ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያንን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸምን ለመጎብኘት ወደ ድሬዳዋ ተጓዙ።
ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ.ም
ድሬዳዋ-ኢትዮጵያ
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸም የደረሰበትን ደረጃ ለመመልከት ዛሬ ማለዳ ወደ ድሬዳዋ ተጓዙ።
ሁለቱ ብፁዓን አባቶችና አብረዋቸው የተጓዙት የቤተክርስቲያናችን ልዑካን ድሬዳዋ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ብፁዕ አቡነ በርቶሎሜዎስ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ክቡር ከንቲባ ከድር ጅዋር የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፣ክቡር መልአከ ኃይል አባ ሰላማ የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ ፣ካህናትና ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ደማቅ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
ብፁዓን አባቶቹና የቤተክርስቲያናችን ልዑካን በቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን የዕድሳት ሥራ አፈጻጸምን ከተመለከቱ በኋላ በቀሪ ሥራዎች አፈጻጸም ዙሪያ መመሪያ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን ለበርካታ ዓመታት ምንም አይነት የዕድሳት ሥራ ያልተከናወነለት በመሆኑ ለከፍተኛ ጉዳት ተዳርጎ መቆየቱን ተከትሎ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተእህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት አባታዊ መመሪያ ታኅሣሥ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ታቦተ ሕጉ ወጥቶ ወዲውኑ የዕድሳት ሥራው እንዲጀመር መደረጉ ይታወሳል።
በዘመን እርዝማኔና እርጅና ምክንያት በከፍተኛ ሁኔታ ለጉዳት ተዳርጎ የቆየው የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የዕድሳት ሥራ በአጭር ጊዜ ውስጥ በከፍተኛ ጥራትና ፍጥነት ተጠናቆ ሐምሌ 19 ቀን 2018 ዓ/ም ተመርቆ ታቦተ ሕጉ ወደ መንበረ ክብሩ ይመለሳል።ለዚህ ውጤታማ ሥራም የኮንትራት ሥራውን አሸንፎ የወሰደው አዶር ኮንስትራክሽን በተለይም ደግሞ የድርጅቱ ባለቤት ኢንጂነር አዲሱ ደመቀና የገዳሙ የአስተዳደር ሰራተኞችና የሥራ ኃላፊዎች የከፈሉት መስዋዕትነት በእጅጉ የሚደነቅ ነው።