የአዳማ ሰቀቀሎ ደብረ ገነት ቅዱስ በዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤቱ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከበረ

ግንቦት ፪ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም አዳማ — በአዳማ ከተማ በውብ የኪነ-ሕንጻ ጥበብ የታነጸው የአዳማ ሰቀቀሎ ደብረ ገነት ቅዱስ በዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያን አዲሱ ሕንጻ ቤተ መቅደስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የሀገረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎችና በሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን በተገኙበት በዛሬው ዕለት ቅዳሴ ቤቱ በታላቅ መንፈሳዊ ድምቀት ተከብሯል።
ትላንት ግንቦት ፩ ቀን በብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ (የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳምና ሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ አባልና የኢትዮጵያ ሃይማኖቶች ተቋማት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ) እንዲሁም በብፁዕ አቡነ ጢሞቲዎስ (የዳውሮ፣ ኮንታ እና የከንባታ ሀላባ ጠንባሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ አባል) ቡራኬ ተባርኮ የተመረቀው ይህ ቤተ መቅደስ በዛሬው ዕለት ቅዳሴ ቤቱ ተከብሯል።
በክብረ በዓሉ ላይ በመገኘት ቡራኬና ትምህርት የሰጡት ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ምእመናን የእግዚአብሔርን ቤት በመሥራታቸው ያለቸውን ደስታ ገልጸው የሚከተለውን መልእክት አስተላልፈዋል፦
“ዛሬ አሳንጻችሁ የወልደ እግዚአብሔርን ሥጋውን የምንበላበት፣ ደሙን የምንጠጣበት የእግዚአብሔርን ቤት ሠርታችኋል። በዚህ ቤተ መቅደስ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያም ፣ ቅዱሳን መላእክትን፣ ጻድቃንና ሰማዕታትን እናገኝባቸዋለን። ይህ ሥፍራ ያዘነ የሚጽናናበት፣ የደከመ የሚበረታበት፣ ያጣ የሚያገኝበትና የተቸገረ ከችግሩ የሚላቀቅበት ዘላለማዊ ቤት ነው” ብለዋል።
ብፁዕነታቸው አክለውም፣ እግዚአብሔር ከምእመናን የሚፈልገው በዋናነት ራሳቸውን እንደሆነ ገልጸው፤ ምእመናን በንስሓ ሕይወት በመመላለስ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል እንዳለባቸው አሳስበዋል።
የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ በበኩላቸው፣ በሀገረ ስብከታቸው እየተከናወኑ ያሉ የቤተ ክርስቲያን የልማት ሥራዎችን በማድነቅ ጥልቅ የሆነ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክትና ቃለ ምዕዳን አስተላልፈዋል።
“ለሁሉም ነገር መሠረቱ ሕዝብ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝበ ክርስቲያን በሰላም፣ በአንድነትና በመቻቻል ተሳስሮ የኖረ ድንቅ ሕዝብ ነው። ይህ ሕዝብ ቤተ ክርስቲያኑን ሠርቶ በማስፈጸም ረገድ ያለውን ጥንካሬ የምናደንቀው ቢሆንም፤ ከምንም በላይ ግን ይህንን ለዘመናት የቆየ ሰላሙን፣ አንድነቱንና መቻቻሉን ጠብቆ ማስቀጠል አለበት” ብለዋል።
አክለውም አዳማ ከተማ የፍቅርና የአንድነት ከተማ መሆኗን ጠቅሰው፣ ከልጅ እስከ አዋቂ በገንዘባቸውና በጉልበታቸው ለደከሙ ሁሉ “እንኳን ደስ አላችሁ” በማለት በአባታዊ ቡራኬና ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል።
በዕለቱ የሀገረ ስብከቱ የስብከተ ወንጌል ኃላፊ መጋቤ ሐዲስ ቆሞስ አባ ኃይለ ገብርኤል ተስፋ፣ በብፁዕነታቸው መልካም ፈቃድ “የማትፈርስ መቅደስ” በሚል ርዕስ ጥልቅ የሆነ የወንጌል ትምህርት አስተምረዋል። መርሐ ግብሩን ደግሞ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ በብቃት መርተውታል።
በመጨረሻም ሕንጻ ቤተ መቅደሱ ከጅምሩ እስከ ፍጻሜው እንዲደርስ በእውቀታቸው፣ በጉልበታቸውና በገንዘባቸው ከፍተኛ ድጋፍ ላደረጉ ምእመናንና ባለሙያዎች ዕውቅናና ምስጋና ተሰጥቷል።
የሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ ማጠቃለያ ዕይታ ፤ ይህ ውብ ሕንጻ ቤተ መቅደስ ከ108 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበት ለፍጻሜ መብቃቱ፣ ከመንፈሳዊ ጥንካሬ ባለፈ የታላቅ አመራርና የተናበበ ሥራ ውጤት መሆኑን ነው።
​በተለይም የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ገነት ቀሲስ ታፈሰ ተስፋዬ፣ ግንባታው ከመሠረት ድንጋይ ጀምሮ እዚህ ደረጃ ላይ እስኪደርስ ድረስ የነበራቸው ሚና የሚደነቅ ነው። አስተዳዳሪው ከዲቁና የክህነት ማዕረግ ጀምሮ በዚህ ደብር ውስጥ በማገልገልና አሁን ላይም በኃላፊነት በመምራት፣ የአዳማ ከተማን ምእመናን በአንድነት በማስተባበር ያሳዩት ቁርጠኝነት ለቤተ መቅደሱ ግንባታ መሳካት ዋነኛ ምሰሶ ሆኖ ተገኝቷል።
​ይህ ክስተት የሚያሳየው፣ አንጋፋ አባቶች ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር በፍቅርና በትሕትና ሲሰለፉ፣ እንደዚህ ያሉ ታላላቅ የልማት ሥራዎችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ማከናወን እንደሚቻል ነው። ሚዲያችን እንደተመለከተው፤ የአስተዳዳሪው የረጅም ዘመን አገልግሎትና ከምእመናን ጋር የገነቡት ጥንካሬ፣ ዛሬ ለታየው ታላቅ መንፈሳዊ ድልና ለቤተ ክርስቲያኒቱ ክብር መጎናጸፊያ ሆኗል። ይህም ለሌሎች አድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችም ትልቅ ትምህርትና አርአያ የሚሆን ተግባር መሆኑን ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ ባደረገው ዳሰሳ አረጋግጧል።©ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በቃሊቲ አካባቢ ለበጎ አድራጎት ሥራ ከ23 ዓመት በፊት ያስገነቡትን Gተ1 የመኖሪያ ሕንጻ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማኅበር በስጦታ አበረከቱ

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የዋሽንግተን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት የስጦታ መርሐ ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ለበጎ አድራጎተት እንዲውል የሕንጻ ቁጥሩ 982 የሆነውንና በግል ገንዘባቸው በ544 ካሬ ሜትር ቦታ ያረፈ ሕንጻ በመገንባት ለዚሁ ዓላማ እንዲውል አድርገዋል።
ሕንጻው ያረፈበት ቦታ 240 ካሬ ሜትር ሲሆን በግንባታ ወቅት የወጣበት ወጪ ከ3ሚሊዮን በላይ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ባለው የገበያ ዋጋ ከ120 ሚሊዮን በላይ ይገመታል።ሕንጻው ከተገነባ 23 ዓመታትን ማስቆጠሩ ተገልጿል።
በመርሐ ግብሩ አቶ አምሓ ይልማ ባቀረቡት መልእክት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ሕንጻውን በገነቡበት ወቅት ያስተላለፉትን በሕግ ፊት የሚጸና ተብሎ የተመዘገበውን የኑዛዜ ሰነድ በጽሑፍ አቅርበውታል።
ቤቱን ለመቄዶንያ አረጋውያንና አእምሮ መርጃ ማዕከል ለማስተላለፍ ከቤተ ሰብ ጭምር ኮሚቴ (ቦርድ) ተቋቁሟል ተብሏል።
በመቀጠልም በስጦታ አድራጊ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤልና በስጦታ ተቀባይ መቄዶንያ የውል ስምምነት ሰነድ እና ካርታ ርክክብ ተፈጽሟል።
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በስጦታ መርሐ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልእክት እግዚአብሔር የሰጠኝን ቤት ለእግዚአብሔር አስረክቤያለሁ ብለዋል። ብፁዕነታቸው ጨምረው እንደገለጹት 19 ዓመት የቤቱ ኪራይ ለበጎ አገልግሎት ውሏል ብለዋል።
መስጠት የማይፈልጉ ኃይሎች የእኔን ስጦታ ሲተቹ ሰምቻለሁ።
ይህ ግን አግባብነት የለውም ብለዋል። ብፁዕነታቸው እኔ የሚቆጠር ንብረት የለኝም ያሉ ሲሆን በመጨረሻም ካርታውንና የቤቱን ቁልፍ የመቄዶንያ መሥራች ብኒያም በለጠ ተረክበው የምስጋና መልእክት አስተላልፈዋል።
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል 18 ዓመታቸው ስለመነኮሱ እግዚአብሔር የመቄዶንያ መሥራች ብንያም በለጠ የጠራቸው አባት መሆናቸውን እናምናለን። ስጦታቸውን የሚያጣጥሉ ኃይሎች መፈጠራቸው አሳዝኖናል ብለዋል።
ቀድሞም የቤት ኪራዩን ሜቄዶንያ ሲጠቀምበት የቆየ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ቤቱ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል 58ኛ መቄዶንያ ቅርንጫፍ እንዲባል ጠይቀዋል።
በመቄዶንያ ታሪክ ትልቁ ስጦታ ይህ ነው በማለት የመቄዶንያ መሥራቹ ብኒያም በለጠ ተናግረዋል።
በመቀጠልም የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች ስለስጦታው አርአያነት ያለው ነው በማለት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።
የመቄዶንያ አረጋውያንና አእምሮ ሕሙማን ማዕከል ተረጅዎችም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ አባታዊ ትምህርት የሰጡ ሲሆን ብፁዕነታቸው በሰጡት ትምህርት የትንሣኤው በኩር የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኔ ተማሩ በማለት ያስተማረውን ትምህርት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በተግባር አውለውታል ብለዋል።
ብፁዕነታቸው ራሳቸውን በመስጠት ትልቁን መሰናከል አልፈዋል ብለዋል። ዛሬ ያጣነው የሚሠራ እንጂ የሚያወራ አይደለም ሲሉ መልዕታቸውን አጠቃለዋል።
በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ኤልያስ የኖርዲክ ሀገራት እና የግሪክ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ የመጨረሻ ትምህርትና ጸሎት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።©Eotc tv.

መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሓዱ ኣምላክ ኣሜን!
ብፁዕ ኣቡነ ሳዊሮስ
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ስራ ኣስኪያጅ፤
ብፁዕ ኣቡነ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ፤
ብፁዕ ኣቡነ ሕርያቆስ
የኣዲስ ኣበባ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዓን ኣበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት፣
በኣጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ የተገኛችሁ በሙሉ፦
ማሕየዊት በምትሆን ሞቱ ሰማያውያንና ምድራውያንን ያስታረቀ፣ በቅድስት ትንሣኤውም የሙታንን ሕይወት በተስፋ ያለመለመ ጌታችን፣ ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንኳን ለዓመታዊው የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ ኣደረሰን ኣደረሳችሁ!
“እስመ ተዋለጠ እግዚአብሔር ዓለመ በክርስቶስ ኣናኅስዮ ኃጢኣቶሙ ወኢነጺሮ ጌጋዮሙ፤ ወረሰየ ላዕሌነ ቃለ ሥምረቱ፤ ወወሃበነ መልእክተ ሣህሉ፡- እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና በደላቸውን ኣይቈጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል ኣኖረ” (2ቆሮ. 5፥19)።
የእግዚአብሔርም ልጅ፣ የሰውም ልጅ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በሰብእነት ሲገለጽ ግልጽ የሆነ ዓላማና ግብ እንደነበረው ቅዱስ መጽሓፍ ይነግረናል፤ እሱም በሰማይም፣ በምድርም ያሉትን በሙሉ ማስታረቅ፣ ማገናኘትና ኣንድ ማድረግ ነበረ፤
ጌታችን ይህንን ሲያደርግ ሰማያውያኑንና ምድራውያኑን የለያየው ምክንያት በማስወገድ ነው፤ የመለያየቱ ምክንያት ክፉ ኅሊና ኣምጦ የወለደው በደልና እሱን ተከትሎ የተከሠተው ኃጢኣት ነበረ፤ በኃጢኣት ምክንያት የገባው ሞት ደግሞ የቅጣቱ ማሳያ ፍርድ ነበረ።
የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በፈጸሙት ስሕተት መነሻነት ምድርንና ምድራውያንን ለከባድ ቅጣትና መርገም የዳረገው ይህ መለያየት ለሰማያውያኑም ተርፎኣል፤
ምክንያቱም መለያየቱ በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰውና በሰው፣ በነፍስና በሥጋ ጭምር የጥል ግድግዳን ገንብቶ እስከ ክርስቶስ ዕለተ ስቅለት መዝለቁን በቅዱስ መጽሓፍ የምናውቀው ስለሆነ ማለት ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት!
ቀዳማዊና ዘላለማዊ የሆነው ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰብእናችንን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም የተገለጸው ሰማያውያንንና ምድራውያንን የለያየው የጥል ግድግዳን ለማፈራረስ ነው፤
ለመለያየት ምክንያት የሆነችውን ኃጢኣት በሰውነቱ በመቅጣት የሕግን ትእዛዝ ከፈጸመ በኋላ የዕርቁን ተግባር በወሳኝ መልኩ ኣከናውኖታል፤
በክርስቶስ ቤዛነት የሆነው ይህ ዕርቅ በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ የተወደደ ነበረና እሱ ራሱ በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ኣስታረቀ፤
ለዚህም ነው ተበዳይ እሱ፣ ቤዛዊ መሥዋዕት ሆኖ የቀረበው እሱ፣ ኣስታራቂ እሱ፣ ታራቂ እሱ ሆኖ የምናገኘው፤ ለሱ የሚሳነው ነገር የለምና ለኛ ግር የሚል ቢመስልም ለሱ ቀላል ነበረ።
በዚህ የዕርቅ ተግባር ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሰውና ሰው፣ ነፍስና ሥጋ ታርቀው በይፋ ተገናኙ፤ በኅብረትና በኣንድነትም መኖር ቻሉ፤ በቀኙ ለተሰቀለው ሽፍታ “ዛሬውኑ ከኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” የሚለው ቃለ ምሕረትና “ኣባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ ኣደራ እሰጣለሁ” የሚለው ቃለ ኣማሕፅኖ የዕርቁ፣ የግንኙነቱና የኣንድነቱ ማሳያ ኣስረጅ ናቸው።
ስቅለተ ክርስቶስ ነፍሶቻችን ወደ ግዞት ቤት ሳይሆን ወደ ገነት እንዲገቡ፣ የሚቀበላቸውም ራሱ እግዚአብሔር እንዲሆን ያስቻለ ታላቅ መለኮታዊ ፍጻሜ ነው፤
እኛ “ክርስቶስ መድኃኒታችን ነው፤ ኣድኖናል” ብለን በልበ ሙሉነት የምንመሰክረው፣ እሱም “ሰላሜን ሰጠኋችሁ” ብሎ የሚያረጋጋን በመሰቀሉ ይህንን ውጤት ስላስገኘልን ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት!
የድኅነታችንና የሰላማችን መሠረት የሆኑትን የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ለዓለም ማኅበረ ሰብ የማብሰርና የማሥረጽ ተግባር የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቍጥር ኣንድ ተልእኮ ነው፤
ነገረ ሞቱና ነገረ ትንሣኤው በኣስተውሎት፣ በጥልቀትና በተመሥጦ ስናስተምር በውስጡ የምናገኘው የዕርቅ፣ የሰላምና የኣንድነት ምስጢር ነው፤
እንደ እውነቱ ከሆነ እኛ የክርስቶስ መልእክተኞች እንደ ቃሉ ራሳችንን ክደን በሚጠበቀው መጠን ተልእኮኣችንን መወጣት ብንችል ኖሮ፣ ኣሁን በዓለማችን የተፈጠረው መለያየትና ግጭት ኣይኖርም ነበር፤
ችግሩን ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ባንችልም በእጅጉ መቀነስና ዓቅሙን ማዳከም እንችል ነበር፤ ነገር ግን ተልእኮኣችንን በኣግባቡ ኣለመወጣት ኣንድ ነገር ሆኖ የዓለሙ መሳሪያ ሆነን መገኘታችን “በዕንቅርት ላይ…” ሆኖ ይስተዋላል።
ይሁንና ኣሁንም ሕዝቡን ወደ ኣንድነት፣ ወደ ፍቅር፣ ወደ ሰላም፣ ወደ ዘላቂ የጋራ ጥቅምና ወደ ፈሪሐ እግዚአብሔር ማምጣት የጉባኤያችን ዓቢይ ተግባር ሊሆን ይገባል፤ እነዚህ ካሉ የምናጣውም ሆነ የሚያመልጠን የለምና ነው፤
ሃገርን በኃላፊነት ተረክባችሁ በላዕላዊ፣ በማእከላዊና በታሕታዊ መዋቅር የምትገኙ፣ እንደዚሁም ኣማራጭ ሓሳብ ኣለን ብላችሁ የምትንቀሳቀሱ ልኂቃነ ሃገር ፣ ሁላችሁም እግዚአብሔርን ከሚያውቅ፣ ከሚያመልክና ከሚፈራ ሕዝብ የተገኛችሁ ናችሁና በልባችሁ እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ድምፁንም ስሙ፤ የሱ ገንዘብ በሆኑ ፍጡራንም ኣትጨክኑ፤ ሰውን መያዝ የሚቻለው ኅሊናን በመርታት እንጂ በሌላ ኣይደለምና፣
የሕዝቡን ፍላጎትና የልብ ትርታ በሚገባ ኣዳምጡ፤ ሕዝቡ የሚፈልገው በኣንድነትና በእኩልነት መኖር፣ በሰላም ወጥቶ መግባት፣ ፍትሕን ማስፈን፣ ለኑሮው የሚበቃ ምጣኔ ሃብትን ማግኘት፣ የእምነት ነጻነትና እኩልነት መረጋገጥ የመሳሰሉት ናቸው።
ሕዝቡ እነዚህ ከተሟሉለት ተደመጠ ማለት ነው፤ ከተደመጠ ደግሞ እሱም በበኩሉ ያደምጣል፤ ይከተላልም፤
ስለሆነም ለሁሉም ልጆቻችንና ወገኖቻችን የምናስተላልፈው ወቅታዊ ጥሪ ሁሉንም ችግሮቻችን በሰላምና በሰላም ብቻ ለመፍታት ተባበሩ የሚል ነው፤ ከዚህ ውጭ የሚደረገው ኣማራጭ ሁሉ ለዘላቂ ሰላማችን ኣይበጅም እንላለን።
በመጨረሻም፦
በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ ኣምስተኛው ቀን የሚካሄደው ዓመታዊው የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተጀመረ መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለመላው ኢትዮጵያውያን እናበስራለን!!!
እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሓት ለእግዚአብሔር፤
አሜን!!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘኣኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ
ተክለ ሃይማኖት፤
ሚያዝያ 28 ቀን 2018 ዓ.ም
ኣዲስ ኣበባ – ኢትዮጵያ

የ፳፻ ፲ወ፰ ዓ/ም የርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የጸሎት መርሐ ግብር በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ተከናወነ

ሚያዚያ ፳፯ ቀን ፳፻፲ወ፰ ዓ/ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የ፳፻ ፲ወ፰ ዓ/ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የመክፈቻ ጸሎት መርሐ ግብር በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ተከናወነ።
በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በተከናወነው የጸሎት ሥነ-ሥርዓት ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆርስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣የጠቅላይ ቤተክህነት የየመምሪያውና የድርጅቶቹ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የግንቦት ፳፻ ፲ወ፰ ዓ/ም የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ በቋሚ ሲኖዶስ ተዘጋጅተው በአጀንዳ አሪቃቂ ኮሚቴ ታይተውና በምልዓተ ጉባኤ ተመርምረው በሚጸድቁ አጀንዳዎች ዙሪያ በጥልቀት በመወያየት ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን ያስተላልፋል።

የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም 76ኛ ዓመት ቅዳሴ ቤት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በድምቀት ተከበሮ ዋለ

ሚያዝያ 27 ቀን 2018 ዓ.ም
በየዓመቱ ሚያዚያ 27 ቀን በዓመት እንድ ግዜ ብቻ ታቦተ ሕጉ ወጥቶ በአውደ ምሕረት ምዕመናን የሚባርክበት ዕለት እና የኢትዮጵያ የነጻነት በዓል በምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም በድምቀት ተከብሮ ውሏል ።
በበዓሉ ላይም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የመንበረ ፓትርያርክ ዋና ስራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና ሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የበላይ ኃላፊ ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ የራያ አላማጣ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የማኅበራት ማደራጃ የቤተ መዛግብት ወመጻሕፍት መመሪያ ኃላፊ ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፣የመንበረ ፓትርያሪክ የመመሪያ የሥራ ኃላፊዎች ፣ረዳት ፕሮፌሰር ግርማ ባቱ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የኢኮኖሚ ጉዳዮች ዘርፍ ምክትል ስራ አስኪያጅ ፣ ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ የማኅበራዊ ጉዳዮች ምክትል ኃላፊ ፣ መልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሴ የአዲስ አበባ ዋና ስራ አስኪያጅ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመምሪያ የሥራ ኃላፊዎች ፣ መጋቤ ኅሩያን አባ ኤልያስ በልሁ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም ዋና አስተዳዳሪ ፣ የገዳማት አድባራት አስተዳዳሪዎች ፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ፣ በርካታ ምዕመናን ተገኝተዋል።
ምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦት ከኢየሩሳሌም ዴር ሱልጣን ገዳም ሀገር በጠላት ወረራ ውስጥ በሆነችበት ጊዜ በንጉሠ ነገሥት አፄ ኃይለ ሥላሴ ጥያቄ ለጸሎት ማድረሻ እና ለመማጸኛ ከጥቂት አገልጋዮችጋር በ 1929 ዓ ም ተጓዘ ።
በእንግሊዝ ለንደን ባት በተባለ ቦታ አርፎ እስከ1933 አገልግሎት እየሰጠ ቆይቷል በቀድሞ ስሙ ገነተ ልዑል ቤተ መንግስት የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለ2 ዓመታት ከቆየ በኃላ በቀድሞ ስሙ ቤተ ሳይዳ ወይም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሆስፒታል የአሁኑ የካቲት 12 ሆስፒታል ማረፊያ ተዘጋጅቶለት ከቆየ በኃላ ሚያዚያ 27 1942 ዓ.ም ወደ አሁኑ ያለበት ስፍራ በመምጣት በገዳምነት እያገለገለ ይገኛል።
በዚህ ቦታም ምስካየ ኅዙናን ተብሎ የተሰየመው በንጉሡ ሲሆን በቀድሞው ቤተ ሳይዳ ሆስፒታል በነበረበት ወቅት ነው የኃዘንተኞች ሁሉ መፅናኛ በመሆኑ ስያሜውን አግኝቷል ፣ ዴር ሱልጣን መድኃኔ ዓለም በኢየሩሳሌም በንጉሳውያን ገዳም በነበረበት ነው።
ስደተኛው መድኃኔ ዓለም መባሉ ደግሞ ኢትዮጵያ ነፃነቷን እስክታገኝ ለንጉሡና ለሰራዊቱ መፅናኛ በመሆን በስደት ከንጉሱ ጋር ከሀገር ሀገር መሰደድ ነው ።
በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ የድል ቀን እና የምስካ የኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቅዳሴ ቤት 76ኛ ዓመት በድምቀት ተከብሯል።
በበዓሉ ላይም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በበዓሉ የታደሙትንብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና የክብር እንግዶች እንዲሁም ምዕመናንን የእንኳን አደረሳችሁ በማለት የበዓሉን የአከባበር ሁኔታ እና የታቦቱን ታሪካ የገለፁ ሲሆን በመቀጠልም ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የስዊድን ግሪክ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ትምህርተ ወንጌል ቃለ ምዕዳን እና ቡራኬ በመስጠት የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።
©ም/ስ/ኀ/ዙ/መ/ገዳም ሚዲያ፤

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና ሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ለምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም የ76ኛ ዓመት ቅዳሴ ቤት እና በጀግኖች አባቶቻችን ለተገኘው 85ኛው የኢትዮጵያ የድል በዓል ያስተላለፉት መልዕክት

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን — በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን
አሰሮ ለሰይጣን — አግአዞ ለአዳም
ሰላም — እምይእዜሰ
ኮነ — ፍሥሐ ወሰላም
​”ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር”
“ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች ” መዝ. 68፡31
• ​ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤
• ​የጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመመሪያ ኃላፊዎች፤
• ​የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የመመሪያ ኃላፊዎች፤
• ​ክቡራን የገዳሙ አስተዳደር ቦርድ አባላት፤
• ​የገዳማት እና የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤
• ​ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እና የገዳሙ አበው መነኮሳት አኃው ዲያቆናት እንዲሁም የገዳሙ ተቋማት ልዩ ልዩ ሠራተኞች፤
• ​የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፤
• ​ከሩቅም ከቅርብም የመጣችሁ የመድኃኔዓለም ወዳጆች ምዕመናንና ምዕመናት፤
• ​እንዲሁም ሕፃናት በቅድሚያ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ።
​በድጋሚ ዛሬ ለምናከብረው ለምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም የ76ኛ ዓመት ቅዳሴ ቤት እና በጀግኖች አባቶቻችን ለተገኘው 85ኛው የኢትዮጵያ የድል በዓል እንኳን አደረሳችሁ።
• ​ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት
• ​ክቡራንና ክቡራት የበዓሉ ተካፋዮች
​በዛሬው ዕለት የምናከብረው በዓል ሁለት መልክ ያለው ድርብ በዓል ነው።
​አንደኛው በዚህ ታላቅ ገዳም የጌታችንና የአምላካችን የመድኃኔ ዓለምን ታቦተ ሕግ ከመንበረ ክብሩ አውጥተን ቅዳሴ ቤቱን በማሰብ የምናከብረው በዓል ሲሆን፤
​ሁለተኛው በኢትዮጵያውያን ካህናት፣ ምዕመናን እና በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ጸሎት እንዲሁም በኢትዮጵያውያን አርበኞች ተጋድሎ የተገኘው የድል በዓል ነው።
​ይህ የኢትዮጵያውያን ድል ይገኝ ዘንድ ጀግኖች አባቶቻችንን የረዳ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦተ ሕግ በመሆኑ ስለ ታቦተ ሕጉ እንዲሁም ስለ ገዳሙ ጥቂት ለማለት እንወዳለን።
​የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦተ ሕግ በዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና በንግሥት ጣይቱ መልካም ፈቃድ በመምህር ፈቃደ እግዚአ እንቁላላዊ አማካኝነት በ1895 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ። ከዚያም በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ላሉ ኢትዮጵያውያን ምዕመናን በዴር ሱልጣን ገዳም አገልግሎት መስጠት ጀመረ።
​የመድኃኔ ዓለም ታቦት አገልግሎት መስጠት የጀመረው ወደ ኢየሩሳሌም በሄደበት በ1895 ዓ.ም ሲሆን ታቦተ ሕጉ እስከ ዛሬ ድረስ የምዕመናን…
​ልመናና ጸሎት በመስማት፣ ያዘኑትን በማጽናናት፣ የተቸገሩትን በመርዳት መጠጊያ ለሌላቸው መጠጊያ በመሆን ለ123 ዓመታት አገልግሎቱን በመስጠት ላይ ይገኛል።
​የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦተ ሕግ ከ1895 ዓ.ም ጀምሮ በሦስት የተለያዩ ሀገሮች ላይ አገልግሎት ሰጥቷል።
​1ኛ. በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ለ34 ዓመታት ከኢትዮጵያውያን ምዕመናን ጋር፤
2ኛ. በእንግሊዝ ሀገር ለ4 ዓመታት ከጃንሆይ ጋር፤
3ኛ. በኢትዮጵያ በአሁኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቀድሞ ስሙ ገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት በአባ ኃይለ ማርያም እየታጠነ ለ2 ዓመታት፤ እንዲሁም የካቲት 12 ሆስፒታል በቀድሞ ስሙ ቤተ ሳይዳ ለ7 ዓመታት።
​አሁን ባለንበት የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለ76 ዓመታት፣ በአጠቃላይ እስከ ዛሬ ድረስ 123 ዓመታት ተገቢውን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል።
​የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦት ወደ ኢየሩሳሌም የሄደበት ዓላማ በዚያ ላሉ ምዕመናን መድኃኔ ዓለምን መማጸኛና መንፈሳዊ አገልግሎትን ማከናወኛ ይሆን ዘንድ ነበር።
​ነገር ግን ወራሪው ጠላት ፋሽስት ኢጣሊያ በ1928 ዓ.ም ኢትዮጵያን ተኝቶ ለመግዛት ወረራን ፈጽሞ በነበረበት ወቅት ግርማዊ ጃንሆይ ለተባበሩት መንግሥታት አቤቱታቸውን ለማሰማት ወደ እንግሊዝ ሀገር ተሰደዱ።
​እንግሊዝ ሀገር በስደት በነበሩበት ወቅት የኢትዮጵያ ጉዳይ በምድራዊ ዳኞች ፍትሕ ሊያገኝ ስላልቻለ ጥር 13 ቀን 1929 ዓ.ም ግርማዊነታቸው በኢየሩሳሌም ወደሚገኙት ብፁዕ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ በመጨረሻ የሚመራ ስማቸው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ እንዲህ የሚል መልዕክት ላኩ፦
​ሞአ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ
​ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ
​ይድረስ ለብፁዕ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር የኢትዮጵያን ነገር እስከሚያሳየን ድረስ በዚህ ስለምንቆይ ቤተሰቦቻችንም ሃይማኖታቸውን እንዳይዘነጉ አምላካችንን የምንማጸንበት ታቦት ያስፈልገናል።
​ስለዚህ አባ ሐናን መልዕክተኛ አድርገን ስለላክን ከመምህር ገሪማ ጋር ተነጋግራችሁ አንድ ታቦት እና ንዋያተ ቅዱሳት፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ከውሉን አገልጋዮች ጋር ላኩልን በማለት መልዕክታቸውን አደረሱ።
​መልዕክቱን የተቀበሉት ብፁዕ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ በወቅቱ የአገልጋይ እጥረት እንዳለ ገልጸው የመድኃኔ ዓለም ታቦትንና ንዋያተ ቅዱሳቱን በማሟላት ከአራት አገልጋይ መነኮሳት ጋር መልዕክተኛው አባ ሐናን መሪ በማድረግ ወደ እንግሊዝ ሸኝተዋል።
​ግርማዊ ጃንሆይም ከኢየሩሳሌም የመጣላቸውን የመድኃኔ ዓለም ታቦት የእንግሊዝ መንግሥት በሰጣቸው ባት በሚባል የአምልኮ ስፍራ ሚያዝያ 27 ቀን 1929 ዓ.ም ከኢየሩሳሌም በመጡት መነኮሳት እና በአባ ሐና አማካኝነት ከመላው ቤተሰባቸው ጋር ለሀገራቸው እና ስለ ኢትዮጵያውያን ሱባኤ ይዘው መድኃኔ ዓለምን መማጸን ጀመሩ።
​በወቅቱ ከሚጸልዩት ጸሎት መካከልም፦
​ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ሰዎች ምዕራፍ 8፥35 በጻፈው መልዕክት የሚገኘውን ኃይለ ቃል በመጠቀም ነበር።
​ቃሉም፦
​”ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይንስ ስደት ወይንስ ራብ ወይንስ ዕራቁትነት ወይንስ ፍርሃት ወይንስ ሰይፍ ነው?” የሚል ሲሆን
​ከሚዘምሩት መዝሙሮች መካከልም፦
“ኢትዮጵያ ሆይ በረከሸ ቀኝ ትርሳኝ” የሚል ይገኝበታል።
​ይህ ኃይለ ቃልና መዝሙር እስከ ዛሬ ድረስ በገዳሙ የሰርክ ጸሎት እየተጸለየ ይገኛል።
​ከ4 ዓመታት በኋላም በ1933 ዓ.ም የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የግርማዊነታቸው እና የኢትዮጵያውያን ጸሎት ተሰምቶ በመድኃኔ ዓለም ተራዳኢነት ጀግኖች ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን ጣሊያንን ድል አደረጉ።
​በዚህ ጊዜ ግርማዊነታቸው “መድኃኔ ዓለም ጸሎታችንን ሰምቶናል፣ በጠላቶቻችን ላይ ድል እንድንቀዳጅ አድርጎናል” አሉ።
​ስለዚህ ጸሎት እና ልመናችንን የሰማን የመድኃኔ ዓለምን ታቦት ይዘን ወደ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ መሄድ አለብን በማለት የመድኃኔ ዓለምን ታቦት እና ንዋያተ ቅዱሳት እንዲሁም አገልጋይ መነኮሳትን ከቤተሰቦቻቸው ጋር አንድ ላይ አድርገው በ1933 ሚያዝያ 27 ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል።
​በዚህ ዕለትም ግርማዊነታቸው ከመላው ኢትዮጵያውያን ጋር በአዲስ አበባ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ሰቅለው በመውለብለብ የድል በዓሉን አክብረዋል።
​ይህ የድል በዓል ዘንድሮ ለ85ኛ ጊዜ እየተከበረ ይገኛል።
​የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦት ከአገር ወደ አገር ሲንቀሳቀስ ያረፈባቸው ቦታዎች 5 ናቸው።
​እነሱም፦
• ​ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም
• ​ከኢየሩሳሌም ወደ እንግሊዝ
• ​ከእንግሊዝ ወደ ካርቱም
• ​ከካርቱም ወደ አሜድላ
• ​ከአሜድላ ወደ አዲስ አበባ መሆኑን ታሪክ ያስረዳል።
​የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ታቦት በሦስት ስሞች ይጠራል።
​1ኛ. ዴር ሱልጣን መድኃኔ ዓለም፦ ዴር ሱልጣን መባሉ በኢየሩሳሌም አገልግሎት ሲከናወንበት የነበረው ቦታ ዴር ሱልጣን በመሆኑና ትርጓሜውም የንጉሥ ገዳም ማለት ስለሆነ፤
2ኛ. ስደተኛው መድኃኔ ዓለም፦ ስደተኛ መባሉ ከጃንሆይ ጋር ከአገር አገር አብሮ በመሰደዱ፤
3ኛ. ምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም፦ ምስካየ ኅዙናን መባሉ የኅዙናን መመኪያ በመሆኑ ነው።
​ምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም የሚለውን ስያሜ ያገኘው የመድኃኔ ዓለም ታቦት በቤተ ሳይዳ ቆይቶ አሁን ያለበት ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በ1940 ሚያዝያ 27 በግርማዊነታቸው የመሠረት ድንጋይ ከተቀመጠ።
​በኋላ በ1942 ሚያዝያ 27 ተጠናቆ ታቦተ ሕጉ ወደ መቅደሱ በሚገባበት ወቅት ግርማዊነታቸው ምስካየ ኅዙናን የሚል ሥያሜ ሰጥተውታል።
ቅዳሴ ቤቱም ዘንድሮ ለ76ኛ ጊዜ እየተከበረ ይገኛል።
​ይህ የመድኃኔ ዓለም ታቦት እስከ ዛሬ ድረስ በአጠቃላይ ለ123 ዓመታት አገልግሎት ሰጥቷል በመስጠት ላይም ይገኛል።
​በአሁኑ ሰዓት ገዳሙን በበላይነት በመምራት ላይ የሚገኘው የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም አስተዳደር ቦርድ ቀደምት አባቶቻችን በገዳሙ ያስቀመጡትን ሥርዓት በማስጠበቅ በሁሉም መንፈሳዊ እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዘርፎች ምዕመናን በባለቤትነት ይገለገሉ ዘንድ ጥብቅ ክትትል እያደረገ ይገኛል።
​የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የመንፈሳዊ እና የዓለማዊ ትምህርትን በሚያከናውንባቸው ተቋማት ውስጥ የገዳሙ አስተዳደር ቦርድ በሚሰጠው መመሪያ መሠረት በመንፈሳዊ እና በዓለማዊ ትምህርት ለሀገር የሚጠቅሙ ትውልድን እያፈራ ይገኛል።
​ገዳሙ በመንፈሳዊው የትምህርት ዘርፍ፦
የንባብ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የመጻሕፍት ሐዲሳት፣ ብሉያት ተማሪዎችን እያስተማረና ለመምህርነት እያበቃ ለቤተ ክርስቲያን ተተኪ መምህራንን በማፍራት ላይ ይገኛል።
​እንዲሁም በተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲጠነክሩ፣ መስማት ለተሳናቸው በራሳቸው ቋንቋ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲማሩ ከፍተኛ ጥረት እያደረገ ይገኛል።
​በዓለማዊ ትምህርት ​የገዳሙ ዘመናዊ ትምህርት ቤት በበቁ አመራሮች እና የማስተማር ብቃታቸው በተረጋገጠ መምህራን ይመራ ዘንድ የገዳሙ አስተዳደር ቦርድ ግምገማ አድርጎ ተገቢውን አመራር በተገቢው ቦታ በመመደብ ከመዋዕለ ሕፃናት እስከ መሰናዶ ትምህርት ድረስ ትውልድን እያስተማረ ለሀገር ተተኪ ምሁራንን በማፍራት ላይ ነው።
​ከዚህ በፊት በገዳሙ ተሠርተው አገልግሎት ላይ የዋሉ የልማት ተቋማት የሆኑትን ባለ ሰባት ፎቅ ሕንፃ፣ መካከለኛ ክሊኒክ እና የተከራዩ ክፍሎችን በማጠናከር ለምዕመናን አስፈላጊውን አገልግሎት እንዲሰጡ በማድረግ ላይ ይገኛል።
​ከዚህ በተጨማሪ የገዳሙ አስተዳደር ቦርድ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም ከተመሠረተበት ትውልድን የማፍራት ዓላማ አንጻር ያሉት የልማት ተቋማት በቂ ባለመሆናቸው ለገዳሙ እና ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች ርስት የሚሆን ከመሬት ሥር ባለ ሁለት ወለል፣ ከመሬት በላይ ባለ አሥራ አንድ (11) ወለል ግዙፍ ሕንፃ በማስገንባት ላይ ይገኛል።
​ይህን ግዙፍ ሕንፃ ለማስገንባት የሚያስፈልገው የገንዘብ መጠን ከስምንት መቶ ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚፈጅ ባለሙያዎች ገልጸዋል።
​በመሆኑም የቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብት ምዕመናን ናቸውና ሕንፃው ከተጀመረበት ጊዜ አንሥቶ እስከ አሁን ድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ምዕመናን በማስተባበር እና የገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ በማዘጋጀት በተገኘው ገንዘብ ከመሬት ሥር ያለው ሁለት ወለል አርማታ ተሞልቶ ከመሬት በላይ አራተኛ ፎቅ በመገንባት ላይ ይገኛል።
​የተወደዳችሁ ምዕመናንና ምዕመናት ይህ ታሪካዊ ገዳም እያስገነባ ያለው ግዙፍ ሕንፃ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት የሚችለው በሁላችሁም ድጋፍ ነው። ሕንፃው እስኪጠናቀቅ ድረስ ገንዘብ ያላችሁ በገንዘብ፣ ጉልበት ያላችሁ በጉልበት፣ ሐሳብ ያላችሁ በሐሳብ ድጋፋችሁን እንድታደርጉ በመድኃኔ ዓለም ስም እንጠይቃችኋለን።
• ​ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት
• ​ክቡራንና ክቡራት የመድኃኔ ዓለም ወዳጆች
​በገዳሙና የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች እንዳሉ ሆነው ወደ ዛሬው ታሪካዊ በዓላችን ስንመለስ
​በመንፈስ ቅዱስ በመቃኘት ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት፦
​ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር
​ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች
​ብሎ በተናገረው መሠረት ግርማዊነታቸውና ጀግኖች ኢትዮጵያውያን ሳይለያዩ በአንድነት የጸሎት እጆቻቸውን ወደ መድኃኔ ዓለም ዘርግተው በመጸለይ ወራሪው ፋሽስት ጣሊያንን ድል አድርገዋል።
​የጥንት አባቶቻችን ከባሕር ማዶ ተሻግሮ የመጣ የሚታይ ጠላትን በኃይለ እግዚአብሔር ድል አድርገው የኢትዮጵያን ዳር ድንበር በማስከበር ባሕልና ቋንቋችን እንዲሁም ሃይማኖታችን ሳይበረዝ ለእኛ እንዲደርስ አድርገዋል። በመሆኑም በበዓሉ እግዚአብሔር በረድኤቱ ቤተ ክርስቲያናችንን እና ሀገራችንን የጠበቀበትን መንገድ እያሰብን በምስጋና የምናከብረው ነው።
​ስለዚህ የተወደዳችሁ ምዕመናን አባቶቻችን ጠብቀው ያቆዩልንን ባሕልና ታሪክ ጠብቀን ለሚመጣው ትውልድ ማስተላለፍ ይገባናል።
​በዓሉን በዓለ ሰላም፣ በዓለ ፍሥሐ ያድርግልን።
​መድኃኔ ዓለም አምላካችን ሀገራችን ኢትዮጵያን ይጠብቅልን
ሕዝባችንን ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ይሰውርልን
​አሜን!!!
​ሚያዝያ 27/08/2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
© EOTC tv

በምሁር ኢየሱስ ገዳም የአዲሱን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ቡራኬን ተከትሎ ሲከበር የነበረው በዓል ተጠናቀቀ

ሚያዚያ ፳፭ ቀን ፳፻፲ወ፰ ዓ.ም
በታላቁ አባት በአቡነ ዜና ማርቆስ የተገደመው የምሁር ኢየሱስ ገዳም ሚያዚያ ፳፬ ቀን በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፀሎተ ቡራኬ ታቦታቱ ከነበሩበት መቃኞ ቤተ ክርስቲያን ወጥተው ወደ አዲሱ ሕንጻ ቤተ ክርስታያን መግባታቸው ይታወሳል።በዓሉ በዛሬው ዕለትም ቀጥሎ የዋለ ሲሆን በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ታቦታቱ ታጅበው ወጥተው በልዩ ድምቀት እየተከበረ ይገኛል።
በዕለቱ የሕንጻ ሥራውን አስመልክቶ በገዳሙ አበመኔት በመምህር አባ ዘኢየሱስ ቀርቧል።
በሪፖርቱ መነሻም የምሁር ኢየሱስ ገዳም አንጋፋ መሆኑ የተጠቀሰ ሲሆን ምስረታውም ከ840 ዓ.ም በፊት በ13 ክ.ዘመን እንደተገደመ እና የገዳሙ መስራች ጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስ 3 ጊዜ ሐዋርያዊ ጉዟቸውን ወደ ገዳሙ ማድረጋቸው ተገልጧል።
በወቅቱ ሕዝቡ እግዚያብሔርን ከማምለክ ወደ ባዕድ አምልኮ ተሻግሮ የነበር ቢሆንም ጻድቁ ሕዝቡን አስተምረው ወደ እግዚአብሔር መመለሳቸው ተወስቷል።
ጻድቁ ለሁለተኛ ዙር ሲመጡም 156 አብያተ ክርስቲያናትን በአካባቢው ማሠራታቸውም ነው የተገለፀው።
ከገዳሙ ታሪክ ጋር ተያይዞም ጻድቁ በዘመናቸው የሠሩት ዘርፈ ብዙ ገድልና ታሪካቸው ታውሷል።
በዘመኑም ገዳሙ በኑቡረ ዕድ ይተዳደር እንደነበር እና እንደ አክሱምና ጎንደር የትምህርት ተቋም ሆኖ ለዘመናት የቆየ መሆኑም ተጠቅሷል።በዘመናት ሂደት በዋናነትም ከመሬት ላራሹ ጀምሮ ገዳሙ እንደተዳከመም ያነሱት የገዳሙ አበመኔት አባ ዘኢየሱስ ከ1988 ጀምሮም በድጋሚ ገዳሙ በብፁዕ አቡነ መልከ ጼድቅ ካልዐይ ጥረት ማንሰራራቱን ጠቅሰዋል።
ዛሬ ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያንም 17 ዓመት መፍጀቱ በሪፖርቱ የተጠቀሰ ሲሆን ይህም ሥራ የተጀመረው በብፁዕነታቸው በ2000 ሲሆን በ2002 ብፁዕነታቸው ማረፋቸው ተገልጿል።
በወቅቱ በወልቂጤ በአዲስ አበባ በሰበታ የጀመሯቸው ትምህርት ቤት እና የሕንጻ ሥራ የነበር በመሆኑ ከጀመሯቸው የልማት ሥራዎች ጋር ይህም የሕንጻ ሥራ ለፍጻሜ መብቃቱ ተገልጿል።
የሕንጻ ሥራውን አስመልክቶ የፈጀው የገንዘብ መጠን በሪፖርት ያልቀረበ ሲሆን ይህንንም አስመልክቶ አባ ዘኢየሱስ በምክንያትነት ያቀረቡት ከሕሊና ጀምሮ ብዙ መዋዕለ ነዋይ የፈሰሰበት በመሆኑ ገንዘብ አይተምነውም ነው ያሉት።
በተጨማሪም ለሕንጻ ሥራው ከሳንቲም ጀምሮ ከፍተኛውን ብር የሰጡ በእግዚአብሔር ፊት እኩል በመሆናቸው ለይቶ ማመስገን እንደማይቻል ነው በምክንያትነት የተጠቀሰው።
ከዚህም የተነሳ በሌሎች አብያተ ክርስቲያን እንደተለመደው የምስጋናና የእውቅና ሰርተፊኬት ያልተከወነ ሲሆን ከዚያ ይልቅ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጸሎተ ማርየም እንዲጸለይላቸው ተደርጓል።
በገዳሙ የበዓላትን ቀንን ጨምሮ የገንዘብ አሰባሰብ የማይደረግ መሆኑም ተገልጿል።
ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ በገዳሙ መነኮሳት እና መነኮሳይት የተሳለ ኢትዮጵያዊ መልክ ባላቸው ቅዱሳን ያጌጠ ሲሆን አንዳንዶቹም ማብራሪያ የሚሹ በመሆናቸው ወደፊቱ በመጽሔት ማብራሪያ እንደሚቀርብበት ተነግሯል።
በዕለቱም ብፁዓን አባቶች ትምህርተ ምዕዳን የሰጡ ሲሆን የብፁዕ አቡነ መልከ ጼድቅ ካልዓይ በሕይወት በነበሩበት ወቅት ከብፁዓን አባቶች ጋር የነበራቸውም ቆይታ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ በትዝታ የዳሰሱበት ነበር።
ትላንት ሚያዚያ ፳፬ በነበረው መርሐ ግብርም ለብፁዕነታቸው የተሠራው መታሰቢያ ሀውልትና ቤተ መዘክር መመረቁ ይታወሳል።
በዕለቱ በብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ቅኔ የቀረበ ሲሆን በደብሩ ካህናትም ወረብ ቀርቧል።
በበዓሉ ላይ ከአዲስ አበባና ከወረዳው የመጡ በርካታ ምዕመናን ፣ የሙር አክሊል ወረዳ አስተዳዳር አቶ ብስራት ገብሩ እና ሌሎችም የመንግሥት ኃላፊዎች፣የእንድብር ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ተገኝተዋል።
በበዓሉ ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ ለካህናት የቅዳሴ አልባሳትም በስጦታ አበርክተዋል።
በመጨረሻም ለብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ለመምሪያ ኃላፊዎች እና ለገዳሙ አበመኔት ለመምህር አባ ዘኢየሱስ የሽልማት መርሐ ግብር ተከናውኖ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።©E.o.t.c.tv.

ታሪካዊው የምሁር ኢየሱስ ገዳም አዲሱ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤት ተከበረ

ሚያዚያ ፳፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም
የምሁር ኢየሱስ ገዳም በጉራጌ ዞን፣ በምሁር አክሊል ወረዳ የሚገኝ ከአዲስ አበባ በ207 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን ጥንታዊና ታሪካዊ ገዳም ነው። ገዳሙ የተመሰረተው በ14ኛው ክፍለ ዘመን በታላቁ አባት በአቡነ ዜና ማርቆስ እንደሆነ የገዳሙ ታሪክ ይነግረናል።
ገዳሙ የከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ማዕከል በመሆን፣ጥንታዊና ብርቅዬ የብራና መጻሕፍትና ንዋያተ ቅድሳትን ጠብቆ በማቆየት፣እንዲሁም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ጉልህ ስፍራ ያላቸው ሊቃውንትን በማፍራት ይታወቃል።በተለይም በውስጡ የሚገኘውና እጅግ ተአምረኛ እንደሆነ የሚነገረው “የምሁር ኢየሱስ” ስዕለ አድኖ ለብዙዎች የፈውስና የበረከት ምንጭ ሆኖ ቆይቷል።
ገዳሙ በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ውስጥ ስመ ጥር የሆነ የጉባኤ ቤት መገኛም ነው። በተለይም በቅኔ፣ በዜማና በመጻሕፍት ትርጓሜ ጥልቅ እውቀት ያላቸውን ሊቃውንት በማፍራት፣በመላው ኢትዮጵያ ለሚገኙ አድባራትና ገዳማት ባለ ውለታም ነው።
ገዳሙ ከመንፈሳዊ ሥራው ባሻገር ለኅበረተሰቡ አገልግሎቶች የሚውሉ በሐዋርያት ከተማ ውስጥ የመዋዕለ-ሕጻናት ትምህርት ቤት፣ የእንግዳ መቀበያና ማረፍያ ቤት፣ በገዳሙ ግቢ ውስጥ ከ1ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ት/ቤት፣ በወልቂጤ ከተማ ደግሞ ከመዋዕለ-ሕጻናት እስከ 10ኛ ክፍል ባለሶስት ፎቅ ሕንጻ ት/ቤት አስገንብቶ በማስተማር የአካባቢውን ህብረተሰብ ተጠቃሚ እያደረገ ነው፡፡
በገዳሙ የተለያዩ ክብረ በዓላት የሚከበሩ ሲሆን በዋናነት ታህሳስ ሶስት የአቡነ ዜናማርቆስ የእረፍት ቀን መታሰቢያ፣አብይ ፆም አጋማሽ(ደብረዘይት) ልዩ የበገና ምሽት፣ በግንቦት ወር ውስጥ አብይ ፆም በተፈታ አርባኛው ቀን(የእርገት በዓል) ሲሆኑ በእነዚህ በዓላት ወቅት ቁጥሩ በዛ ያለ ከተለያዩ የአካባቢው፣ የሃገሪቱ ክፍሎች እና ከሃገር ውጪ በሚመጡ ቱሪስቶች በድምቀት ይከበራል።
በዛሬው ዕለት ደግሞ ይህንን ታሪካዊ ገዳም ከነበረበት የቆየ ህንጻ ቤተ ክርስቲያን ወደ ዘመናዊና ሰፊ ቤተ ክርስቲያን ለመቀየር በርካታ ምእመናን፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚኖሩ የገዳሙ ልጆችና በጎ አድራጊዎች በገንዘባቸው፣ በጉልበታቸውና በዕውቀታቸው ደክመዋል። ዛሬ ሚያዚያ 24 ቀንም ይህ ድካም ፍሬ አፍርቶ የገዳሙ አዲሱ ቤተ ክርስቲያን የቅዳሴ ቤት (ምረቃ) በታላቅ ድምቀት እየተከበረ ይገኛል።
በዕለቱ በተለያየ አልባሳት ከደመቁ ካህናትና ሰንበት ተማሪዎች በተጨማሪ ከገዳሙ አቅራቢያ ከሚገኘው ከሃዋርያት ከተማ ጀምሮ በባንዲራ የተዋበ አካባቢ፣ የሚጥለውን ዝናብና ንፋስ ተቋቁመው ገዳሙ ድረስ በተለያዩ መኪኖች ያጀቡ የዞኑ ፖሊሶች፣ ሞተር ሳይክሎችና ባጃጆች እንዲሁም በየራሳቸው ባህልና ወግ የሚዘምሩ ነዋሪዎችን በዓሉን ልዩ ድምቀት ሰጥተውት ውለዋል።
በክብረ በዓሉ ላይ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣የገዳማት አስተዳዳሪዎች ፣የገዳሙ መነኮሳትና አባቶች፣ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣እንዲሁም በሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን በስፍራው ተገኝተው ይህንን ታሪካዊ በዓል በዝማሬና በደስታ እያጀቡት ይገኛል።
በተጨማሪም የብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ ካልኣይ የመታሰቢያ ሐውልት እና ቤተ መዘክር በገዳሙ ግቢ ተመርቋል።
መርሐ ግብሩ በነገው ዕለትም የሚቀጥል ሲሆን ስርዓተ ቅዳሴ ተከውኖ ታቦታቱ ወጥተው ሕዝቡን ይባርካሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት
©EOTC tv

በሸገር ሀገረ ስብከት የኮዬ ገላን ክፍለ ከተማ ደንጎራ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ሕንጻ የቤተክርስቲያን በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ ቅዳሴ ቤቱ ከበረ

ሚያዚያ 24 ቀን 2018 ዓ.ም
ሚያዝያ 24 ቀን 2018 ዓም በተካሄደው የሕንጻ ቤተክርስቲያን ምርቃት ሥነ ሥርዐት ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንደተናገሩት “እንኳን ደስ አላችሁ፣ ስትደክሙበት ለነበረው ሥራችሁ ለፍጻሜ በቅቷል።” ብለዋል። ብፁዕነታቸው አክለውም “የድካማችሁን ፍሬና የሥራችንን ውጤት ለማየት ያበቃን አምላካችን እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው።” ሲሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
ብፁዕ አቡነ ሚካኤል የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሉቀ ጳጳስ ባስተላለፉት መልእክት ቤተክርስቲያን የሚሠራ የተፈቀደለት ነው። እናንተ ተፈቅዶላችሁ ቤተክርስቲያን ስለ ሠራችሁ እንኳን ደስ አላችሁ። ብለዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ በርናባስ የዋግህምራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ መልአከ ኃይል አባ አፈወርቅ ዮሐንስ የመልካ ኖኖ፣ጉጂ ገፈርሳ ክፍለ ከተማ ኃላፊ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የለሚ ኩራ ሥራ አስኪያጅ፣ ሊቀ ልሣናት በዳሳ ቶላ የክፍለ ከተማው ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የአጥቢያው ምእመናንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።©Eotc tv.