በምሁር ኢየሱስ ገዳም የአዲሱን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ቡራኬን ተከትሎ ሲከበር የነበረው በዓል ተጠናቀቀ
ሚያዚያ ፳፭ ቀን ፳፻፲ወ፰ ዓ.ም
በታላቁ አባት በአቡነ ዜና ማርቆስ የተገደመው የምሁር ኢየሱስ ገዳም ሚያዚያ ፳፬ ቀን በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፀሎተ ቡራኬ ታቦታቱ ከነበሩበት መቃኞ ቤተ ክርስቲያን ወጥተው ወደ አዲሱ ሕንጻ ቤተ ክርስታያን መግባታቸው ይታወሳል።በዓሉ በዛሬው ዕለትም ቀጥሎ የዋለ ሲሆን በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ታቦታቱ ታጅበው ወጥተው በልዩ ድምቀት እየተከበረ ይገኛል።
በዕለቱ የሕንጻ ሥራውን አስመልክቶ በገዳሙ አበመኔት በመምህር አባ ዘኢየሱስ ቀርቧል።
በሪፖርቱ መነሻም የምሁር ኢየሱስ ገዳም አንጋፋ መሆኑ የተጠቀሰ ሲሆን ምስረታውም ከ840 ዓ.ም በፊት በ13 ክ.ዘመን እንደተገደመ እና የገዳሙ መስራች ጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስ 3 ጊዜ ሐዋርያዊ ጉዟቸውን ወደ ገዳሙ ማድረጋቸው ተገልጧል።
በወቅቱ ሕዝቡ እግዚያብሔርን ከማምለክ ወደ ባዕድ አምልኮ ተሻግሮ የነበር ቢሆንም ጻድቁ ሕዝቡን አስተምረው ወደ እግዚአብሔር መመለሳቸው ተወስቷል።
ጻድቁ ለሁለተኛ ዙር ሲመጡም 156 አብያተ ክርስቲያናትን በአካባቢው ማሠራታቸውም ነው የተገለፀው።
ከገዳሙ ታሪክ ጋር ተያይዞም ጻድቁ በዘመናቸው የሠሩት ዘርፈ ብዙ ገድልና ታሪካቸው ታውሷል።
በዘመኑም ገዳሙ በኑቡረ ዕድ ይተዳደር እንደነበር እና እንደ አክሱምና ጎንደር የትምህርት ተቋም ሆኖ ለዘመናት የቆየ መሆኑም ተጠቅሷል።በዘመናት ሂደት በዋናነትም ከመሬት ላራሹ ጀምሮ ገዳሙ እንደተዳከመም ያነሱት የገዳሙ አበመኔት አባ ዘኢየሱስ ከ1988 ጀምሮም በድጋሚ ገዳሙ በብፁዕ አቡነ መልከ ጼድቅ ካልዐይ ጥረት ማንሰራራቱን ጠቅሰዋል።
ዛሬ ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያንም 17 ዓመት መፍጀቱ በሪፖርቱ የተጠቀሰ ሲሆን ይህም ሥራ የተጀመረው በብፁዕነታቸው በ2000 ሲሆን በ2002 ብፁዕነታቸው ማረፋቸው ተገልጿል።
በወቅቱ በወልቂጤ በአዲስ አበባ በሰበታ የጀመሯቸው ትምህርት ቤት እና የሕንጻ ሥራ የነበር በመሆኑ ከጀመሯቸው የልማት ሥራዎች ጋር ይህም የሕንጻ ሥራ ለፍጻሜ መብቃቱ ተገልጿል።
የሕንጻ ሥራውን አስመልክቶ የፈጀው የገንዘብ መጠን በሪፖርት ያልቀረበ ሲሆን ይህንንም አስመልክቶ አባ ዘኢየሱስ በምክንያትነት ያቀረቡት ከሕሊና ጀምሮ ብዙ መዋዕለ ነዋይ የፈሰሰበት በመሆኑ ገንዘብ አይተምነውም ነው ያሉት።
በተጨማሪም ለሕንጻ ሥራው ከሳንቲም ጀምሮ ከፍተኛውን ብር የሰጡ በእግዚአብሔር ፊት እኩል በመሆናቸው ለይቶ ማመስገን እንደማይቻል ነው በምክንያትነት የተጠቀሰው።
ከዚህም የተነሳ በሌሎች አብያተ ክርስቲያን እንደተለመደው የምስጋናና የእውቅና ሰርተፊኬት ያልተከወነ ሲሆን ከዚያ ይልቅ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጸሎተ ማርየም እንዲጸለይላቸው ተደርጓል።
በገዳሙ የበዓላትን ቀንን ጨምሮ የገንዘብ አሰባሰብ የማይደረግ መሆኑም ተገልጿል።
ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ በገዳሙ መነኮሳት እና መነኮሳይት የተሳለ ኢትዮጵያዊ መልክ ባላቸው ቅዱሳን ያጌጠ ሲሆን አንዳንዶቹም ማብራሪያ የሚሹ በመሆናቸው ወደፊቱ በመጽሔት ማብራሪያ እንደሚቀርብበት ተነግሯል።
በዕለቱም ብፁዓን አባቶች ትምህርተ ምዕዳን የሰጡ ሲሆን የብፁዕ አቡነ መልከ ጼድቅ ካልዓይ በሕይወት በነበሩበት ወቅት ከብፁዓን አባቶች ጋር የነበራቸውም ቆይታ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ በትዝታ የዳሰሱበት ነበር።
ትላንት ሚያዚያ ፳፬ በነበረው መርሐ ግብርም ለብፁዕነታቸው የተሠራው መታሰቢያ ሀውልትና ቤተ መዘክር መመረቁ ይታወሳል።
በዕለቱ በብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ቅኔ የቀረበ ሲሆን በደብሩ ካህናትም ወረብ ቀርቧል።
በበዓሉ ላይ ከአዲስ አበባና ከወረዳው የመጡ በርካታ ምዕመናን ፣ የሙር አክሊል ወረዳ አስተዳዳር አቶ ብስራት ገብሩ እና ሌሎችም የመንግሥት ኃላፊዎች፣የእንድብር ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ተገኝተዋል።
በበዓሉ ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ ለካህናት የቅዳሴ አልባሳትም በስጦታ አበርክተዋል።
በመጨረሻም ለብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ለመምሪያ ኃላፊዎች እና ለገዳሙ አበመኔት ለመምህር አባ ዘኢየሱስ የሽልማት መርሐ ግብር ተከናውኖ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።©E.o.t.c.tv.