በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የሚመራው የቤተክርስቲያን ልዑክ ዓመታዊውን የቅዱስ ገብርኤልን በዓል በቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱሰ ገብርኤል ገዳም አክብሮ በሰላም ተመልሷል።

ሐምሌ 20 ቀን 2018 ዓ.ም ድሬዳዋ -ኢትዮጵያ
በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ዓመታዊውን የቅዱስ ገብርኤልን በዓል በደማቅ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት በማክበር በሰላም ወደ መንበረ ፓትርያርክ ተመልሷል።
ሁለቱ ብፁዓን አባቶች በቆይታቸው በድሬዳዋ ሳባ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የተገነባውን ሁለገብ ሕንጻን የመረቁ ሲሆን የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ጽሕፈት ቤት እድሳት ሥራንና የአዳሰፈራሽ ግንባታ ሥራንን እንዲሁም በሀገረ ስብከቱ ወጪ በመገንባት ላይ ያሉ የልማት ሥራዎችን ተመልክተዋል።
ከዚህ በተጨማሪም የድሬዳዋ መልካጀብዱ አቡነ አረጋዊና ቅድስት አርሴማ ገዳምን የጎበኙ ሲሆን በገዳሙ የሚኖሩ እጓለማውታ ሕጻናትንም ባርከዋል።በቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ዓመታዊውን የቅዱስ ገብርኤል በዓልን በደማቅ መንፈሳዊ ሥነሥርዓት ያከበሩት ብፁዓን አባቶቹ በድሬዳዋ ከተማ የሚገኙ የተለያዩ ትውልድ ተኮር የልማት ሥራዎችንም ጎብኝተዋል።
በብፁዓን አባትች የሚመራው ልዑክ ዛሬ ከቀትር በኋላ ከድሬዳዋ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲነሳ ክቡር አቶ ሀርቢ ቡህ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ፣ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎች አሸኛኘት አድርገውለታል።

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በኢትዮጵያ የታላቋ ብሪታንያ አምባሳደር እና በአፍሪካ ኅብረት የቋሚ መልእክተኛ ክቡር ዳረን ዌልችን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

ሐምሌ 20 ቀን 2018 ዓ.ም
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤ በኢትዮጵያ የታላቋ ብሪታንያ አምባሳደር እና በአፍሪካ ኅብረት የቋሚ መልእክተኛ ክቡር ዳረን ዌልችን
(HE Darren Welch | UK Ambassador to Ethiopia & Permanent Representative to the African Union) በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
አምባሳደር ዳረን ዌልች ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር ያደረጉትን ውይይት አስመልክተው ለጣቢያችን ለኢኦተቤ ቴቪ (EOTCTV) በሰጡት አስተያየት፤ በኢትዮጵያ እና በእንግሊዝ መካከል ከጥንት ጀምሮ፣ በኋላም ዘመናዊ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ከተመሠረተበት ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት አንስቶ ለዘመናት የዘለቀ ጠንካራ ታሪክ እንዳለ አስታውሰዋል።
አክለውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበርካታ ጥንታዊ ታሪኮችና ቅርሶች ባለቤት፣ እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ ልዩ ገጽታና ትልቅ ቦታ ያላት የክርስቲያን መድረክ መሆኗን ገልጸዋል።
ቤተ ክርስቲያኗ ለሀገሪቱ ሰላም፣ ታሪክ እና ማህበረሰብ የምታበረክተውን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያከብሩ የጠቀሱት አምባሳደሩ፤ ኢትዮጵያ የተለያዩ ሃይማኖቶች በሰላም አብረው የሚኖሩባት ድንቅ የህብረት አርአያ መሆኗን ጠቁመዋል ።
በተጨማሪም የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት በቀጣይ ለአብሮነት እና ዘላቂ ሰላም ለማስፈን ከነበረው በበለጠ አጠናክረው እንደሚሰሩ አክለዋል ።
በመጨረሻም በኢትዮጵያ በተለያዩ ወቅቶች የሚስተዋሉ የሰላም እጦት እና የኢኮኖሚ አለመረጋጋቶችን ለመቅረፍ ከቤተ ክርስቲያኗ ጎን በመሆን ለጋራ ሰላም እና ለአብሮነት ተባብረው እንደሚሠሩ በመግለጽ፤ ለዚህም ሁሉም አካል የድርሻውን ኃላፊነት ሊወስድ እንደሚገባ አሳስበዋል።©Eotc tv

“ለቅኖች ምስጋና ይገባል። “መዝ 32፥1

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በዓመት ሁለት ጊዜ ማለትም በታኅሣሥ እና በሐምሌ 19 ቀናት የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ለማክበር ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ወደ ቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የሚጓዙ መሆኑ ይታወቃል።
ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በዓመት ሁለት ጊዜ በሚያደርጉት በዚህ ሐዋርያዊ ጉዞ በድሬዳዋ ከተማ የሚደረግላቸው አቀባበል እጅግ ደማቅ ሲሆን በተለይም ከቅርብ አመታት ወዲህ በክቡር ከንቲባ ከድር ጁዋርና በሥራ ባልደረቦቻቸው እንዲሁም በከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ ኮሚሽን በኩል የሚደረገው አቀባበል እጅጉን ያማረና የቤተክርስቲያ
ናችንን ክብር የገለጠ መህኑም የአደባባይ ምስጢር ነው።
የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር እንደተለመደው ሁሉ የ2018 ዓ.ም የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ለማክበር በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት
ሊቀ ጳጳስ የሚመራ የቤተክርስቲያን ልዑክ ወደ ድሬዳዋ ከተማ በተጓዘበት ጊዜ አቶ ሀርቢ ቡህ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የሥራ ባልደረቦቻቸው፣ በፖሊስ ማርሽ ባንድና በፈረሰኞች የታጀበ ደማቅ አቀባበል ተደርጎለታል።
ለዚህም ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፣ለፌዴራል ፖሊስ፣
ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ ኮሚሽን፣ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ትራፊክ ፖሊሶች፣ቅድስት ቤተክርስቲያንን በማክበር ላደረጋችሁት እጅግ ደማቅ አቀባበልና አሸኛኘት ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ከፍ ያለ ምስጋናዋን ታቀርባለች።እግዚአብሔር አምላክ ለሥራችሁ ስኬትን፣
ለከተማችሁ እድገትን፣ለሀገራችን ሰላምን እንዲሰጥ የዘወትር ጸሎቷ መሆኑን ለመግለጽ ትወዳለች።
በአጠቃላይ የሐምሌ 2018 ዓ.ም የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ባከበርንበት ጊዜየፌዴራል፣ የድሬዳዋና የምሥራቅ ሐረርጌ ፖሊስ አመራሮችና አባላት እንዲሁም ልዩልዩ የጸጥታ ተቋማት አንድነት በመፍጠር ሕዝበ ክርስቲያኑ በዓሉን ያለምንም የጸጥታ ችግር በሰላም እንዲያከብርና ወደ መጣበት እንዲመለስ በማድረግ፤በአጠቃላይ በዓላችን በሰላም ተከብሮ ይውል ዘንድ ላደረጋችሁት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ቅድስት ቤተክርስቲያን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለች።
የኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን
ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
ሐምሌ 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በሀዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም በታላቅ ድምቀት ተከበረ።

ሐምሌ 19/2018 ዓ.ም ሀዋሳ – ኢትዮጵያ
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ሕፃኑን ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ያዳነበትን ዓመታዊ ክብረ በዓል የሚዘክረው የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በዓለ ንግሥ በሀዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በአባቶች፣ በመንግሥት ኃላፊዎችና ከመላው ኢትዮጵያ በተሰበሰቡ በርካታ ምዕመናን በታላቅ ድምቀት ተከብሯል።
በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የሲዳማ ሀገረ ስብከትና የሀዋሳ ታቦር ፍኖተ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ጥበባት አባ ዘሚካኤል መርጊያ፣ መልአከ ሕይወት ቆሞስ አባ ወልደጊዮርጊስ ታዬ፣ መጋቤ ሥርዓት ቀሲስ ዳንኤል ጌታቸው፣ መልአከ መንክራት ቆሞስ አባ ገሪማ፣ የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ፣ የመንግሥት አመራሮች፣ የገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንና በርካታ ምዕመናን ተገኝተዋል።
ክብረ በዓሉ ከዋዜማው ጀምሮ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ስብሐተ እግዚአብሔር በድምቀት ተከናውኖ፣ በማግስቱ የቅዳሴ ሥርዓት በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መሪነት ተፈጽሟል። በዚሁ ወቅት መጋቤ ሐዲስ መምህር ወልደ ትንሣኤ የአዲስ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩኒቨርሲቲ የሐዲስ ኪዳን መምህር ቃለ እግዚአብሔር አስተምረው፣ ታቦታቱም በዝማሬና በእልልታ ታጅበው የዑደት ሥርዓት ተከናውኗል።
በመቀጠል የገዳሙ ሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያንና ሊቃውንት ለበዓሉ የሚመጥን ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል።
የሲዳማ ሀገረ ስብከት የሲዳምኛ ትርጉም ክፍል ኃላፊ መልአከ ሰላም ቀሲስ ታረቀኝ እንግዳ በበኩላቸው ሀገረ ስብከቱ መንፈሳዊ አገልግሎትን በሲዳምኛ ቋንቋ ተደራሽ ለማድረግ የጸሎት መጻሕፍት ወደ ሲዳምኛ ቋንቋ መተርጎማቸውን፣ በቀጣይም ሌሎች ቅዱሳት መጻሕፍት እየተተረጎሙ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የገዳሙ አስተዳዳሪ መልአከ ፀሐይ መምህር ቆሞስ አባ ኪዳነማርያም አንዱዓለም የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት በማስተላለፍ፣ ገዳሙ ከሚያከናውናቸው የልማት ሥራዎች በተጨማሪ ለገጠር አብያተ ክርስቲያናት፣ ለአቅመ ደካሞችና ለችግረኞች የሚያደርገውን ድጋፍ አብራርተው፣ ለበዓሉ መሳካት አስተዋፅኦ ላበረከቱ ተቋማትና ግለሰቦች ምስጋና አቅርበዋል።
የሲዳማ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ጥበባት አባ ዘሚካኤል መርጊያ ቅዱስ ገብርኤል በእግዚአብሔር ተልኮ ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን ከሰማዕትነት ፈተና ያዳነበት ታሪክ በእምነት መጽናትንና ፈተናን በእምነት ማለፍን የሚያስተምር መሆኑን ገልጸዋል።
በመቀጠል የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ በዓሉን ለማክበር ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ለመጡ ምዕመናን እንኳን ደህና መጣችሁ፣ እንኳን አደረሳችሁ በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈው፣ በቀጣይም የቅዱስ ገብርኤልን በዓለ ንግሥ በሀዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ተገኝተው እንዲያከብሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ብፁዕ አቡነ ዮሴፍም ከኢሳይያስ 43፥1-3 የተወሰደውን “በውኃ ውስጥ ባለፍህ ጊዜ ከአንተ ጋር እሆናለሁ…” የሚለውን ቃለ እግዚአብሔር መነሻ በማድረግ፣ ስለ በዓሉ መንፈሳዊ ትርጉም፣ ስለ እምነት ጽናትና በዘመናችን እየታዩ ስለሚገኙ የሰው ጭካኔና አረመኔነት ሰፊ ትምህርት አስተላልፈዋል። በተጨማሪም ለክልሉና ለሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ለሚያደርጉት ትብብር ምስጋና አቅርበው፣ ገዳሙ በልማትና በማኅበራዊ ድጋፍ ላይ ያለውን አስተዋፅኦ አብራርተዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ካስተላለፉ በኋላ፣ የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በታላቅ ድምቀትና ያለምንም የጸጥታ ችግር በሰላም ተጠናቋል።©ናዛዚ ሚዲያ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ወቅታዊ ጉዳዮች በማስመልከት አባታዊ መልእክት አስተላለፉ።

ሓምሌ 18 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ቅዱስነታቸው ያስተላለፉት አባታዊ መልእክት እንደሚከተለው ነው፦
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
“ገባሬ ሣህል እግዚአብሔር፥ ወይፈትህ ለኩሉ ግፉዓን፦
እግዚአብሔር ይቅርታ አድራጊ ነው፤ ለተበደሉ ሁሉ ይፈርዳል።”
(መዝሙር ፻፪፥፮)
ከሁሉ በማስቀደም በሀገር ውስጥ እና በመላው ዓለም የምትኖሩ ኦርቶዶክሳውያን የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንን ሐምሌ 19 ቀን 2018 ዓመተ ምሕረት በከፍተኛ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ለሚከበረው፤ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ በእምነታቸው የጸኑትን ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን በመከራቸው መካከል እየተራዳ የእሳቱን ነበልባል እንደክረምት ውኃ ላቀዘቀዘበት፤ በእግዚአብሔር ቃል ኪዳን የታመኑትንም እስከ ሰማዕትነት ፍጻሜ ድረስ የሚያጸና መሆኑን ለምንዘክርበት ታላቅ በዓል እንኳን አደረሳችሁ ለማለት እንወዳለን።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ የወንጌልን ብርሃን በማብራት፣ የሰላምን መንገድ በማስተማር፣ ፍትሕን በማጽናት፣ የተጨነቁትንም በማጽናናት፣ ሕዝብንና ሀገርን እየደገፈች የኖረች ናት።
በዚህ ቅዱስ ተልእኮ ውስጥም መናንያን መነኮሳት እና መነኮሳይያት ዓለምንና ከዓለም የሚገኘውን ጊዜያዊ ክብር፣ ጥቅም፣ ምቾትና የመሳሰሉትን በፈቃዳቸው ትተው፤ በየገዳማቱ በበአታቸው በጾም፣ በጸሎት ተወስነው፤ ሕይወታቸውን በትሕትና ለእግዚአብሔር በመስጠት፤ ስለ ራሳቸው ብቻ ሳይሆን ስለ ሀገር፣ ስለ ሕዝብ፣ ስለ ሰላምና ስለ ዓለም ደኅንነት በመዓልትና በሌሊት የሚጸልዩ የምድራችን በረከቶች ናቸው።
መስቀልን በተሸከሙ፣ ጸሎትን መከታ ባደረጉ፣ ለፍጥረት ሁሉ ምሕረትን በሚለምኑ፣ ራሳቸውን ለመከላከልም ምንም ዓይነት ቁሳዊ ዝግጅት በሌላቸው በእነዚህ መናንያን ላይ እጅን ማንሣት በእግዚአብሔር ዘንድ የተከለከለ፣ በታሪክ ፊትም የሚያሳፍር ድርጊት ነው።
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን!
በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በቦረና ወረዳ በግዮን አባይ ገዳመ አስቄጥስ ቅድስት አርሴማ፣ አቡነ አረጋዊና ቅዱስ ቂርቆስ የአባቶችና የእናቶች አንድነት ገዳም ሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓመተ ምሕረት በተፈጸመው ጥቃት የመናንያን መነኮሳይያት ሕይወት በግፍ መጥፋቱን፤ በርካቶች መቁሰላቸውን፤ በገዳሙና በንዋየ ቅድሳቱ ውድመት መድረሱን ከሀገረ ስብከቱ መግለጫ በከፍተኛ ሐዘን የሰማን ሲሆን፤ በተመሳሳይም በዚሁ ዕለት በሀድያና ስልጤ ሀገረ ስብከት የአምልኮ ሥፍራ በኃይል መፍረሱና በምእመናን ላይ ጥቃት መድረሱ የሚያሳዝንና በፍጹም ተቀባይነት የሌለው የተወገዘ ተግባር ነው።
በመሆኑም የጸሎት፣ የትምህርት፣ የሰላምና የመንፈሳዊ እሴት ማዕከል የሆኑትን ገዳማት መጠበቅ የአንድ ሃይማኖት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፣ የሰው ልጅ ክብርን፣ የሕግ የበላይነትንና የሀገር ሰላምን የማስጠበቅ ሓላፊነት ያላቸው በየደረጃው የሚገኙ ባለሥልጣናትና የሕግ አስከባሪ አካላት ጭምር እንደመሆኑ አሰቃቂ ጥቃት የፈጸሙት ተጠያቂዎች ለፍትሕ እንዲቀርቡ፤ ሌሎች ገዳማትና አድባራት ደኅንነታቸው እንዲጠበቅልን፤ ለተጎዱትም ተገቢው ድጋፍ እንዲደረግልን ዛሬም አበክረን እንጠይቃለን ።
በመጨረሻም ሕዝበ ክርስቲያንና መላው ኢትዮጵያውያን የጥቃት ሰለባ ከሆኑት ወገኖች ጋር በመንፈሳዊም ሆነ በሰብአዊ ድጋፍ አብራችሁ እንድትቆሙ ከአደራ ጭምር እያሳሰብን፤ በጽድቅ የሚፈርደው እግዚአብሔር አምላካችን ለተበደሉት ፍትሕን፣ ለቆሰሉት ፈውስን፣ በግፍ ሕይወታቸውን ለተነጠቁት ዕረፍተ ነፍስን፣ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ፍጹም ሰላምን ይስጥልን እያልን አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አሜን።
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ሐምሌ 18 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
© የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት

ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የተሰሩ የልማት ሥራዎችን ተመለከቱ፤ በድሬዳዋ መልካ ጀብዱ መካነ ቅዱሳን አቡነ አረጋዊ ወአርሴማ ገዳም የሚገኙ እጓለማውታ ሕጻናትን ጎበኙ።

ሐምሌ 18 ቀን 2018 ዓ.ም
ድሬዳዋ -ኢትዮጵያ
በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣
የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ያሳደሰውን የሀገረ ስብከቱን ጽሕፈት ቤትና በሀገረ ስብከቱ ወጪና የአዋጪነት ጥናት መሰረት በድሬዳዋ ደብረ ምጥማቅ ቅዱስ ፊሊጶስ ቤተክርስቲያን በመገንባት ላይ የሚገኘውን የገበያ ማዕከል ጎብኝተዋል።
በተያያዘ ዜና ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የድሬዳዋ በመልካጀብዱ መካነ ቅዱሳን አቡነ አረጋዊ ወከርሴማ ገዳም ሕጻናት ማሳደጊያ የሚኖሩ ዕጓለማውታ ሕጻናትንና በተቋሙ የተከናወኑ ልዩልዩ የልማት ሥራዎችን ተመልክተዋል።ሕጻናቱ በዕውቀትና በፈሪሐ እግዚአብሔር እናዲያድጉ በማድረግ ረገድም ተቋሙ እየሰራ ያለውን ሥራም ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አድንቀዋል።
ለገዳሙ ማኅበረሰብዕም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ ክቡር አቶ ሀርቢ ቡህ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ፣ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገ፣ረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣የጠቅላይ ቤተክህነት የየመምሪያው ኃላፊዎች ተገኝተዋል።በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ትምህርተ ወንጌልና ቃለ ምዕዳን ተሰጥቶ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል።

የድሬዳዋ ሳባ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ያስገኘባው ባለ ሦስት ወለል ሁለገብ ሕንጻ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጸሎተ ቡራኬ በዛሬው ዕለት ተመረቋል።

ሐምሌ 17 ቀን 2018 ዓ.ም
ድሬዳዋ-ኢትዮጵያ
የድሬዳዋ ሳባ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ያስገኘባው ባለ ሦስት ወለል ሁለገብ ሕንጻ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጸሎተ ቡራኬ በዛሬው ዕለት ተመረቋል።
በተያያዘ ዜና በቅጽረ ቤተክርስቲያኑ የሚገኘውና ለክኒሊክ አገልግሎት የተሰራው ሕንጻም የተመረቀ ሲሆን ተከራይቶ ለቤተክርስቲያኑ ገቢ ማስገኛ አገልግሎት የሚውል መሆኑ ተገልጿል።
በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ርብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣የጠቅላይ ቤተክህነት የየምምሪያው ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን ዕድሳት ተጠናቆ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው ተባረከ።

ሐምሌ ፲፮ ቀን ፻፻ ፲ወ፰ ዓ.ም ቁልቢ
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣
የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከሰባ ዓመታት አገልግሎት በኋላ የታደሰውን የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን ባርከው ታቦተ ሕጉን ወደ መንበረ ክብሩ አስገቡ።
በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የምዕራብ ሐረርጌ
ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ርብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣የጠቅላይ ቤተክህነት የየምምሪያው ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ የሚመራ የቤተክርስቲያናችን ልዑክ ወደ ቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ተጓዘ።

ሐምሌ ፲፮ ቀን ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣
የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሚመራ የቤተክርስቲያን ልዑክ ወደ ቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ተጉዟል።
ከልዑካን ቡድኑ መካከል በፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ
ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ
አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ
አቡነ ገብርኤል የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ርብከት ሊቀ ጳጳስ ፣
የጠቅላይ ቤተክህነት የየምምሪያው ኃላፊዎች ይገኙበታል።
የልዑክ ቡድኑ ወደ ቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የተጓዘው ዓመታዊውን የቅዱስ ገብርኤል በዓልን ለማክበርና ከሰባ ዓመታት አገልግሎት በኋላ ከፍተኛ ጉዳት ላይ ደርሶ የነበረው የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን ታድሶ በመጠናቀቁ ታቦተ ሕጉን ወደ መንበረ ክብሩ ለመመለስና በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ለመገኘት ነው።
በዚህም መሰረት ብፁዓን አባቶቹ በዛሬው ዕለት በገዳሙ ተገኝተው ታቦተ ሕጉን ወደ መንበረ ክብሩ የሚያስገቡ ሲሆን የታደሰው ሕንጻ ቤተክርስቲያንም ይመረቃል።
በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ ሥራ አስኪያጁ የሚመራው የቤተክርስቲ ያናችን ልዑክ ድሬዳዋ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ ክቡር አቶ ሀርቢ ቡህ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ፣ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገ፣ረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ካህናትና ሰንበት ተማሪዎች በዝማሬ አቀባበል ያደረጉለት ሲሆን የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደርም በክብር ዘብና በማርሽ ባንድ የታጀበ ደማቅ አቀባበል አድርጎለታል።

አሐዱ ባንክ ላደረገው ሁለተናዊ እገዛ በቋሚ ሲኖዶስ የእውቅናና የምስጋና ምስክር ወረቀት ተበረከተለት።

ሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ መመሪያ ሰጪነት በሕዝብ ግንኙነት መምሪያ አዘጋጅነት ሐምሌ 9 እና 10 ቀናት 2018ዓ.ም ሲካሄድ የቆየው ሀገር አቀፍ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኀላፊዎች የምክክርና የውይይት መርሐግብር ዘርፈ ብዙ ግንዛቤዎችን በማስጨበጥ የተጠናቀቀ ሲሆን ይህንን የሥልጠና መርሐ ግብር ሙሉ ወጪ በመሸፈን አስተዋጽኦ ላደረገው ለአሃዱ ባንክ አክሲዮን ማኅበር እና መምሪያውን በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት ትብብር ላደረጉ አካላት እንዲሁም ባለፉት አራት ዓመታት በተለያዩ የሥልጠና መርሐ ግብሮች ላይ ለተሳተፉ ምሁራን የቤተክርስቲያን ልጆች በዛሬው እለት የምስጋና ምስክር ወረቀት ስጦታ ከቅዱስ ፓትርያርኩ እጅ ተበርክቶላቸዋል።
በመርሐ_ግብሩ የመግቢያ ንግግር ያደረጉት የመምሪያው ዋና ኀላፊ ሊቀ ሥዩማን እስክንድር ገብረክርስቶስ ቤተክርስቲያን
ቴክኖሎጂ የታጠቀ፣ሀቀኝነትን መሰረት ያደረገ፣ተቋም ተኮር የሆነ የሕዝብ ግንኙነት ሥራን ለመሥራት የሚያስችል ግንዛቤ ማስጨበጥን ዓላማው ያደረገው ሥልጠና በቅርቡ መሰጠቱን አስታውሰዎ የሥልጠናውን ወጪ እንዲሸፍን ለአሐዱ ባንክ የቀረበው ጥሪ ባንኩ አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ሥልጠናውን በስኬት እንድናከናውን ስላደረገን በቅዱስነትዎና በቋሚ ሲኖዶስ ፊት ልባዊ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ብለዋል።
በመቀጠልም ሕዝብ ግንኙነት ለአራት ተከታታይ ዓመታት በሚያደርጋቸው ስልጠናዎች እውቀታቸውንና ጊዜያቸውን ሳይሰስቱ የመምሪያው አጋር በመሆኑ ያገዙ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በዚሁ እለት እውቅና የምስክር ወረቀት እንዲሰጣቸው የተደረገው ቀጣዩን ሥራችንን ስኬታማ ለማድረግ ስለሆነ ላበረከታችሁልን አስተዋጽኦ ሁሉ ምስጋናችን ይድረሳችሁ ብለዋል።
በዚሁ ጊዜ ብፀዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት የሰማነው ሁሉ ለቤተክርስቲያን የሚጠቅም ሥራ ነው። ቤተክርስቲያን የሁላችንም ስለሆነች ቤተክርስቲያንን መርዳት የሁላችንም ግዴታ ነው ። በቤተክርስቲያን ላይ የሚነሱ አጸያፊ ስም ማጥፋቶችን ለመከላከልም ይሁን የቤተክርስቲያን ትክክለኛ አንደበት ለመሆን የተሰጠው የግንዛቤ ማስጨበጫ እጅግ ደስ የሚል ነውና ለቤተክርስቲያን የሚጠቅም ስለሆነ ለሥልጠናው ስኬት ድጋፍ ላደረጋችሁ ሁሉ እግዚአብሔር ይስጥልን ብለዋል።
ከቅዱስነታቸው መልዕክት ቀደም ብሎ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ የመምሪያውን ዋና ኀላፊ በማመስገን ጀምረው በውይይቱ መርሐግብሩ ቤተክርስቲያን ሊያስከብር የሚችል ምክክር እንደተደረገ ምስክርነታቸውን ሰጥተው በቀጣይም በቤቶችና ሕንጻዎችም ይሁን በሕዝብ ግንኙነት መምሪያ የሚታየው ለውጥ እንዲቀጥል አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል።
በመጨረሻም የአሐዱ ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ “ከብዙኃን ለብዙኃን” በሚለው ሥራችን መሠረት ቤተክርስቲያን ለምታደርገው ማንኛውም ልማት እገዛ ማድረግ ተቀዳሚ ተግባራችን ነው ብለዋል።(ፎቶ Eotc tv)