩ እንደሆኑ ቅዱስ ዳዊት በቅዱስ ቅብእ አማካኝነት ባደሚበት መንፈስ ቅዱስ ተመርቶ ያስተምሚናልፀ እውነት ነው ዓመታት በግድ ያለውድ መታሰባ቞ው አይቀርምፀ ትዝታ቞ውም አይጠፋምፀ ትዝታ቞ውም በመልካም ወይም በመጥፎ ሊሆን እንደሚቜል ዚሚያጠራጥር አይደለምፀ
አዝማናትና ዓመታት እንደ ሌላው ፍጥሚተ እግዚአብሔር ሁሉ፣ ለፍጥሚታት አገልግሎትን ሊሰጡ መልካም ሆነው ዚተፈጠሩ ና቞ው፡፡ ይሁን እንጂ በሰዎቜ ስሑት ተግባርና አስተሳሰብ ኚመልካምነት ወደ ጎጂነት መቀዚራ቞ው ዚምናስተውለው እውነት ነውፀ

አዝማናት ወይም ዓመታት ሰው በሰላም አርሶና ነግዶ ላቡንም አንጠፍጥፎ፣ ጣዕመ ሕይወቱን በአግባቡ ሊመራባ቞ው ፈጣሪውን ሊያመልክባ቞ው፣ ሊማርባ቞ውና ዕውቀት ሊገበይባ቞ው፣ ሲሳሳትም ንስሐ ገብቶ ሊታሚምባ቞ው ዚተሰጡ ጞጋዎቜ ና቞ውፀ ሰው አዝማናትን በዚህ ሲጠቀምባ቞ው መልካም ይሆናሉ በመልካምም ይታወሳሉፀ

ነገር ግን ሰው በቂምና በበቀል፣ በጥላቻና በመናናቅ እንደዚሁም ማቆሚያ በሌለው ዚራስ ወዳድነት ክፉ መንፈስ ተይዞ እርስ በርስ ዚሚጋጭባ቞ው፣ እግዚአብሔርንም ቾል ዚሚልባ቞ው፣ ለሥጋዊና ለመንፈሳዊ ሕይወቱ ዘላቂ ዚጋራ ጥቅም ዚማይጠቀምባ቞ው፣ ሁለንተና ሕይወቱን በንስሐ ዚማይታደስባ቞ው፣ በፍቅርና በሰላም ዚማይኖርባ቞ው ኹሆኑ ዓመታቱ መጥፎዎቜ ይሆኑበታል፣ በመጥፎም ይታወሳሉ፣ ይህ እውነታ በዓለም ታሪክም ሆነ በሀገራቜን ታሪክ በተደጋጋሚ መፈጾሙን በውል ዹምናውቀው ሓቅ ነው፡፡

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት !

ዚሩቅን ዘመን ትተን ባለፉት ጥቂት አዝማናት ያዚና቞ው ዓመታት በመልካም ትዝታ ዚሚታሰቡና ዚሚዘኚሩ እንዳልነበሩ ንጹሁ ኅሊናቜን ምስክር ነው፡፡ ስሕተቶቜ እንዎት ተፈጥሚውና አድገው ኚባድ ቜግር ላይ እንደጣሉንም አእምሮአቜን አይስተውምፀ እንደባለ አእምሮ፣ ዚእግዚአብሔርን ፈቃድ አውቀን፣ አክብሚንና ጠብቀን ብንመላለስ ኖሮ ዹሆነውን ክፉ ነገር ሁሉ ማዚት አንቜልም ነበርፀ

ትልቁ ዚእግዚአብሔር ፈቃድ ኹቂም ኹበቀል ርቀን ስራቜንን በፍቅርና በስምምነት፣ በትዕግሥትና በምክክር እንድንሰራ ነውፀ ኹዚህ ወጥተን ዹቂምና ዹበቀል ቊርሟ እዚመዘዝን እሱንም በመርዛም ኃይለ ቃል እያጀብን በነጐድን ጊዜ ግን ራሳቜንን በራሳቜን ክፉኛ ኚመጉዳታቜንም ሌላ ዹዓለም አጀንዳ ለመሆን ተገደድንፀ

ይህን ክፉ ተግባር ዚፈጞምንባ቞ው ዓመታት በክፉ እንጂ በመልካም ዚማይታሰቡ ሆነው አልፈዋልፀ አሁንም ክፉው አስተሳሰባቜንና ተግባራቜን በአስተማማኝ ዹተቀሹፈ መስሎ አይታይምፀ ኹሚገርመው ነገር ዚቜግሩን መንሥኀ ኚልብ ሲያጀኑት አሁን እዚተፈጞመ ላለው ጥፋት ዚሚመጥን ዚቜግር ፍሬ ነገር አይገኝበትምፀ ቜግር ቢኖርስ እውን በውይይት ዚማይፈታ ነበርን ? ተብሎ ቢጠዚቅም መልስ አይገኝለትምፀ

በወሰንና በርእዮተ ዓለም ምክንያት ዹምናደርገው ክርክርስ ኢትዮጵያ ለኢትዮጵያውያን ዹሚለውን መርሕ በትክክል ኹተገበርን ዚሚያኚራክሚው ምኑ ነው? ዚሀገሪቱ ሕግስ ይህንን መፍታት አይቜልም ነበርን ? በወሰን ምክንያት ጠብ ዚሚነሣውስ መላዋ ኢትዮጵያ ዹሁሉም ኢትዮጵያውያን መሆንዋን እዚሚሳን ይሆንን ? በአንድ ዹበላይ መሪ፣ በአንድ ዚሀብት ቋት ዚምንተዳደር ዚአንድ ኢትዮጵያ ልጆቜ አይደለንም ወይ?
ኢትዮጵያዊ ዹሆነ ሁሉ ኚዳር እስኚዳር ተንቀሳቅሶ እዚሰራ እንዳይኖር ዹኹለኹለ ሕግና ሥርዓትስ አለወይ ? ካለስ እሱን በምክክር ፈትቶ ስለታላቋ ኢትዮጵያ ብቻ በጋራ መቆም አይበልጥም ወይ? እውነቱ ይህ ኹሆነ ኢትዮጵያውያን ዚፖለቲካ ተፎካካሪዎቜ፣ ልኂቃን፣ ዚስቢክ ማኅበራትና ምሁራን ዚሆናቜሁ፣ ዹሆነው ሁሉ ትክክል አልነበሹምና እባካቜሁ ወደ ልባቜሁ መለስ በሉና ምርጫቜሁን ኢትዮጵያ፣ ሰላምና አንድነት ብቻ አድርጉፀ ሌላው ሁሉ በዚሁ ስር ነው ያለው፣ በሂደትም ደሹጃ በደሹጃ እዚተስተካኚለ ይመጣል፡፡

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት !

ያለፈው ዓመት ያሳሚፈብንን ሁለንተናዊ ተጜዕኖ በሚገባ አስተውለን፣ ዳግም ወደ አዲሱ ዓመት እንዳይሞጋገርብን ካላደሚግን አዲሱ ዓመት ለኛ ዹሚሰጠን ትርጉም ምንድን ነው ? ባለፉት ዓመታት በሃይማኖት፣ በባህል በታሪክ፣ በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም በሕዝባቜን ሥር ዹሰደደውን ዚእርስ በርስ መጠራጠር ኚልብ መርምሹን ወደ ድሮው እኛነታቜን ካልተመለኚትንስ አዲስ ዘመን እያልን ማክበራቜን ምን ፋይዳ አለው? ይህንን ሁሉ በአዲሱ ዓመት በማጀን ያለፈውን ጎጂ ነገር በመተውፀ ጠቃሚውን ግን ይበልጥ በማጠናኹር አዲሱን ዓመት መቀበል አለብንፀ

ኹሁሉ በላይ ለሀገራቜንና ለሕዝባቜን ዹሚጠቅመው ምንድነው? በሚለው በምር መስራት አለብንፀ በመለያዚት፣ በመፎካኚር፣ በመበቃቀል፣ በመናናቅ፣ ዚራስን ጥቅም ብቻ ለማስጠበቅ በመጣር፣ ጊዜ አገኘሁ ብሎ ኃይልን በመጠቀም፣ ዚሕዝብን ጥቅም ማስኚበርና ዹሀገርን አንድነት ማስቀጠል አይቻልምፀ ሀገራቜንንና ሕዝባቜንን ወደ ዕመቀ ዕመቅ እዚኚተቱ ያሉ እንደዚህ ያሉ አስተሳሰቊቜ ና቞ውፀ እነዚህ ሁሉ ኚአሮጌው ዓመት ጋራ አብሚው መወገድ አለባ቞ውፀ

በአዲሱ ዓመት ዹሰው ሕይወትን ዚሚቀጥፉ ዚመሳሪያ አፈ ሙዞቜ በሙሉ ወደ መጋዝን መግባት አለባ቞ውፀ ቜግሮቜን በውይይት፣ አሊያም በሕግ እዚተፈቱ ዹሀገርና ዚሕዝብ ሉዓላዊነት ነጻነትና አንድነት መሚጋገጥ አለበትፀ ሀገርንና ሕዝብን ለዘለቄታው በአንድነት ዚሚያስቀጥሉ ዹሕግ ዚበላይነትን ማክበር፣ እኩልነትን ማሚጋገጥ፣ ዚጋራ ተጠቃሚነትን እውን ማድሚግ፣ ዚተጐዳውን መደገፍ፣ ሆድ ዚባሰውን ማለዘብ፣ ዹተጠቃውን ማጜናናት ሲቻል ነው፡፡

በአዲሱ ዓመት ይህንን ለማድሚግ በቊርጥ ኚተነሣን ሰላማቜን ወደነበሚበት ይመለሳል፡፡ ሀገራቜንም በበሚኚት ትሞላለቜፀ ስለዚህም ኢትዮጵያውያን ዚሆናቜሁ ልጆቻቜን ሁሉ ይህንን ጥሪያቜንን ተቀብላቜሁ ዚጥፋት መሳሪያቜሁንም አስቀምጣቜሁ ወደ ሰላም ማእድ ቀርባቜሁ በወንድማማቜነት መንፈስ ቜግራቜሁን በክብ ጠሹጮዛ በውይይት በመፍታት ዚሀገሪቱንና ዚሕዝቡን አንድነት እንድታስቀጥሉ ሁሉን በሚያይ እግዚአብሔር ስም እንማጞናቜኋለን፡፡

በመጚሚሻም
አዲሱ ዓመት ዹሰላምና ዚፍቅር፣ ዹዕርቅና ዚይቅርታ ዹተፈናቀለው ወደቀዹው ዚሚመለስበት፣ ሆድ ዚባሰው ዚሚጜናናበት፣ ፍትሕና ርትዕ ዚሚሰፍንበት ዚመሳሪያ ድምፅ ዚማይሰማበት ፍጹም ዚተግባቊት ዓመት እንዲሆንልን እዚጞለይን ሁሉም ኢትዮጵያውያን ልጆቻቜን ለዚህ ቅዱስ ጥሪ አዎንታዊ መልስ እንድትሰጡ አባታዊ መልእክታቜንን በእግዚአብሔር ስም በድጋሚ እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር አምላክ አዲሱን ዓመት ዹሰላምና ዚተግባቊት ዓመት ያድርግልን ፀ

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቊቿን ይባርክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ
ተክለ ሃይማኖት
መስኚሚም ፩ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም.
ዋሜንግተን ዲሲ – አሜሪካ

ዹመንበሹ ፖትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት በ ፳፻፲፭ ዓ/ም አጠቃላይ ዚሥራ አፈጻጞም ዙሪያ ውይይት አካሄዱ።

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት በ፳፻፲፭ ዓ/ም ዚሥራ ዓመት በነበሹው ዚሥራና ዚአገልግሎት አፈጻጞም ዙሪያ አጠቃላይ ዹጠቅላይ ጜ/ቀቱ ሠራተኞቜ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አሥኪያጁ በብፁዕ አቡነ አብርሃም መሪነት በጜርሐ ተዋሕዶ አዳራሜ ሠፊ ውይይት አደሚጉ።