የቤቶችና ሕንጻዎች ልማት ድርጅት ሠራተኞቹን አመሰገነ።

ሰኔ 22 ቀን 2018 ዓ.ም
በመርሐግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያናዊ ልማትና ተራድኦ ኮሚሽን እና የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት የበላይ ሊቀ ጳጳስ ሊቀ ሥዩማን እስክንድር ገብረ ክርስቶስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዋና ኃላፊ እና የቤቶችና ሕንጻዎች ልማት ድርጅች ዋና ሥራ አስኪያጅ እንዲሁም የድርጅቱ ልዩ ልዩ ኃላፊዎች እና ሠራተኞች ተገኝተዋል::
በመርሐግብሩ በተቋሙ የተሻለ አፈጻጸም ያስመዘገቡ የተቋሙ ሠራተኞች የምሥጋናና የዕውቅና መርሐ ግብር የተከናወነ ሲሆን ለሠራተኞቹ በብፁዕ አቡነ ሳሙኤልና በሊቀ ሥዩማን እስክንድር ገ/ክርስቶስ አማካኝነት የምሥጋና የምሥክር ወረቀት ተሰጥቷል።
ሊቀ ሥዩማን እስክንድር ገ/ክርስቶስ በመሥጋና እና በዕውቅና መርሐግብሩ ላይ ድርጅቱ ላስመዘገባቸው ውጤቶች የድርጅቱ ሠራተኞች እጅግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክታችኋል በዚህም ለትጋታችሁ እና ለጽናታችሁ በድርጅቱ ስም እያመሰገንኩኝ ወደፊትም ለሚኖረን ቆይታ በከፍተኛ የሥራ ኃላፊነት እራሳችሁን እንድታዘጋጁና ሥራችሁን በኃላፊነትና በታማኝነት እንድትሠሩ በማለት መልዕክት አስተላልፈዋል።
አክለውም ከዚህ ቀደም ድርጅቱ የመጣባቸው የአሠራር ክፍቶች አሁን ላይ የማይቀጥልና ሁሉም ሠራተኛ ሥራውን በአግባቡ መሥራት እንዳለበት እንዲሁም የምሥጋና መርሐ ግብሩ እንዳለ ሆኖ የአሠራር ክፍተት የሚታይባቸው ሠራተኞች አስተዳደራዊ እርምጃ እንደሚወሰድበት ጠቅሰው በቀጣይ ዓመት ድርጅቱ እራሱን እና አሠራሩን በቴክኖሎጂ በማዘመን ዘመኑን የዋጀ እና የተቀላጠፈ አገልግሎት የሚሰጥበትን ከፍተኛ ሥራዎች የምናከናውንበት ነው ብለዋል።
ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል በመርሐ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት እንዲ አይነት የዕውቅናና የምሥጋና መርሐ ግብራት የሠራተኛውን የሚያቀራርቡ ለተሻለ ሥራ የሚያተጉ ከመሆናቸው ባሻገር ጥሩ የአመራር ጥበብ የታየበት ነው ያሉ ሲሆን ይሄ ተግባር የአንድን ድርጅት የማዘመንና የማሳደግ ውጤት ጉልህ ማሳያ ነው ፤ አሁን የተሸለማችሁ በቀጣይ የተሻለ ውጤት በማምጣት ራሳችሁንም ተቋማችሁን ማሳደግ መለወጥ ይገባችኋል፤ በዚኛው ዙር ያልተሸለማችሁ የተቋሙ ሠራተኞች በቀጣይ በሥራችሁ በመትጋትና በመለወጥ በቀጣይ ዓመት የተሻለ ውጤት በማምጣት እንድትሸለሙ ሲሉ አባታዊ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በመጨረሻም የእውቅናና የምሥክር ወረቀት የተሰጣቸው የድርጅቱ ሠራተኞች ለተደረገላቸው እውቅናና ምሥጋና መደሰታቸውን ገልጸው በቀጣይ ተቋሙን አሁን ካለው በተሻለ በትጋትና በታማኝነት እንደሚያገለግሉ ቃል ገብተዋል።
መርሐ ግብሩ በብፁዕ አቡነ ሳሙኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያናዊ ተራዶኦ ልማት ኮሚሽንና የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት የበላይ ሊቀ ጳጳስ በጸሎት ተጠናቋል።© EOTC TV

“ተመራቂዎች በየተሰማሩበት የስምሪት መስክ ሁሉ እንደ መብራት ሊያበሩ ይገባል” ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ

(ሰኔ 20 ቀን 2018 ዓ.ም )
አንጋፋውና ታሪካዊው የባቱ (ዝዋይ) ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳምና ሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ በሥራ አመራር የዲፕሎማ መርሐ ግብር ያሰለጠናቸውን 23 ደቀ መዛሙርት እንዲሁም በ67ኛው ዙር የሦስት ወራት የካህናት ማሠልጠኛ ክፍል የተከታተሉ 36 ዕጩ አገልጋዮችን በድምሩ 59 ተተኪ መምህራንንና አገልጋዮችን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በታላቅ ድምቀት አስመርቋል።
ይህ ታላቅ የምረቃ መርሐ ግብር በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የጋራ ጸሎት የተከፈተ ሲሆን፣ የዕለቱ የቅዱስ ወንጌል ንባብ በብፁዕ አቡነ ማርቆስ አማካኝነት ቀርቦ ሥነ-ሥርዓቱ በይፋ ተጀምሯል።
በበዓሉ ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ የኮሌጁና የገዳሙ የበላይ ኃላፊ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ አባል እንዲሁም የኢትዮጵያ ሃይማኖቶች ተቋማት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (ሳልሳዊ) እና ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የኮሌጁና የገዳሙ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፦ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የእንኳን ደህና መጣችሁ፣ ለተመራቂ ደቀ መዛሙርት ደግሞ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት በማስተላለፍ ሰፊ አባታዊ መመሪያና ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል።
ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክትም ፦ “የተማራችሁት የሥራ አመራር ሳይንስና የተቀበላችሁት የካህናት ሥልጠና፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በዘመናዊ አሠራርና በጥንታዊው መንፈሳዊ ሥርዓት አስተባብሮ ለመምራት ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው” ብለዋል።
አያይዘውም ተመራቂዎች በየተሰማሩበት የስምሪት መስክ ሁሉ እንደ መብራት አብርተው፣ እንደ ጨው አልጭተው፣ የወቅቱን ፈተናዎች በጽናት በማሸነፍና ትውልዱን በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር በመቅረጽ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮና ትውፊት በተግባር እንዲያስጠብቁ አደራ ብለዋል።
በተለይም ደግሞ በዕውቀትና በአገልግሎት እጥረት ምክንያት ፈተና በበዛባቸው የአህጉረ ስብከቱ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ላይ በመገኘት፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተማርና ወንጌልን በማስፋፋት አገልጋይነታቸውን ይበልጥ እንዲያጠናክሩ መመሪያ ሰጥተዋል።
በመቀጠል ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ባስተላለፉት ቃለ ምዕዳን፣ እርሳቸውም የዚሁ የቅዱስ ገብርኤል ገዳም ፍሬ መሆናቸውን በኩራት ገልጸው ታሪክን ወደ ኋላ በመመለስ የገዳሙን መሠረት አስታውሰዋል። ትናንት በችግርና በጥቂት ጅማሮ የነበረው ገዳም፣ ዛሬ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ መሪነት ሁለንተናዊና አርአያነት ያለው የልማትና የትምህርት ማእከል መሆኑን በማነጻጸር አብራርተዋል። ይህ ስኬት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሆነ አገርን ለሚረከበው ተተኪ ትውልድ ያለው ፋይዳ የላቀ መሆኑን ገልጸዋል።
የገዳሙ አበምኔት ሊቀ ሊቃውንት ቆሞስ አባ አትናቴዎስ በበኩላቸው፣ የ67ኛ ዙር የካህናት ሥልጠና 36 ደቀ መዛሙርት መመረቃቸውን አብስረው፣ የገዳሙን ታሪካዊ ጉዞና ልማት አብራርተዋል።
አበምኔቱ ባደረጉት ንግግር፤ የቀድሞው የሸዋ ክፍለ ሀገር ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (ካልዕ) የነበረውን ታላቅ ራእይና ዓላማ በመንተራስ፣ የአሁኑ የገዳሙ የበላይ ጠባቂና የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (ሳልሳዊ) ላለፉት 31 ዓመታት ገዳሙ ዛሬ ለደረሰበት የከፍታ ደረጃ እንዲበቃ የከፈሉትን ታላቅ መሥዋዕትነትና ያሳዩትን የረጅም ርቀት አርቆ አሳቢነት በዝርዝር አብራርተዋል።
አያይዘውም በብፁዕነታቸው አርቆ አሳቢነትና መሪነት ተቋሙን ወደ ፊት ወደ “ዩኒቨርሲቲ” ደረጃ ለማሳደግ ታላቅ ዓላማ ተይዞ በገዳሙ ውስጥ የማይጠፉ ዘላቂ አሻራዎች እየተቀመጡ መሆናቸውን ገልጸው፤ በባቱ ከተማ ላይ እየተገነባ የሚገኘውን ግዙፍ የG+8 ሕንጻ የግንባታ ሂደት በመጥቀስ፣ ገዳሙ ወደፊት በራስ አገዝ ልማት ራሱን እንዲያስተዳድር እየተደረገ ያለውን ጥረት ገልጸዋል።
የሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጁ ዲን መጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ ታፈሰ ስለ ተቋሙ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ማብራሪያ ሰጥተዋል። ኮሌጁ በአሁኑ ወቅት 5ኛ ዙር ላይ መድረሱንና እስካሁን 123 ደቀ መዛሙርትን ማፍራቱን ጠቅሰው፣ ዘንድሮ ደግሞ 23 ተማሪዎችን ለምረቃ ማብቃታቸውን ገልጸዋል። ኮሌጁ ከአራቱም አቅጣጫዎች ከተለያዩ አህጉረ ስብከት መሥፈርቱን አሟልተው የመጡ ሰልጣኞችን ተቀብሎ የሚያስተምር መሆኑን ጠቁመው፤ የሥራ አመራር ተማሪዎቹ በቆይታቸው ከተለመደው ትምህርት በተጨማሪ በገዳሙ የአብነት ትምህርት ቤት ውስጥ በመግባት የቅኔ ትምህርት መቁጠራቸውን በልዩ ስኬትነት አንስተዋል። አያይዘውም ኮሌጁ አድማሱን በማስፋት በአዲስ አበባ፣ በአዳማና በአርባ ምንጭ በርቀት የትምህርት መርሐ ግብር እያስተማረ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዕለቱ የኮሌጁ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ተባባሪ ፕሮፌሰር ቀሲስ ሙሉጌታ ስዩም በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልእክት አስተላልፈዋል።
የባቱ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ሁስማን ተስሔ በምረቃው ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፣ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር የምታስተምረው ሰላምን መሆኑን ገልጸው፤ ገዳሙ ከመንፈሳዊ አገልግሎቱ ጎን ለጎን ማኅበረሰቡን በሥራ አመራር ሳይንስ ማስተማሩና በልማት ላይ እያሳየ ያለው ከፍተኛ ተሳትፎ ለአካባቢው ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አረጋግጠዋል። ልማትና ሰላም የማይነጣጠሉ መሆናቸውን በመግለጽ፣ በጥቂቱ የተጀመረው ይህ ታላቅ ተቋም ዛሬ ለደረሰበት የከፍታ ደረጃ ለገዳሙና ለአባቶች የላቀ ምስጋና አቅርበዋል።
በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ማጠናቀቂያ ላይ፣ በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ ከ1ኛ እስከ 3ኛ ለወጡ የደረጃ ተማሪዎች የተዘጋጀው ልዩ የክብር ሽልማት፤ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እጅ የተበረከተላቸው ሲሆን፣ ተመራቂዎቹም የአባቶችን አምላካዊ ቡራኬ በመቀበል ሽልማታቸውን ተረክበዋል።
በዚህ ደማቅ የበዓል መርሐ ግብር ላይ በገዳሙ የቅኔ መምህርና በተመራቂ ደቀ መዛሙርት አማካኝነት ቅኔ እንዲሁም ያሬዳዊ ወረብ ቀርቦ ሥነ ሥርዓቱ በጸሎት ተጠናቋል።
በምረቃ ሥነ- ሥርዓቱ ላይ የሀገረ ስብከታችን ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የሀገረ ስብከታችን ም/ሥራ አስኪያጅ: የሀገረ ስብከታችን የመመሪያው ክፍል ኃላፊዎች፣ የኮሌጁና የገዳሙ የየክፍሉ ኃላፊዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፣ ተመራቂዎችና ወላጆቻቸው አባ ገዳዎች አደ ሥንቄዎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የዕለቱን ታላቅ የምረቃ ሥነ-ሥርዓትና አጠቃላይ መርሐ ግብር በብፁዕነተታቸው አባታዊ መመሪያ እና በወጣው ቅደም ተከተል መሠረት በከፍተኛ ትጋት የመሩት የሥራ አመራር ኮሌጁ የሬጅስትራር ክፍል ዋና ኃላፊ መምህር ዲበ ኩሉ ጌታነህ እና በአፋን አሮሞ የገዳማችን ቁጥጥር ናቸው።”
© ሐመረ ተዋሐደ ሚዲያ

የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሁለተኛውን ዙር የነገረ መለኮት ደቀ መዛሙርት በታላቅ ድምቀት አስመረቀ።

ሰኔ ፳ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም
በብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ሣልሳይ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተመሠረተው የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ ለሦስት ተከታታይ ዓመታት በነገረ መለኮት ትምህርት ዘርፍ ሲያስተምራቸው የነበሩ የሁለተኛ ዙር ደቀ መዛሙርት በዛሬው ዕለት በታላቅ ድምቀት አስመርቋል።
የሀገርና የቅድስት ቤተክርስቲያን ተተኪ አገልጋዮችንና ምሁራንን በማፍራት ላይ የሚገኘው የዚህ ኮሌጅ ታሪካዊ የምረቃ ሥነ-ሥርዓት በከፍተኛ መንፈሳዊ ድምቀትና ሥርዓት የተከናወነ ሲሆን፤ በበዓሉ ላይ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ሣልሳይ (የኮሌጁ መሥራችና የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ)፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ (የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የታቦር ፍኖተ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ) እና ብፁዕ አቡነ መቃሪዎስ (የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ) ተገኝተዋል። በተጨማሪም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ከፍተኛ ልዑካን እና የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አመራር አካላት፣ ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት አካላት በክብር እንግድነት በመገኘት የሥነ-ሥርዓቱ ተካፋይ ሆነዋል።
በዛሬው የምረቃ መርሐ ግብር ላይ መደበኛ የነገረ መለኮት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ 19 ደቀ መዛሙርት እንዲሁም ለአንድ ወር ተከታታይ የአጭር ጊዜ የአቅም ማጠናከሪያ ሥልጠና ሲከታተሉ የነበሩ 30 ካህናትና አገልጋዮች በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እጅ የዲፕሎማና የሰርተፍኬት የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል። ይህ የምረቃ በዓል ኮሌጁ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ዘርፍ እያበረከተ ያለውን ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያሳይ ሲሆን፤ ተመራቂዎቹም ላለፉት ሦስት ዓመታት የቀሰሙትን ዕውቀት መሠረት በማድረግ ኦርቶዶክሳዊነትን ለማስፋፋትና ቅድስት ቤተክርስቲያንን በዕውቀት ለማገልገል የሚሰማሩበት ልዩ ምዕራፍ መሆኑ ተገልጿል።
ኮሌጁ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ዘርፍ እያበረከተ ያለው ይህ ከፍተኛ አስተዋጽኦ፣ በሀገረ ስብከቱም ሆነ በቤተክርስቲያኗ ውስጥ የሚታየውን የአገልጋይ እጥረት ለመቅረፍ ትልቅ ተስፋ የሰነቀ መሆኑም በዕለቱ ተነግሯል።
በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ሰፋ ያለና ጥልቅ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል።
ለአጠቃላዩ ተመራቂዎች መንፈሳዊ መመሪያና አባታዊ መልዕክት ያስተላለፉት ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ሣልሳይ፤ መነሻቸውን “ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ ኑሩ” (ፊል 1፥27) በሚለው የቅዱስ መጽሐፍ ቃል ላይ በማድረግ ይህ ዕለት የትምህርታቸው ማብቂያ ሳይሆን የአገልግሎታቸው ጅማሬ መሆኑን ተመራቂዎቹ አውቀው ሊያስቡበት እንደሚገባ አሳስበዋል።
በጉባኤው ውስጥ የተማሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምዕመናንን የሚጠብቁበት ክንድ በመሆኑ፣ የተቀሰመው ዕውቀት ከአገልግሎት የተለየ እንዳይሆንና በትምህርት ደረጃ ብቻ ሳይቀረጽ በተግባር ላይ ሊውል እንደሚገባም መመሪያ ሰጥተዋል። ተመራቂዎቹ ለምዕመናን ምሳሌ በመሆን መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን በሓላፊነት ስሜትና በትጋት ሊወጡ እንደሚገባ የገለጹት ብፁዕነታቸው፣ የክህነት አገልግሎት ልዩ ክብር ያለው ቢሆንም ከሁሉ በላይ የመስዋዕትነትና የኃላፊነት ዋጋ መሆኑን፣ ያላችሁበት ዘመንም በብዙ ፈተናዎች የተከበበ መሆኑን በተለየ ሁኔታ መገንዘብና ማወቅ እንደሚገባ በጥብቅ አሳስበዋል። ታሪካዊው የምረቃ ሥነ-ሥርዓት በብፁዕ አቡነ መቃርዮስ ቃለ ምዕዳንና አባታዊ ቡራኬ ተጠናቋል። © ሣሌም የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች እንደገና ለማቋቋም፣ ለማደራጀት እና ለማጠናከር ያዘጋጀውን አዲስ ረቂቅ አዋጅ ለውይይት አቀረበ።

ሰኔ 20 ቀን 2018 ዓ.ም
በአዲስ አበባ እየተካሄደ በሚገኘው በዚህ የውይይት መርሐግብር ላይ፤ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና ሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በመንፈሳዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ ኣፈ መምህር ኣባ ገብረ ሥላሴ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሕግ መምሪያ ዋና ኃላፊ፣ አባቶች፣ ሊቃውንት፣ የፌደራል የመጀመርያ፣ ከፍተኛ ፣ ጠቅላይ እና ሰበር ሰሚ ፍርድ ቤት ዳኞች፣ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ፣ታዋቂ የሕግ ምሁራን፣ ጠበቆች፣የፍትሕ አካላት እና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሀገሪቱ የሕግ ሥርዓት ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቷንና ያለ ቤተ ክርስቲያኒቱ
አስተዋጽኦ የሕግ ጥናት ሙሉ ሊሆን እንደማይችል የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በመድረኩ ገልፀዋል።
ብፁዕነታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሕግና የፍትሕ ሥርዓት መሠረት በመጣል በኩል ታሪካዊ አሻራ አላት ብለዋል።
በተለይም ጥንታዊው “ፍትሐ ነገሥት” መንፈሳዊ ይዘትና መመሪያ ብቻ ያለው ሳይሆን፣ በአሁኑ ዘመን በሀገሪቱ ለሚሠራባቸው የፍትሐ ብሔር እና የወንጀለኛ መቅጫ ሕጎች መነሻ በመሆን ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳደረገ ብፁዕነታቸው በንግግራቸው አብራርተዋል። በዚህም የተነሳ ማንኛውም የሕግ ጥናትና ምርምር ሲካሄድ የቤተ ክርስቲያኒቱን የታሪክና የሕግ ማህደር ያላካተተ ከሆነ ሙሉነት እንደሚጎድለው ጠቁመዋል።
በተጨማሪም ሃይማኖታዊና ባህላዊ ሕጎች በዘመናዊው ሥርዓት ውስጥ ያላቸውን ቦታ በተመለከተ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እንዳነሱት፤ አሁን ሥራ ላይ ያለው የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዲሪ) ሕገ መንግሥት አንቀጽ 34 ንኡስ አንቀጽ 5 የሃይማኖትና የባህል ሕጎችን በግልና በቤተሰብ ጉዳዮች ላይ ዕውቅና እንደሚሰጥና እንደሚፈቅድ ዋቢ አድርገው አስታውሰዋል።
በአጠቃላይ የኢትዮጵያ የሕግ ታሪክ ሲነሳ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ ከግምት ውስጥ ሊገባ እንደሚገባና ሕጎቻችንም ከዚህ
ታሪካዊና ነባር ዕሴት የተቀዱ መሆናቸውን በመገንዘብ ሊሠሩ እንደሚገባ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
ለረጅም ጊዜ ጥናት ሲደረግበት የቆየው ይህ ረቂቅ አዋጅ፤ በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 34 ንኡስ አንቀጽ 5 እና 78 ንኡስ አንቀጽ 5 በተደነገገው መሠረት፣ በሃይማኖት ሕግጋት ላይ ተመሥርተው የሚዳኙ የሃይማኖት የፍርድ ተቋማት ዕውቅና ሊሰጣቸው እንደሚችል በሚያስቀምጠው የሕግ ማዕቀፍ ላይ የተመሠረተ ነው።
ይህ አዋጅ ጸድቆ ወደ ተግባር ሲገባ፤ ተከራካሪ ወገኖች በፈቃደኝነት ላይ በተመሠረተ ሁኔታ በጋብቻ፣ በፍቺ፣ በቀለብ አወሳሰን፣ በውርስና ስጦታ ጉዳዮች እንዲሁም ከቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች የሥራ ግንኙነትና ከቀኖናዊ አስተምህሮ ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ላይ በመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶቹ በኩል ዳኝነት እንዲያገኙ ሰፊ ዕድል ይከፍታል በማለት ኣፈ መምህር ኣባ ገብረ ሥላሴ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሕግ መምሪያ ዋና ኃላፊ ገልፀዋል።
በውይይት መድረኩ የተገኙት የሕግ ምሁራን በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ የቤተ ክርስቲያኒቱን የፍትሕ ሥርዓት ከማዘመን ባለፈ፣
የመደበኛ ፍርድ ቤቶችን የሥራ ጫና በማቅለል ረገድ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ጠቁመው፤ አዋጁ በፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግጋትና በቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖናዊ ሕጎች (እንደ ፍትሐ ነገሥት እና ዲድስቅልያ) መካከል ያለውን መስተጋብር ግልጽ በሚያደርግበት ሁኔታ ላይ ገንቢ የሕግ ሙያዊ ምክረ ሐሳባቸውን አክለውበታል።
በዛሬው ዕለት የተሰበሰቡት ግብዓቶች ታክለውበት ረቂቅ አዋጁ ይበልጥ ዳብሮ በቅርቡ ለሚመለከተው የመንግሥት የሕግ አውጪ አካል ቀርቦ ዕውቅና ያገኛል ተብሎ ይጠበቃል።
ይህ አዋጅ መጽደቁ ቤተ ክርስቲያኒቱ በመንፈሳዊ ጠቅላይ፣ ከፍተኛ እና የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቶች ተዋቅራ ተደራሽነቷን እንድታሰፋ ሕጋዊ መሠረት የሚጥል መሆኑም በውይይቱ ላይ ተጠቁሟል። © EOTC tv

የአንድ ክፍለ ዘመን ጽናትን በታላቅ የወንጌል ፍሬ የመለሰው የጅማ ሀገረ ስብከት 81 ወገኖችን ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን መለሰ

​ሰኔ 17 ቀን 2018 ዓ.ም| ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
በጅማ ሀገረ ስብከት፣ በኖኖ ቤንጃ ወረዳ በአልጋ ከተማ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ለተከታታይ አምስት ቀናት ሲካሄድ የሰነበተው ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ በታላቅ ድል ተጠናቀቀ። በጉባኤው ማጠናቀቂያ ላይ ቀደም ሲል የተለያዩ እምነቶችን ይከተሉ የነበሩ 81 ወገኖች ወደ እናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመመለስ የሥላሴን ልጅነት (የክርስትና ጥምቀትን) ማግኘታቸውን የሀገረ ስብከቱ ሕዝብ ግንኙነት አስታውቋል።
​የኖኖ ቤንጃ ወረዳ ሕዝበ ክርስቲያን ላለፉት አንድ መቶ ዓመታት (አንድ ክፍለ ዘመን) ያህል በታሪካቸው ውስጥ እጅግ ፈታኝና አስቸጋሪ የነበረውን የመንፈሳዊ እረኛ እጥረት በጽናት ተጋፍጠውታል። በዚህ ረዥም ዘመን ውስጥ ቋሚ ካህን ሳይመደብላቸው፣ ሕፃናትን አጥምቆና ሥጋ ወደሙን አክብሮ የሚያቀብል መንፈሳዊ አገልጋይ ሳይኖራቸው፣ እንዲሁም የማዕደ ቃል ኪዳኑን ወንጌል የሚመግብ ሰባኪ ሳያገኙ በከፍተኛ መንፈሳዊ ጥም ውስጥ ለመቆየት ተገደው ነበር።
​ይሁን እንጂ፣ ይህ ሁሉ መገለልና የእረኛ እጥረት ሳይበግራቸው፣ ከቀደሙት አባቶቻቸውና እናቶቻቸው የተቀበሉትን የእምነት ቀንዲል ሳያጠፉ፣ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታቸውን ክብርና ማንነት በልባቸው ጽላት ላይ ቀርጸው የኖሩ እውነተኛ የሃይማኖት ጠበቆችና የጽናት ተምሳሌት መሆናቸውን በተግባር አስመስክረዋል። ይህ የአንድ ክፍለ ዘመን ታሪካዊ ተጋድሎና የውስጥ ጽናት ነው ዛሬ ለታየው ታላቅ መንፈሳዊ ፍሬና የወገኖቻችን መመለስ ማዕዘን የሆነው።
​በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ሚስዮናውያን “ዘመቻ ፊልጶስ” በሚል ስያሜ ወደ አካባቢው በመንቀሳቀስ ምዕመናኑን ከኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነታቸው ለመለየት ከፍተኛ ግፊት ቢያደርጉም፣ የአካባቢው ጽኑዓን አባቶችና እናቶች ግን፦
​“እምነታችን አንዲት ናት፤ እሷም ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ናት!”
​በማለት የአባቶቻቸውን አደራና የሃይማኖት ርስት ሳያስደፍሩ በጽናት መቆየታቸው በጉባኤው ላይ ተንጸባርቋል።
​ማዕደ ቃል ኪዳኗን ናፍቀው ቆይተው ዛሬ ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እቅፍ ከተመለሱት ወገኖች መካከል አንዳንዶቹ በዕለቱ ባስተላለፉት ልብ የሚነካና ጥልቅ ምስክርነት፤ ከተዋሕዶ እምነታቸው ርቀው ለዓመታት እንዲንከራተቱ ያደረጋቸው ዋነኛው ምክንያት “የቋንቋ ተደራሽነት ክፍተት” እንደነበር በቁጭት አውስተዋል። በተለይም ማኅበረሰቡን ከተኩላ ለመጠበቅ የሚደረገውን መንፈሳዊ ጉዞ ለማደናቀፍ በሚንቀሳቀሱ አካላት “በገዛ ቋንቋችሁ ካልተማራችሁና ካልጸለያችሁ ከእግዚአብሔር ጋር መንገድ ላይ ተላልፋችኋል፤ ጸሎታችሁም አይሰማም” በሚል የተቀነባበረ የሐሰት ፕሮፓጋንዳና የተሳሳተ ትምህርት ታጥረው፣ በከፍተኛ መንፈሳዊ መደናገር ውስጥ ቆይተው እንደነበር በግልጽ ተናግረዋል።
​ይሁን እንጂ፣ በአሁኑ ወቅት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን የወንጌል አገልግሎት የማኅበረሰቡን ቋንቋና ባህል ማዕከል ባደረገ መልኩ በአካባቢው በስፋትና በጥራት በመዘርጋቱ፣ ያ የነበረው የጨለማ መጋረጃ ሊቀደድ ችሏል። ዛሬ ላይ ያለምንም መጋረጃ በገዛ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው የእግዚአብሔርን ቃል መመገብ፣ ከአምላካቸው ጋርም በልባቸው ቋንቋ መገናኘት በመቻላቸው የተሰማቸውን ቃላት የማይገልጸው ታላቅ መንፈሳዊ ደስታና ዕርካታ በደማቅ እንባ ታጅበው መስክረዋል።
​ቤተ ክርስቲያኗ በማኅበረሰቡ ቋንቋና ባህል መሠረት አድርጋ የጀመረችው የወንጌል አገልግሎት ምን ያህል ውጤታማና ታላቅ ድል እየተቀዳጀበት ያለ መሆኑን የኖኖ ቤንጃ ወረዳ በተግባር አሳይቷል። በዚሁ መሠረት በያዝነው በ2018 በጀት ዓመት ብቻ ከወረዳው በአጠቃላይ 318 ምዕመናን ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን ተመልሰው የቅድስት ሥላሴን ልጅነት አግኝተዋል።
​የዜና ምንጭ፦ ጅማ ሀገረ ስብከት
ዘጋቢ ሪፖርተር፦ ላዕከ ወንጌል ኃይሉ አየለ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳምን የሕንጻ ቤተክርስቲያን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸም ሂደትን ተዘዋውረው ተመለከቱ።

ሰኔ 9ቀን 2018 ዓ.ም /ቁልቢ/
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣
የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ክቡር ንቡረዕድ ኤልያስ አብርሃ የጠቅላይ ቤተክህነት የመንፈሳዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅና የጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች በቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የሕንጻ ቤተክርስቲያን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸም የደረሰበትን ሁኔታ ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።
በዚሁ ጊዜ የሕንጻ ቤተክርስቲያኑ የዕድሳት ሥራ በተያዘለት ጊዜ ገደብ ውስጥ በጥሩ ሁኔታ እየተካሔደ የሚገኝ ሲሆን የግንባታ ሥራውም ሰባ ፐርሰንት ተሠርቶ የተጠናቀቀ መሆኑንና በቀሪው አንድ ወር ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ የግንባታ ሥራው ተጠናቆ
ሐምሌ 17 ቀን ታቦተ ሕጉ ከመቃኞ በመውጣት ወደ ሕንጻ ቤተክርስቲያኑ እንደሚገባ አማካሪ መሐንዲሱ ፕሮፌሰር ፋሲል
እና የሕንጻ ሥራ ተቋራጩ የአዶር ኮንስትራክሽን ባለቤት ኢንጂነር አዲሱ ደመቀ ገልጸዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ባስተላለፉት አባታዊ የሥራ መመሪያ ቀደምት አባቶች ሠርተው ያቆዩልንን ይህን የመሰለ ጥንታዊ ገዳም ተንከባክቦና ጠብቆ ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ ይቻል ዘንድ በሚቻለው መጠን በርካታ ሥራዎች እየሠራን መሆኑን በተግባር የሚያረጋግጥ ሥራ በዚህ ታላቅ ገዳም እየተከናወነ ስለሆነ ቀሪ ሥራዎች የቤተክርስቲያኑን ጥንታዊነትና ታሪካዊነትን በጠበቀ መልኩ በጊዜው ተጠናቆ ለምርቃት እንዲበቃ።ጠንክራችሁ ሥሩ ካሉ በኋላ የዕድሳት ሥራውን በማከናወን ላይ የሚገኘው አዶር ኮንስትራክሽን በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ይህን ሥራ እዚህ ደረጃ ላይ ማድረስ በመቻላቸው ምስጋና ይገባቸዋል ብለዋል።
በመቀጠልሞ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት የዚህ ታሪካዊ ሥራ አካል በመሆናችን እድለኞች
ነን ካሉ በኋላ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ አባታዊ አመራር ሰጪነት
ይህን ታሪካዊ ቤተክርስቲያን ለማደስ በመቻላችን ደስተኞች ነን ብለዋል።አያይዘውም እየተሠራ ያለው ሥራ በጣም የሚደነቅና አፈጻጸሙም የሚያስመሰግን በመሆኑ ሥራውን የምታከናውኑ ባለሙያዎችም ምስጋና ይገባችኋል ካሉ በኋላ ይህ አንጋፋ ቤተክርስቲያን የእድሳት ሥራው እጅግ በጥንቃቄ መሰራት
የሚገባው መሆኑን ተገንዝባችሁ ሥራችሁን ከአሁን በበለጠ ትጋት እንድትፈጽሙ አደራ እንላለን በማለት አባታዊ መልዕክታቸውን አጠቃለዋል።

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያንን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸምን ለመጎብኘት ወደ ድሬዳዋ ተጓዙ።

ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ.ም
ድሬዳዋ-ኢትዮጵያ
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸም የደረሰበትን ደረጃ ለመመልከት ዛሬ ማለዳ ወደ ድሬዳዋ ተጓዙ።
ሁለቱ ብፁዓን አባቶችና አብረዋቸው የተጓዙት የቤተክርስቲያናችን ልዑካን ድሬዳዋ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ብፁዕ አቡነ በርቶሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ክቡር ከንቲባ ከድር ጅዋር የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፣ክቡር መልአከ ኃይል አባ ሰላማ የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ ፣ካህናትና ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ደማቅ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
ብፁዓን አባቶቹና የቤተክርስቲያናችን ልዑካን በቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸምን ከተመለከቱ በኋላ በቀሪ ሥራዎች አፈጻጸም ዙሪያ መመሪያ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን ለበርካታ ዓመታት ምንም አይነት የዕድሳት ሥራ ያልተከናወነለት በመሆኑ ለከፍተኛ ጉዳት ተዳርጎ መቆየቱን ተከትሎ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተእህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት አባታዊ መመሪያ ታኅሣሥ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ታቦተ ሕጉ ወጥቶ ወዲውኑ የዕድሳት ሥራው እንዲጀመር መደረጉ ይታወሳል።
በዘመን እርዝማኔና እርጅና ምክንያት በከፍተኛ ሁኔታ ለጉዳት ተዳርጎ የቆየው የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የዕድሳት ሥራ በአጭር ጊዜ ውስጥ በከፍተኛ ጥራትና ፍጥነት ተጠናቆ ሐምሌ 19 ቀን 2018 ዓ/ም ተመርቆ ታቦተ ሕጉ ወደ መንበረ ክብሩ ይመለሳል።ለዚህ ውጤታማ ሥራም የኮንትራት ሥራውን አሸንፎ የወሰደው አዶር ኮንስትራክሽን በተለይም ደግሞ የድርጅቱ ባለቤት ኢንጂነር አዲሱ ደመቀና የገዳሙ የአስተዳደር ሰራተኞችና የሥራ ኃላፊዎች የከፈሉት መስዋዕትነት በእጅጉ የሚደነቅ ነው።

ለብፁዕ አቡነ ኤፍሬም በደምቢ ዶሎ ከተማ ደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው

ሰኔ 6/10/2018
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን፣ የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን በማገልገል ላይ የሚገኙት ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፣በግንቦት 2018 ዓ በተካሔደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የቄለም ወለጋን ሀገረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ መወሰኑ ይታወቃል።
በዚህም መሰረት ብፁዕነታቸው ይህንኑ ኃላፊነት ለመረከብ ሰኔ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ወደ ደቢዶሎ ከተማ ሲያቀኑ፣በከተሣው ነዋሪዎች ምዕመናንና ምዕመናት ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል ።
ብፁዕነታቸው ወደ ቄለም ወለጋ ሀገረ ስብከት በተጓዙበት ጊዜ
ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ዶ/ር)፦ የኢሉ አባቦርና የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም የመቱ ፈለገ ሕይወት መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ፣ መላከ ምሕረት ቆሞስ አባ ገብረ እግዚአብሔር፦ የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ።በኩረ ትጉህ ቀሲስ ምትኩ ከንቲባ፦ የጠቅላይ ቤተክህነት የቅርስ ጥበቃ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ኃላፊ ሊቀ ልሳናት ቀሲስ በዳሳ ቶላ፦ የጠቅላይ ቤተክህነት የሊቃውንት ጉባኤና የኮዬ ፈጬ ክፍላተ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ላዕከ ወንጌል ኃይሉ አየለ፦ የጠቅላይ ቤተክህነት ሕዝብ ግንኙነት ምክትል መምሪያ ኃላፊ፣ መጋቤ ብሉይ ሣህለ ማርያም፦ የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ።
መላከ ሄዶም ቀሲስ ግርማ ኢማና፦ የደቢዶሎ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ተገኝተዋል ።
ብፁዕነታቸው ደቢዶሎ ደብረ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን እንደደረሱ፤ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የማህበራት ተወካዮች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፣ የነገረ መለኮት ምሩቃን እና ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣናት ደማቅ አቀባበል ያደረጉላቸው ሲሆን በስነ-ስርዓቱ ላይም የደብረ ፀሐይ ደንቢዶሎ መድኃኔዓለም ሰንበት ተማሪዎችና የአዲስ አበባና የሸገር ሀገረ ስብከት ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ያሬዳዊ ዜማ አቅርበዋል።
በዚሁ መርሐ ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ዶ/ር) ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት አንድነት ለቤተክርስቲያን ሁለንተናዊ ልማት ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ በሁሉም ቋንቋ በቀረበው አገልግሎት መደሰታቸውንና ይህን የመሰለ ሁሉን አቀፍ አገልግሎት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ገልጸዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ለተደረገላቸው ደማቅ አቀባበል ምስጋ አቅርበው ስለ ወለጋ ክልል ሰላም የሚነገረውና በተጨባጭ ያዩት እጅግ የተለየ መሆኑን በመጠቆም የሕዝቡ አንድነትና ፍቅር ልባቸውን እንደነካው ከገለጹ በኋላ ይህ መርሐ ግብር በሰላም እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉት ሁሉ ምስጋናቸውን በማቅረብ ቃለ ምዕዳንና ቃለ በረከት አስተላልፈው የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል።
ዘጋቢ የላዕከ ወንጌል ኃይሉ አየለ ነው፤

በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የሚመራ የቤተክርስቲያናችን ልዑክ አርሲ-አቦምሳ ወረዳ ተገኝቶ ምዕመናንን አጽናና ጊዜያዊ ርዳታም አበረከተ።

ሰኔ 4ቀን 2018 ዓ.ም
አርሲ-አቦምሳ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ በአርሲ ዞን አንዳንድ ወረዳዎች የተከሰተውን ችግር ተከትሎ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የሚመራ የቤተክርስቲያናችን ልዑክ በሥፍራው በመገኘት ተጎጂዎችን እንዲያጽናና ጊዜያዊ ርዳታም እንዲያደርግ
ያስተላለፈውን ውሳኔ ተከትሎ ዛሬ ማለዳ ወደ አርሲ ዞን አቦምሳ ወረዳ በመጓዝ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች አጽናንቷል፤ ጊዜያዊ ርዳታም አበርክቷል።
በአቦምሳ ወረዳ የትንሣኤ ብርሃን ደብረ ገነት መድኀኔዓለም ቤተክርስቲያን በመገኘት ተጎጂ ኦርቶዶክሳዊያንን ያጽናኑት
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ቅድስት ቤተክርስቲያን በበኦርቶዶክሳዊያን ልጆቿ ላይ በደረሰው ጉዳት እጅግ በጣም ማዘኗን ገልጸው እግዚአብሔር አምላክ ለሞቱት ወገኖቻችን መንግስተሰማያትን እንዲያወርስልን፣ለቤተሰቦቻቸው መጽናናት እንዲያድልልን የዘወትር ጸሎታችን ነው።በርቱ፣ጠንክሩ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን ብለዋል።
አያይዘውም ቋሚ ሲኖዶስ በአካል ተገኝቶ እናንተን ለማጽናናትና ጊዜያዊ ድጋፍ ለማድረግ በመካከላችሁ ተገኝተናል ያሉት ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ችግሩን ከመሰረቱ ለመፍታትና የተቃጠለውን ቤተክርስቲያን ለመሥራት የሚያስቼል አቢይ ኮሚቴ በጠቅላይ ቤተክህነት ተሰይሞ ወደ ሥራ ገብቷል ብለዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ጎርጎሬዎስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ቅድስት ቤተክርስቲያን በተከሰተው ችግር ጥልቅ ኀዘን የተሰማት መሆኑን ገልጸው ምዕመናን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ፣በፈተና ሁሉ እንዲታገሱ አደራ ካሉ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ኀዘንተኞችን እንዲያጽናና ከዳግም ኀዘን እንዲሰውርልን ዘወትር እንጸልያለን በማለት ቃለ ምዕዳንና ቃለ ቡራኬ ሰጥተዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ለተፈናቀሉ ወገኖች የተዘጋጀውን ርዳታ ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ አስረክበዋል።በዚሁ ጊዜ የአቦምሳ ከተማ የሀገር ሽማግሌዎችና አባ ገዳዎች ብፁዓን አባቶችን እንኳን ደህና መጣችሁልን በማለት በሀገሩ ባህል መሰረት የሰንጋ ስጦታ ካበረከቱ በኋላ የደረሰውን ጉዳት በመኮነን ሕዝቡ በስምምነት፣
በአንድነትና በመቻል የኖረና ወደፊትም የሚኖር ሕዝበብ መሆኑን ጠቅሰው የተፈጠረውን ችግር ሃይማኖታዊ መልክ ለማስያዝ የሚደረገው ጥረት ተገቢነት የሌለው ነው ብለዋል።ለብፁዓን አባቶች የተበረከተው የሰንጋ ስጦታም ለተፈናቀሉ ወገኖች እንዲደርስ ተደርጎ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል።

“በአርሲ የተቃጠለውን ቤተ ክርስቲያን እንሠራለን” የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች

ሰኔ ፪ቀን ፳፻፲ወ፰ ዓ/ም
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች በምሥራቅ አርሲ ሀገረ ስብከት በተፈጠረው የኦርቶዶክሳውያን ግድያና የቤተ ክርስቲያን መቃጠል ኃዘናቸውን ገልጸው በብፁዕነታቸውን መመሪያ ሰጪነት የተቃጠለውን ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ፈቃደኛ መሆናቸውን አሳወቁ።
አስተዳዳሪዎቹ ይህንን ያሉት በዛሬው ዕለት በተካሄደው የጋራ ስብሰባ ለጽድቅና ለመንግሥተ ሰማይ ዓላማ የሚሰበሰብ የቤተክርስቲያን ገቢ አስመልክቶ ውይይትና ምክክር በተደረገበት ስብሰባ ላይ ነው።
በስብሰባው ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና ሸገር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባና ሀዲያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ መልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ የሀገረ ስብከቱ ወና ሥራ አስኪያጅ ፣ መጋቤ ትፍስሕት ሙሉጌታ ቸርነት የሀገረ ስብከቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ፣ የሀገረ ስብከቱ የዋና ዋና ክፍል ሐላፊዎች ፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ሥራ አክኪያጆች፣ የገዳማትና አድባራት እእተዳዳሪዎች የክፍለ ከተማ ቤተ ክህነትና የአድባራት የሒሳብ ሹሞች ተገኝተዋል።
የስብሰባው ጉዳይ እውነተኞች ምዕመናን የሰጡትንና በተለያዩ የሰዋዊና ቁሳዊ ልማት ምክንያት ለቤተ ክርስቲያን ገቢ ያደረጉትን ገንዘብ ሕግና አሠራርን በመጠበቅ ቤተ ክርስቲያን ለተመሠረተችበት ሕያው ዓላማና መንፈሳዊ ሥራ ላይ አገልግሎት ላይ ይውል ዘንድ ምክክር ለማድረግ የተጠራ ስብሰባ እንደሆነ ተገልጿል።
በጉባኤውም በሀገረ ስብከቱ የሒሳብና በጀት ዋና ክፍል ሐላፊ ሊቀ ኅሩያን አስናቀ ሸዋየ አጭር ሪፖርት የቀረበ ሲሆን በዚህ መነሻነትም ከሀገረ ስብከቱ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ክርስቲያናት የያሉ ተሳታፊዎች ሐሳብና አስተያየት ሰጥተዋል።
አስተያያት ሰጪዎቹ እንዳሉት የቤተ ክርስቲያን ገቢዎችን ሕግና አሠራርን ጠብቆ ለተገቢው ዓላማ መዋል፣ ተቋማዊ ተናብቦትና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለችበት ሁሉ የተፈጠሩ ችግሮችና ቁስሎችን የጋራ በማድረግ ከግል ፍላጎትና ሐሳብ ይልቅ ቤተ ክርስቲያን በማስቀድም መሥራት በሚሉ ጉዳዮች ላይ አስተያያቶች ቀርበዋል።
በተለይም በሀገረ ስብከቱ ደረጃ እየተለመዱ የመጡ ዘመኑን ያነበቡና ችግር በችግር ሳይሆን በመፍትሔ እናክማቸውን በሚል መንገድ የተጀመሩ የውስጥ አሠራሮችና የተጨባጥ የሆኑ የራስ አገዝ ልማቶች በእጅጉ የሚበረታቱና የሚያስመሰግኑ መሆናቸውን ከከፍተኛ አድናቆት ጋር ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስና መልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ እንዲሁም የሀገረ ስብከቱን የሥራ ሐላፊዎች አመስግነዋል።
በሌላ በኩል አስተዳዳሪዎቹ በገጠሪቱ ያለቸው ቤተ ክርስቲያን ስታነባ ያመናል ፤ ቁስሏም ይጠዘጥዘናል፤ በመሆኑም በሰሙኑ በምሥራቅ አርሲ ሀገረ ስብከት የተቃጠለውን ቤተ ክርስቲያን በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ መመሪያ ሰጪነት ተባብረን ለመሥራት ፈቃደኛ መሆናችን እንገልጻለን ብለዋል።
የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ በበኩላቸው በብፁዕነታቸው የሚመራው ሀገረ ስብከት ነገን በማሰብ ዛሬ ላይ አቅዶ እየሠራ በመሆኑን በማስታወስ በዚህ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችን የሥራ ሐላፊዎች ድርሻቸው ሰፊ ነው ብለዋል።
አክለውም የተቀበልነው ሕያው ተልእኮ ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቅ ብቻ ሳይሆን በታማኝነት በመንፈሳዊ ትርፍ ዘመኑን በዋጀ መልኩ ለቀጣዩ ትውልድ በክብር የማስተላላፍ ድርሻ አለብን ለዚህ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ገቢ በአግባቡ መጠበቅና ቤተ ክርስቲያን ጠቀም ሥራዎችን በመሥራት መሆን አለበት ብለዋል።
የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የተሰጠንን ሐላፊነት በአግባቡ መተርጎምና ለቤተ ክርስቲያን ብልጫ ላለው አገልግሎት ማውል ይኖርብናል ያሉ ሲሆን በተለይም አሠራራችን ዘመኑን የዋጀ፣ ለምእምናን ቅርብ የሆነና ዘላቂ ለውጥ ላይ መሠረት ያደረገ መሆን አለበት ብለዋል።
ቀጥለውም የቤተ ክርስቲያን ገቢ ከምእመናን መቀነት እስከ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሚደርስ መስመር ያለው ተቋማዊ አሠራር ያለው በመሆኑ አልቅሳ አንብታ ለሐጢአት ሥርየት ብላ የምትሰጥውን የአንዲት ምእመን ስጦታና ዛሬን ለነገ እናሻግር በሚል መርሕ የተሠሩ የራስ አገዝ ልማቶች ገቢዎች በሰዓቱ መሰብሰብና ለታለመው ዓላማ ማዋል ይገባናል ብለዋል።
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሁሉም አህጉረ ስብከት ደጋፊ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና መጋቢ የሁሉ መጠጊያ እንደሆነ የገለጹት ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ አቡነ ሳዊሮስ ሊቀ ጳጳስ በቤተ ክርስቲያናችን ተቋማዊ ህልውና እና ተልእኮ ማስፈጸም ረገድ ድርሻው ሰፊ ነው ብለዋል።
በመሆኑም የሰው ልማት ላይና የተቋማት ዕድገት ላይ በእጅጉ መሥራት እንደሚገባው የተጠቆሙት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሚሠሩ ወንጌልን የሚስፋፋባቸው፣ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት የሚረዱበት እና ራሳቸውን ያልቻሉ አህጉረ ስብከት የሚደጎሙበት ሁሉን አቀፍ የራስ አገዝ ልማቶች ላይ በማገዝ ትልቁን ድርሻ እንደሚወጣ ተስፋቸውን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በተለያዩ አህጉረ ስብከት በበምእመናንና በአብያተ ክርስቲያናት ጉዳት ሲያጋጥም ቅዱስ ሲኖዶስ የሚያዘው በፍጥነት ለችግር የሚደርስ ሀገረ ስብከት መሆኑ ይታወቃል።
በምሥራቅ አርሲ ሀገረ ስብከት ግንቦት 23/2018 ዓ/ም ጀምሮ በተፈጠረው ጥቃት ንጹሐን ምእመናን በግፍ እንደሞቱና ከመቶ ዓመት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረው የጠለታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን እንደተቃጠለ የሚታወስ ነው ነው።
©የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ