ዚወልዳ ዱካ ቡኊታና ወልዳ ሥላሎ ጠቅላላ ማኅበራት ኚኊሮሚያ ክልል በክሚምት ወራት ዚሚያሠለጥኗ቞ውን መምህራን በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ዚሚሠሩትን ልዩ ልዩ ዚልማት ሥራዎቜንና ሙዚዹሙን ጎበኙ፡፡

አዲስአበባ -ኢትዮጵያ ዚወልዳ ዱካ ቡኊታና ወልዳ ሥላሎ ጠቅላላ ማኅበራት በፍኖተ ጜድቅ ጠቅላላ ማኅበር ድጋፍ ኚኊሮሚያ ክልል በክሚምት ወራት ዚሚያሠለጥኗ቞ውን መምህራን በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ዚሚሠሩትን ልዩ ልዩ ዚልማት ሥራዎቜንና ሙዚዹሙን ጎበኙ፡፡
ነሐሮ ፩ ቀን ፳፻፲፰ ዓም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተን ኹዹክፍለ ሀገሩ ጠርቶ ማስተማር፣ ማሠልጠን በጣም ትልቅ ሥራ ነውፀ እዚህ መጥታቜሁ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት እንድትጎበኙ ዚጥንቱንም አሁን ዚተሠራውን እንድትመለኚቱ ስለመጣቜሁ እንኳን ደህና መጣቜሁ” ብለዋል። ብፁዕነታ቞ው አያይዘውም “ስለ ቀተክርስቲያናቜሁ እንድታውቁ፣ እንድትሠለጥኑ ያደሚጉትን ዹፍኖተ ጜድቅ ባለቀት መጋቀ አእላፍ ጞጋዬን እናመሰግናለን፡፡” ሲሉ መልእክታ቞ውን እስተላልፈዋል፡፡
ዚወልዳ ሥላሎ ጠቅላላ ማኅበራት በኹፍተኛ ትምህርት ተቋማት ላይ አገልግሎት ዚሚሰጥ በ2010 ዓ.ም ዹተመሠሹተ ነው፡፡ ዚማኅበሩ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዲ/ን ጾጋው ታዬ እንደተናገሩት በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ልማት እያዚን ነው፡፡ ብዙ ለውጊቜ አይተናል እኛ ዛሬ ዚመጣነው ዚአባቶቻቜንን ፈለግ ተኚትለን ለቀተክርስቲያን ዘብ እንድንቆም፣ ኹዚህ ባገኘነው ትምህርት ጥሩ ነገር እንድንሠራ ነውፀ ባዚነው ለውጥ በጣም ደስ ብሎናል” ብለዋል፡፡
ወልዳ ዱካ ቡኊታ ጠቅላላ ማኅበራት ኹ2004 ዓ.ም ጀምሮ በኊሮሚያ ክልል አገልግሎት እዚሰጠ ዹሚገኝ ማኅበር ነው፡፡ ዚማኅበሩ ሥራ አስኪያጅ መጋቀ ሥርዐት ቀሲስ ኢንጅነር ፍቃዱ ኹበደ እንደተናገሩት በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት፣ ሙዚዹምና ዚልማት ሥራዎቜ ተዋውሹን ተመልክተናልፀ ልማቶቹ በጣም አስደናቂ ና቞ውፀ እኛ ክሚምት ዚምናሠለጥና቞ው ልጆቜ ይህን አጋጣሚ ተጠቅመው ዹጠቅላይ ቀተክህነቱን ልማት ተመልክተው ሲሄዱ በዚአጥቢያ቞ው ኹዚህ ባገኙት ልምድ እንዲሠሩ ለማድሚግ ነው ሲሉ ገልጞዋል፡፡
መ/ር ኀልያስ ሙላቱ ዹፍኖተ ጜድቅ ጠቅላላ ማኅበራት ዋና ሥራ አስኪያጅ እንደተናገሩት ማኅበሩ ኚሚያኚናውና቞ው ዘርፈ ብዙ ሥራዎቜ አንዱ ሥልጠና ነው፡፡ ወልዳ ዱካ ቡኊታ ጠቅላላ ማኅበራት 200 ዚሚሆኑ፣ ወልዳ ሥላሎ ጠቅላላ ማኅበራት ደግሞ ኹ30 ዩኒቚርስቲዎቜ 200 ተማሪዎቜ መጥተው በፍኖተ ጜድቅ ድጋፍ ለትምህርት ዚሚያስፈልጉ ቁሳቁሶቜን፣ ምግብ፣ ማደሪያ መማሪያ ክፍል በማመቻ቞ት ለሥልጠናውም ኹ15 ሚሊዹን ብር ወጪ መደሹጉን” ገልጞዋል፡፡ መ/ር ኀልያስ አያይዘውም በመንበሹ ፓትርያርክ እዚተሠራ ያለው ግቢውን ማስዋብ ልማትም ልዩ ነው፡፡ ይህም ለትውልዱ ልዩ ኩራት፣ ትልቅ ትምህርት ዚሚሰጥ ትልቅ ሥራ አይተናል፡፡ በሙዚዹሙም ያዚነው ዚቀተክርስቲያን ታሪክን ነውፀ ይህም ታሪክ ተጠብቆ በመቆዚቱ እኛም በማዚታቜን ዹቀደሙ አባቶቻቜን እንዎት ባለ መልኩ ይህቜን ቀተክርስቲያን ጠብቀው ለእኛ እንዳስሚኚቡን፣ ምን ዓይነት ቅርስ እንዳለን አይተናል፡፡ ይህን ታሪክ በማዹቮ ኮርቻለሁ፣ ተደንቄአለሁ፡፡ እኛ ደግሞ ይህን ታሪክ ማስቀጠል ኚእኛ ይጠበቃል” ሲሉ ገልጞዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጞሐፊ፣ ዚራያ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በጉብኝት ወቅት ባስተላለፉት መልእክት “በመንበሹ ፓትርያርክ ለጉብኝት በመምጣታቜሁ ልትመሰገኑ ይገባልፀ ሃይማኖታቜሁን ጠብቃቜሁ፣ ሥርዐታቜሁን አስኚብራቜሁ ቀተክርስቲያናቜሁን ማገልገል ኚሁላቜሁም ይጠበቃል” ሲሉ አባታዊ መልእክታ቞ውን አስተላልፈዋል፡፡©Eotc tv

አዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚትን በተመለኹተ በቋሚ ሲኖዶስ ኹተቋቋመው አጣሪ ኮሚ቎ ዹተሰጠ መግለጫ!

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ
በአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ዚሚስተዋለውን ዚመልካም አስተዳደር ቜግር ተኚትሎ ኹሀገሹ ስብኚቱ እስኚ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድሚሰ ዚተኚሰቱትን ቜግሮቜ ማለትም ሕገ- ወጥ ቅጥር፣ዕድገት ፣ዝውውር፣ሕገ- ወጥ ዚፋይናንስ አሰራሮቜና ዚገንዘብ ዝውውሮቜ፣
ሕገ -ወጥ ዚቊታና ዚቀት ኪራይ ውሎቜን ሕገ- ወጥ ተደራራቢ ሥራዎቜን ወዘተ …በዝርዝር በማጥናት ኚመፍትሔ ሐሳብ ጭምር ዚሚያቀርብ ኮሚ቎ በመሰዹም ወደ ሥራ እንዲገባ ማድሚጉ ይታወቃል።
በዚህም መሠሚት ዹተቋቋመው ኮሚ቎ ዚማጣራት ሥራው ውጀታማና ተቋም ተኮር፣እንዲሁም በሀቅ ላይ ዹተመሰሹተና በሀገሹ ስብኚቱ ዚሚስተዋለውን ቜግር ኚመሠሚቱ መፍታት ዚሚያስቜል ዚመፍትሔ ሐሳብ ዚሚቀርብበት መሆን ይቜል ዘንድ ዚቅድመ ማጣራት ስልቶቜን በመቀዚስ ዚማጣራት ሥራውን ለመጀመር ዚሚያስቜል እንቅስቃሎ በማድሚግ ላይ ዹሚገኝ ሲሆን በቀዳሚ ዕቅዱ ኚአካተታ቞ው ዋና ዋና ተግባራት መካኚል መሚጃዎቜን ዚመሰብሰብ፣ዚመተንተንና በዲጂታል ቮክኖሎጂ ዚማደራጀት ሥራ ዋነኛ ተግባሩ አድርጎ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል።
በመሆኑም በአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት በተለይም ደግሞ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ ኹፍ ሲል በተዘሚዘሩ ተግባራትና መሰል በሆኑ ዚመልካም አስተዳደር ቜግሮቜ ምክንያት ተጎጂ ዚሆናቜሁና በቂ ማስሚጃ ማቅሚብ ዚምትቜሉ ሁሉ ዘወትር በሥራ ሰዓት በእጃቜሁ ዹሚገኘውን ማስሚጃ ኮፒ በመያዝ በጠቅላይ ቀተ ክህነት ጜሕፈት ቀት ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በተኹፈተው ዹመሹጃ መሰብሰቢያ ቢሮ በመገኘት በድምጜና በምስል ጭምር መሚጃዎቜንና ማስሚጃዎቜን በመስጠት ዚማጣራት ሥራው ውጀታማ እንዲሆን ዚበኩላቜሁን አስተዋጜኊ ማበርኚት ዚምትቜሉ መሆኑን እዚገለጞ መሹጃና ማስሚጃ ዚሚሰጥ ማንኛውም አካል መሹጃ በመስጠቱ ምክንያት በሥራው ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳይደርስበት ኮሚ቎ው አስቀዶሞ በቋሚ ሲኖዶስ ዋስትና እንዲሰጥ ያደሚገ መሆኑን እዚገለጞ ያላቜሁን መሹጃና ማስሚጃ በነጻነት ማቅሚብ ዚምትቜሉ መሆኑን ኚወዲሁ ለማሳሰብ ይወዳል።
አጣሪ ኮሚ቎ው
ሐምሌ 29 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ

“መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ”

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሓዱ አምላክ፣ አሜን !
በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም ዚምትገኙ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን እምነት ተኚታዮቜ በሙሉ!
ዹሰውን ወገን ለማዳን ዹልጁ ማደሪያ ትሆን ዘንድ ድንግል ማርያምን ዹመሹጠ መፍቀሬ ሰብእ እግዚአብሔር ኣምላካቜን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዓሥራ ስምንት ዓመተ ምሕሚት ጟመ ማርያም ኣደሚሰን ኣደሚሳቜሁ!
“ወእመሰ ታፈቅሩኒ ዕቀቡ ትእዛዝዚ፡- ኚወደዳቜሁኝስ ትእዛዜን ጠብቁ” (ዮሐ.14፥15)ፀ
ፍቅር ዚሕያዋን ኣካላት ሹቂቅ መገናኛ ነው፣ ሕያዋን ኣካላት በውጫዊው ግዙፍ ኣካላ቞ው በተወሰኑ ጊዜያትና ቊታ ይገናኛሉ ፀ ስለ ጋራ ጉዳያ቞ውም በጋራ ይመክራሉፀ ይበልጥም ይቀራሚባሉ፡፡
ይሁንና ዚሕያዋን ኣካላት ግንኙነት በኣካል በጊዜና በቊታ ብቻ ዹተወሰነ ኣይደለም፣ በፍቅሹ መንፈስ ተገናኝተውም ይግባባሉ፣ ኚኣካላዊ ግንኙነት በላይ ዹበለጠም ይኾው ፍቅሹ መንፈስ ነውፀ ኹዚህ ኣንጻር እግዚአብሔርንም ማግኘት ዚምንቜለው በዚሁ ፍቅሹ መንፈስ ሆነን በእምነት ዓይን ነው!
ይህም በመሆኑ ሓዋርያው ቅዱስ ዮሓንስ በመልእክቱ “በፍቅር ዹሚኖር በእግዚአብሔርይኖራል፣ እግዚአብሔርም በእርሱ ይኖራል” በማለት ያስተምሚናል፣ (1ዮሐ. 4፥16) ይህም ማለት ኚሱ ጋር በፍቅር ስንገናኝፀ እሱም በኛ፣ እኛም በእሱ ዚመኖሩ ኩነት ይፈጠራል ማለት ነው፡፡
ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት!
ጌታቜን “አፍቅሮ ለእግዚአብሔር ኣምላክኚፀ- አምላክህን እግዚአብሔርን ውደደው” በማለት በፍጹም ልባቜን እንድንወደው፣ እንደዚሁም ራሳቜንን በምንወድበት መጠን እርስ በእርሳቜን እንድንዋደድ ማዘዙን እናውቃለንፀ
ዚመውደዳቜን መለኪያ ሚዛንና መገለጫ ምልክትም ትእዛዙን ማክበርና መጠበቅ እንደሆነ “ብትወዱኝስ ትእዛዜን ጠብቁ” በማለት ኣስተምሮናል
ኹዚህ ኣኳያ ጌታን መውደድ ማለት ትእዛዙን በመጠበቅ ዚሚገለጜ ግዙፍ ነገር እንጂ ምናባዊና ዚማይታይ ድብብቆሜ ነገር ኣይደለም ማለት ነው፣
ጌታቜንን ዚመውደድ ነገር ትእዛዙን በመጠበቅ ዚሚገለጜ ኹሆነ ትእዛዙ ምንድን ነው? ዹሚለውን ማዚት ኣስፈላጊ ይሆናልፀ ትእዛዙን በጥቅል ስናይ እግዚአብሔርንና ባልንጀራን በመውደድ እንደሚጠቃለል ራሱ ጌታቜን ኣስገንዝቊናል፣
በተለይም በባልንጀራቜን ላይ ዹምንኹተለው መውደድ ኹላይ እንደተገለጞው “እንደራስህ ኣድርገህ ውደድ” ተብለ በግልጜ ተቀምጊኣልፀ
ዹሰው ባልንጀራ እነማን ናቾው? በሕይወት ያሉት ናቾው? ወይስ ዚሞቱት? ወገን ዘመድ? ወይስ ዹሰው ወገን በሙሉ ዹሚለውንም ማወቅ ኣስፈላጊ ነው፡፡
ጌታቜን ነገሩን በዚህ ደሹጃ ለያይቶ ኣላስቀመጠም፣ ለምን? ቢባል ባልንጀራ ማለት ዹተወሰነን ዹማኅበሹ ሰብ ወገን ዚሚያሳይ ሳይሆን መላውን ዹሰው ወገን ዚሚገልጜ በመሆኑፀ እንደዚሁም ዚሞቱም ሆኑ ያለነው ሁላቜን በእሱ ፊት ሕያዋንና እርስ በእርሳቜን ባልንጀሮቜ በመሆናቜን ነውፀ
በመሆኑም መዋደዳቜንም ሆነ መኚባበራቜን በሕይወተ ሥጋ ሳለን ብቻ ሳይሆን ኚዚያም በኋላ እስኚ በሌለው ዕድሜ በመሆኑ ጌታቜን በጊዜ በቊታና በኹፊል ለይቶ ኣላስቀመጠም፡፡
ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት !
ኹነሐሮ ፩ ቀን ጀምሮ ለ፲፭ ቀናት ዚምንጟመው ዚጟመ ማርያም መነሻ ምክንያቱ ዚእግዚአብሔርትእዛዝና ፍቅር ነው፣
እግዚአብሔር ሰውን በኣጠቃላይ በተለይም ደግሞ እንደፈቃዱ ዚኖሩ ቅዱሳንን እንድናኚብርኣዞናል ክቅዱሳን ፍጥሚታት መካክል ደግሞ ቅድስት ድንግል ማርያም ዚመጀመሪያውን ደሹጃ ትይዛለቜፀ
ይህም በመሆኑ ኚፍጥሚት ወገን ኹሏ ክብር ዚሚደርስ ባለመኖሩ ኹሁሉም ኣብልጠን እናክብራታለንፀ
ኊርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን በዚህ ደሹጃ ዚድንግል ማርያምን ክብር ስትገልጜ ክእግዚአብሔርና ለባስያነ እግዚአብሔር ክሆኑ ቀደምት ኣበው ተምራ ነው!
በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዹነበሹው ዕውቁ ቅዱስና ዓለም ዓቀፋዊው አባት ቅዱስ ኀፍሬም ዚድንግል ማርያምን ክብር! ቅድስና እና ልዕልና ሲናገር “ይእቲ ተዓቢ እምኪሩቀል፡ ወትፈደፍድ እምሱራፌል፣ እስመ ኮነት ታቊተ ለአሓዱ ዘእምቅድስት ሥላሎ- እሷ ኚኪሩቀል ትበልጣለቜ! ኚሱራፌልም ትልቃለቜ፣ ኚቅድስት ሥላሎ ኣንዱ ለሆነው ታቊት ወይም ማደሪያ ሆናለቜና” በማለት አስተምሮናል፡፡
በመሆኑም ለስሟ መታሰቢያ በሆነው በዚህ ጟም ድንግል ማርያምን በዚህ ደሹጃ ስናክብርትእዛዙን እንጠብቃለንፀ ትእዛዙን በመጠበቃቜን ደግሞ እሱን መውደዳቜንን እናሚጋግጣለን ! እኛ ድንግል ማርያምን እንድንወዳት “እናታቜሁ” ብሎ እንዳዘዘ፣ እሷም ልትወደን “ልጆቜዅ ተብላ ታዛለቜና ስለኛ ትጞልያለቜ፡፡
በጞሎቷም ኚመኚራ ትታደገናለቜፀ በኣጠቃላይ በእግዚአብሔር’ በቅዱሳንና በእኛ መካኚል ያለው ግንኙነት በዚህ ትእዛዝና ፍቅር በትዕይንተ ዓለም ባለቜ ቀተ ክርስቲያን ዘንድ ዚተሳሰሚ ነው፡፡
ስለሆነም በዚህ ዚጟመ ፍልሰታ ለማርያም ሱባዔ ዚተራቡትን በመመገብ፣ ዚታሚዙትን በማልበስ፣ ዚተጣሎትን በማስታሚቅፀ ዚታመሙትንና ዚታስሩትን በመጠዚቅፀ ቅዱስ ቍርባንን በመቀበልና ለኃጢኣታቜን ዚንሥሐ ሥርዚትን በመለመን ሱባዔውን ልናሳልፍ ይገባል፡፡
በመጚሚሻም
በሀገራቜንም ሆነ በዓለም ዙሪያ ኚባድ ስጋት ዹሆነው ዚፍጥሚት ኣውዳሚ ጊርነትን በመለኮታዊ ጥበቡና ሥልጣኑ እንዲያስቆምልን በቅን ልቡናፀ በትሑት ሰብእና ሆነን እግዚአብሔርን በዚህ ሱባዔ እንድንጠይቀው ኣደራ ጭምር ኣባታዊ መልክታቜንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለንፀ
ዚተባሚኚና ዚተቀደስ ጟም ያድርግልንፀ
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቊቜዋን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ አሜን!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእስ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘኣኵስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት
ነሐሮ 1 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባፀ ኢትዮጵያ
ፎቶ Eotc tv

ዹመንበሹ ጞባዖት ቅድስት ሥላሎ ካ቎ድራል ያስገነባው 1B+G+8 ሕንጻ በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ ተመሚቀ።

ሐምሌ 25 ቀን 2018 ዓ.ም
ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ዹመንበሹ ጞባዖት ቅድስት ሥላሎ ካ቎ድራል ኚበኲሚ ምእመናን ኹበደ ተካልኝ በስጊታ ባገኘው በ22 ማዞሪያ ጎላጎል ሕንጻ አጠገብ ያስገነባው B+G+8 ሕንጻ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት ቡራኬ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል ።
በሕንጻው ምርቃት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜ/ቀት ዋና ሥራ አስኪያጅ ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋ እና ሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጞሐፊፀዚራያ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ፀ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ዚአዲስ አበባ ፣ ሀዲያ እና ስልጀ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ጥሪ ዹተደሹገላቾው እንግዶቜ ተገኝተዋል ።
ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሢራክ አድማሱ ዹመንበሹ ጞባዖት ቅድስት ሥላሎ ካ቎ድራል አስተዳዳሪ ዚእንኳን ደህና መጣቜሁ መልዕክት አስተላልፈው ጾሎተ ኪዳን ደርሷል።
ላዕኹ ሰላም ሜታው ብርሃኑ ዚካ቎ድራሉ ዋና ጾሐፊ ዚሕንጻው ሥራ ዹተመለኹተ ሪፖርት አቅርበዋል ።
በሪፖርታ቞ውም በኲሚ ምእመናን ኹበደ ተካልኝ ዹግል ይዞታ቞ውን 1636 ካሬ ሜትር ቊታ ለካ቎ድራሉ በስጊታ ዚሰጡ ሲሆን በዚህም በ1080 ካሬ ላይ ያሚፈ ኚምድር በታቜ ዚመኪና ማቆሚያ ጚምሮ ባለ 9 ወለል ያለው ባለ ሁለት ሊፍት ሕንጻ ሲሆን ለግንባታው 200,150,916.79 ወጪ መደሹጉን ገልጾዋል ።
ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሢራክ አድማሱ በሕንጻው ሥራ ያጋጠሙ ቜግሮቜ እና ዚተወሰዱ መፍትሔዎቜን ገልጾው በሥራው ድጋፍ ያደሚጉትን ባለድርሻ ተቋማት እና ግለሰቊቜ አመስግነዋል ።
ዚአዲስ አበባ ፣ ሐድያ እና ስልጀ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ይህ ሕንጻ በቀተክርስቲያን በዚክብሚ በዓላቱ ዹሚኹናወነው ጥላ መዘቅዘቅ እና ልመና በማስቀሚት ቀተክርስቲያን በኢኮኖሚ ራሷን ቜላ መንፈሳዊ እና ማኅበራዊ አገልግሎቷን እንድታኚናውን ዚሚያደርግ ነው ብለዋል።
ዚሕንጻ ግንባታ ሥራውም ሌሎቜ አድባራት እና ገዳማት ሊማሩበት ይገባል ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት ሕንጻው ሹጅም ጊዜ ወስዶ እንደ መሠራቱ አጚራሚሱ ያማሚ ዹሠመሹ ነው። ይኾም ለካ቎ድራሉ ዘላቂ ጥቅም ዚሚሰጥ ነው ብለዋል።
መርሐ ግብሩ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጾሎተ ቡራኬ ተጠናቋል።©ዚኢኊተቀ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/

ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ መምህራን ዚአሰልጣኞቜ ሥልጠና ዚምርቃት መርሐ ግብር ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ በተገኙበት በቅድስት ሥላሎ መ/ዮንቚርሲቲ ተካሔደ።

ሐምሌ፳፩ ቀን፳፻፲ወ፰ ዓ.ም
ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ ማደራጃ መምሪያ ሰንበት ትምህርት ቀቶቜ አንድነት ዹአህጉሹ ስብኚቶቜ ሰንበት ትምህርት ቀቶቜ መምህራን ዚአሰልጣኞቜ ሥልጠና ዚምርቃት መርሐ ግብር በቅድስት ሥላሎ ዩኒቚርስቲ መሰብሰቢያ አዳራሜ ብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት እያኚናወነ ይገኛል ።
በዕለቱም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጞሐፊ፣ ዚራያ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ቀለሜንጊስ ዹሰሜን ሾዋ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ እና ዚሰንበት ትምህርት ቀት ማደራጃ መምሪያ ዹበላይ ኃላፊ ሊቀጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ ዚደቡብ ኩሞ እና አሪ ዞኖቹቜ አህጉሹ ስብኚት ሊቀጳጳስ እና ዚቅድስት ስላሎ ዩኒቚርስቲ ፕሬዚዳንት ፣ ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ አንድነት መምሪያ ኃላፊዎቜ እና ጥሪ ዹተደሹገላቾው እንግዶቜ ተገኝተዋል ።
ትምሐርቱ ኹ37 አህጉሹ ስብኚቶቜ ለተወጣጡ 300 ሠልጣኞቜ ኹሐምሌ 6 እስኚ 20 ለተኚታታይ 14 ቀናት ዹተሰጠ ሲሆን በዋናነትም መሠሚታዊ ዚሥርዓተ ትምህርት ማስተግበሪያ ዘዎዎቜ እንደተሰጠ ተጠቁሟል ። ሥልጠናውም በተለያዩ ዚኢትዮጵያ ቋንቋዎቜ ዚታገዘ እንደነበር እና ሠልጣኞቹ 60 በመቶ በክህነት ማዕሹግ ላይ ያሉመሆና቞ው ተገልጿል ።
©ዚኢኊተቀ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/