በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ (አይሲቲ) እና የዲጂታል ሽግግር አማካሪ ኮሚቴ ለአስተዳደር ጉባኤው በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ እየሠራ ያለውን የተለያዩ የጥናት ሰነዶች አቀረበ፡፡
ሰኔ 24 ቀን 2018 ዓ.ምየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ (አይሲቲ) እና ዲጂታል ሽግግር አማካሪ ኮሚቴ በዘመናዊ የዲጂታል ዓለም ውስጥ ቤተክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎቷን ተደራሽ ማድረግ የምትችልባቸውንና አስተዳደራዊ አቅሟን ለማሳደግ የሚረዱ ሙያዊ ምክረ ሐሳቦችንና ስልታዊ ጥናቶችን በማቅረብ እንዲሠራ የተቋቋመ ኮሚቴ ነው፡፡
የኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ዮሐንስ ተስፋዬ ለአስተዳደር ጉባኤ ባቀረቡት ጥናት “ቤተክርስቲያን በቴክኖሎጂ የዳበረ ዘመናዊ የቤተክርስቲያን አስተዳደር ሥርዐትን ለመገንባት ከመንፈሳዊ እሴቶች ጋር የተጣጣመ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ ለቀጣይ ትውልድ አገልግሎት መስጠት የሚችል የኢንፎርሜሽንና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂን መጠቀም እንደሚያስፈልጋት አስረድተዋል፡፡
የዲጂታል ቴክኖሎጂ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤትክርስቲያን ስብከተ ወንጌል ለማስፋፋት፣ አስተዳደሯን ለማዘመን፣ የፋይናንስ ሥራዎቿን ለማቀላጠፍ፣ የቤተክርስቲያን ጥንታዊና ታሪካዊ ቅርሶቿን ለማስጠበቅና ለማስተዳደር ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው መሆኑ በጥናቱ ተመላክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስቀድሞ ለአገልግሎት ትጠቀምባቸው የነበሩ ሀርድ ኮፒዎች ዲጂታይዝ ለማድረግ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ (አይሲቲ) እና ዲጂታል ሽግግር አማካሪ ስትራቴጂክ ሰነድ መዘጋጀቱን ሰብሳቢው ገልጸዋል።
ቤተክርስቲያን ለዘመናት የቆዩ የብራና መጻሕፍት፣ የቅኔ፣ የያሬዳዊ ዜማዎችና የቅዱሳት ሥዕላት ባለቤት መሆኖከአጥቢያ እስከ መንበረ ፓትርያርክ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ካህናትና ምእመናንን የምትመራ ቢሆንም እነዚህ ሁሉ ትላልቅ መረጃዎችና መዛግብት ግን በአንድ ላይ ተሰንደው ከመቀመጥ ይልቅ በተበታታነ ሁኔታ እንደሚገኙ ተገልጿል። በመሆኑም የቤተክርስቲያን ቅርስና ሀብት ዘመኑ የሚጠይቀውን የዲጂታል ቴክኖሎጂ በመጠቀም በአንድ ማዕከል ሠንዶ ማስቀመጥ እንደሚገባ ሰብሳቢው አስገንዝበዋል ፡፡
የአስተዳደር ጉባኤ አባላቱም በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ አመራር ለዘርፉ የተሰጠውን ትኩረትና የተከናወኑ ተግባራትን በማድነቅ አስተያየት የሰጡ ሲሆን፤ እነዚህ ትላልቅ ሥራዎች በአጭር ጊዜ ተጠናቀው በአዲሱ በጀት ዓመት ተግባራዊ ሊሆኑ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጥናቱን በማዘጋጀት ያቀረቡ የኮሚቴ አባላትን አመስግነው፤ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለቤተክርስቲያን አገልግሎት አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበት በግንቦት ፳፻፲፰ ዓ.ም የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ አጀንዳው መቅረቡን ጠቅሰዋል። ምልዓተ ጉባኤውም በአጀንዳውና የቀረቡለት የተለያዩ ሥራዎችን በመገምገም የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ መመሪያ መስጠቱን አውስተዋል።ዛሬ የቀረቡትም የተለያዩ የጥናት ሰነዶችም ይህንኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ መሠረት በማድረግ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም በብፁነታቸው የተመራው የአስተዳደር ጉባኤ አባላት በመንበረ ፓትርያተርክ ቅጽር ግቢ የሚሠራውን የልማት ሥራ ተመልክተውዋል፤ በተለይም ለብፁዓን አባቶች ማረፊያ ቤት አጠገብ የሚሠራውን ግንባታ በልዩ ትኩረት በአፋጣኝ ተሠርቶ እንዲጠናቀቅ አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡©Eotc tv