“ተመራቂዎች በየተሰማሩበት የስምሪት መስክ ሁሉ እንደ መብራት ሊያበሩ ይገባል” ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ
(ሰኔ 20 ቀን 2018 ዓ.ም )አንጋፋውና ታሪካዊው የባቱ (ዝዋይ) ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳምና ሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ በሥራ አመራር የዲፕሎማ መርሐ ግብር ያሰለጠናቸውን 23 ደቀ መዛሙርት እንዲሁም በ67ኛው ዙር የሦስት ወራት የካህናት ማሠልጠኛ ክፍል የተከታተሉ 36 ዕጩ አገልጋዮችን በድምሩ 59 ተተኪ መምህራንንና አገልጋዮችን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በታላቅ ድምቀት አስመርቋል።
ይህ ታላቅ የምረቃ መርሐ ግብር በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የጋራ ጸሎት የተከፈተ ሲሆን፣ የዕለቱ የቅዱስ ወንጌል ንባብ በብፁዕ አቡነ ማርቆስ አማካኝነት ቀርቦ ሥነ-ሥርዓቱ በይፋ ተጀምሯል።
በበዓሉ ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ፣ የኮሌጁና የገዳሙ የበላይ ኃላፊ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ አባል እንዲሁም የኢትዮጵያ ሃይማኖቶች ተቋማት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (ሳልሳዊ) እና ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የኮሌጁና የገዳሙ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፦ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የእንኳን ደህና መጣችሁ፣ ለተመራቂ ደቀ መዛሙርት ደግሞ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት በማስተላለፍ ሰፊ አባታዊ መመሪያና ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል።
ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክትም ፦ “የተማራችሁት የሥራ አመራር ሳይንስና የተቀበላችሁት የካህናት ሥልጠና፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በዘመናዊ አሠራርና በጥንታዊው መንፈሳዊ ሥርዓት አስተባብሮ ለመምራት ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው” ብለዋል።
አያይዘውም ተመራቂዎች በየተሰማሩበት የስምሪት መስክ ሁሉ እንደ መብራት አብርተው፣ እንደ ጨው አልጭተው፣ የወቅቱን ፈተናዎች በጽናት በማሸነፍና ትውልዱን በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር በመቅረጽ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮና ትውፊት በተግባር እንዲያስጠብቁ አደራ ብለዋል።
በተለይም ደግሞ በዕውቀትና በአገልግሎት እጥረት ምክንያት ፈተና በበዛባቸው የአህጉረ ስብከቱ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ላይ በመገኘት፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተማርና ወንጌልን በማስፋፋት አገልጋይነታቸውን ይበልጥ እንዲያጠናክሩ መመሪያ ሰጥተዋል።
በመቀጠል ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ባስተላለፉት ቃለ ምዕዳን፣ እርሳቸውም የዚሁ የቅዱስ ገብርኤል ገዳም ፍሬ መሆናቸውን በኩራት ገልጸው ታሪክን ወደ ኋላ በመመለስ የገዳሙን መሠረት አስታውሰዋል። ትናንት በችግርና በጥቂት ጅማሮ የነበረው ገዳም፣ ዛሬ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ መሪነት ሁለንተናዊና አርአያነት ያለው የልማትና የትምህርት ማእከል መሆኑን በማነጻጸር አብራርተዋል። ይህ ስኬት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሆነ አገርን ለሚረከበው ተተኪ ትውልድ ያለው ፋይዳ የላቀ መሆኑን ገልጸዋል።
የገዳሙ አበምኔት ሊቀ ሊቃውንት ቆሞስ አባ አትናቴዎስ በበኩላቸው፣ የ67ኛ ዙር የካህናት ሥልጠና 36 ደቀ መዛሙርት መመረቃቸውን አብስረው፣ የገዳሙን ታሪካዊ ጉዞና ልማት አብራርተዋል።
አበምኔቱ ባደረጉት ንግግር፤ የቀድሞው የሸዋ ክፍለ ሀገር ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (ካልዕ) የነበረውን ታላቅ ራእይና ዓላማ በመንተራስ፣ የአሁኑ የገዳሙ የበላይ ጠባቂና የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (ሳልሳዊ) ላለፉት 31 ዓመታት ገዳሙ ዛሬ ለደረሰበት የከፍታ ደረጃ እንዲበቃ የከፈሉትን ታላቅ መሥዋዕትነትና ያሳዩትን የረጅም ርቀት አርቆ አሳቢነት በዝርዝር አብራርተዋል።
አያይዘውም በብፁዕነታቸው አርቆ አሳቢነትና መሪነት ተቋሙን ወደ ፊት ወደ “ዩኒቨርሲቲ” ደረጃ ለማሳደግ ታላቅ ዓላማ ተይዞ በገዳሙ ውስጥ የማይጠፉ ዘላቂ አሻራዎች እየተቀመጡ መሆናቸውን ገልጸው፤ በባቱ ከተማ ላይ እየተገነባ የሚገኘውን ግዙፍ የG+8 ሕንጻ የግንባታ ሂደት በመጥቀስ፣ ገዳሙ ወደፊት በራስ አገዝ ልማት ራሱን እንዲያስተዳድር እየተደረገ ያለውን ጥረት ገልጸዋል።
የሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጁ ዲን መጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ ታፈሰ ስለ ተቋሙ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ማብራሪያ ሰጥተዋል። ኮሌጁ በአሁኑ ወቅት 5ኛ ዙር ላይ መድረሱንና እስካሁን 123 ደቀ መዛሙርትን ማፍራቱን ጠቅሰው፣ ዘንድሮ ደግሞ 23 ተማሪዎችን ለምረቃ ማብቃታቸውን ገልጸዋል። ኮሌጁ ከአራቱም አቅጣጫዎች ከተለያዩ አህጉረ ስብከት መሥፈርቱን አሟልተው የመጡ ሰልጣኞችን ተቀብሎ የሚያስተምር መሆኑን ጠቁመው፤ የሥራ አመራር ተማሪዎቹ በቆይታቸው ከተለመደው ትምህርት በተጨማሪ በገዳሙ የአብነት ትምህርት ቤት ውስጥ በመግባት የቅኔ ትምህርት መቁጠራቸውን በልዩ ስኬትነት አንስተዋል። አያይዘውም ኮሌጁ አድማሱን በማስፋት በአዲስ አበባ፣ በአዳማና በአርባ ምንጭ በርቀት የትምህርት መርሐ ግብር እያስተማረ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዕለቱ የኮሌጁ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ተባባሪ ፕሮፌሰር ቀሲስ ሙሉጌታ ስዩም በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልእክት አስተላልፈዋል።
የባቱ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ሁስማን ተስሔ በምረቃው ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፣ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር የምታስተምረው ሰላምን መሆኑን ገልጸው፤ ገዳሙ ከመንፈሳዊ አገልግሎቱ ጎን ለጎን ማኅበረሰቡን በሥራ አመራር ሳይንስ ማስተማሩና በልማት ላይ እያሳየ ያለው ከፍተኛ ተሳትፎ ለአካባቢው ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አረጋግጠዋል። ልማትና ሰላም የማይነጣጠሉ መሆናቸውን በመግለጽ፣ በጥቂቱ የተጀመረው ይህ ታላቅ ተቋም ዛሬ ለደረሰበት የከፍታ ደረጃ ለገዳሙና ለአባቶች የላቀ ምስጋና አቅርበዋል።
በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ማጠናቀቂያ ላይ፣ በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ ከ1ኛ እስከ 3ኛ ለወጡ የደረጃ ተማሪዎች የተዘጋጀው ልዩ የክብር ሽልማት፤ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እጅ የተበረከተላቸው ሲሆን፣ ተመራቂዎቹም የአባቶችን አምላካዊ ቡራኬ በመቀበል ሽልማታቸውን ተረክበዋል።
በዚህ ደማቅ የበዓል መርሐ ግብር ላይ በገዳሙ የቅኔ መምህርና በተመራቂ ደቀ መዛሙርት አማካኝነት ቅኔ እንዲሁም ያሬዳዊ ወረብ ቀርቦ ሥነ ሥርዓቱ በጸሎት ተጠናቋል።
በምረቃ ሥነ- ሥርዓቱ ላይ የሀገረ ስብከታችን ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የሀገረ ስብከታችን ም/ሥራ አስኪያጅ: የሀገረ ስብከታችን የመመሪያው ክፍል ኃላፊዎች፣ የኮሌጁና የገዳሙ የየክፍሉ ኃላፊዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፣ ተመራቂዎችና ወላጆቻቸው አባ ገዳዎች አደ ሥንቄዎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የዕለቱን ታላቅ የምረቃ ሥነ-ሥርዓትና አጠቃላይ መርሐ ግብር በብፁዕነተታቸው አባታዊ መመሪያ እና በወጣው ቅደም ተከተል መሠረት በከፍተኛ ትጋት የመሩት የሥራ አመራር ኮሌጁ የሬጅስትራር ክፍል ዋና ኃላፊ መምህር ዲበ ኩሉ ጌታነህ እና በአፋን አሮሞ የገዳማችን ቁጥጥር ናቸው።”
© ሐመረ ተዋሐደ ሚዲያ