ዚብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ እንኳን አደሹሰዎ መርሐግብር በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ጜሐፈት ቀት በደማቅ መንፈሳዊ ስነስርዓት ተካሄደ

ሚያዚያ ፭ ቀን ፪፻ ፲ወ፰ዓ.ም.
ኢኊተቀክ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
አዲስአበባ , ኢትዮጵያ
በዚዓመቱ በትንሣኀ ማግስት ፣ በአዲስ ዓመት ማግስትና በጌታቜን በኢዚሱስ ክርስቶስ ዚልደት በዓል ማግስት ኹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ጜሕፈት ቀት ጀምሮ እስኚ አዲስአበባ ሀገሹ ስብኚት አድባራትና ገዳማት አገልጋዮቜ በመሰባሰብ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ዚእንኳን አደሹሰዎ መርሐግብር ይካሄዳል።
በዚሁ መሠሚት ዚዘንድሮ ዹ2018ዓ.ም ዚትንሣኀ በዓል ምክንያት በማድሚግ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ጜሕፈት ቀት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ዚምስካዚ ኅዙናን መድኀኔዓለም ገዳም ዹበላይ ኀላፊ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊ ፣ ዚራያ ስድስቱ ወሚዳዎቜ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ዚቅርሳቅርስ ወመዘክርና ቀተመጻሕፍት ፣ ዚማሕበራት ምዝገባ ፣ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያዎቜ ዹበላይ ኀላፊ፣
ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ዚአዲስአበባ፣ ዚሐድያና ስልጀ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዓን አበው ለቃነ ጳጳሳት፣
ንቡሚእድ ኀልያስ አብርሃ በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት በመንፈሳዊ ዘርፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ
ሚ/ፕ ግርማ ባቱ (ቀሲስ) ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ፣
መ/ም አባ ገብሚ መድኅን ንጉሀ ዚአዲስአበባ ሀገሹ ስብኚት ዋና ሥራ አስኪያጅ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክልነት ጜሕፈት ቀት ኹፍተኛ ዚሥራ ኀላፊዎቜና ሠራተኞቜ ፣ዚአዲስ አበባ ሀገሹ ስብኚት ኹፍተኛ ዚሥራ ኀላፊዎቜና ሠራተኞቜ፣ዚአዲስአበባ ሀገሹ ስብኚት አድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎቜ ፣ዚሰንበት ትምህርት ቀት ወጣቶቜ ፣ጥሪ ዹተደሹገላቾው እንግዶቜ በተገኙበት መርሐግብሩ ተካሂዷል።
መርሐግብሩ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃና ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት መሪነት ዚደብሚ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቀተክርስቲያን አገልጋይ ካህናት ጾሎተ ወንጌል አድራሜነት በጞሎት ዹተኹፈተ ሲሆን ዚበርካታ ሊቃውንት መፍለቂያ በሆነውና በአንጋፋው በሰዋስዋወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርትና መምህራን አማካኝነት ያሬዳዊ ዜማ መነሻነት ዚእለቱ ተኚታታይ መርሐግብራት መቅሚብ ጀምሚዋል።
ኚሊቃውንቱ ያሬዳዊ ዜማ በመቀጠል ዚአዲስአበባ ሀገሹ ስብኚት አድባራትና ገዳማት ተወካዮቜ ዚትንሣኀውን ምስጢር በሚያብራራ መቅድም በመነሣት በልጅነት መታዘዝ ለቅዱስነታ቞ው ዚእንኳን አደሹሰዎ መልእክት በጜሑፍ አቅርበው በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ጜሕፈት ቀት ዚሰንበት ትምህርት ቀቶቜ ማደራጃ መምሪያ ማዕኚላውያን ዚሰንበት ትምህርት ቀት አባላትና ዹጋሞኛ ዘማርያን በያሬዳዊ ዜማ ቅዱስነታ቞ውን እንኳን አደሹሰዎ ብለዋል።
በመቀጠልም ሊቃውንተ ቀተክርስቲያን እለቱን ዚሚመለኚት ቅኔ በማቅሚብ መርሐግብሩ ቀጥሏል። ኚሊቃውንቱ ቅኔ በመቀጠል ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ጜሕፈት ቀት ዋና ሥራ አስኪያጅ ለቅዱስነታ቞ው ዚእንኳን አደሹሰዎ መልእክት ሲያቀርቡ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥሚት ነው በሚል ሐይለ ቃል በመነሳት ዚአሮጌው ዘመን ልዩ መገለጫ ዹሆነውን ስንፍና በሥራ ጥላቻን በፍቅር በመተካትና ዛሬን ዚሰጡንን ዚአባቶቻቜንን ውለታ ባለመርሳት ዚቅድስት ቀተክርስቲያንን ይዞታዋን ማስኚበር፣ ዚተጀመሩ ሕንጻዎቜን ማስፈፀም፣ ቅጥር ጊቢውን ውብና ጜዱ ለማድሚግ ዚቅዱስነታ቞ው ጞሎትና አባታዊ መመሪያ ዋጋው ላቅ ያለ መሆኑን ገልጾው ቅዱስነታ቞ው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ እንዲሰጡ ጋብዘዋል።
በመጚሚሻም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ በዚህ መልኩ በተዘጋጀው ዚእንኳን አደሹሰዎ መርሐግብር ደስተኛ መሆናቾውን ገልጾው ጌታቜን እና መድኀኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር በሥጋ ማርያም በመገለጥ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሥጋውን ዹቅሹሰውና ደሙን ያፈሰሰው ይህንን ዓለም ለማዳንና ለማደስ ነው።
እግዚአብሔር ይህንን ዓለም አመቻቜቶ ክቡር ለሆነው ለሰው ልጅ ሲሰጥ በሰውና በእግዚአብሔር መካኚል ያለውን ዚጥል ግድግዳ በማፍሚስና ዚዲያብሎስን ስልጣን በመሻር ነበር። ነገር ግን ዹተኹፈለልንን ዚክርስቶስ ዋጋ ዚሚሳ በሚመስል መልኩ እርስ በእርሳቜን እዚተበላላን እንገኛለን በማለት ማንኛውም አማኝ በተኚፈለለት ልክ እንዲኖር አባታዊ መመሪያ ሰጥተው በቅዱስነታ቞ው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ዹበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ በ2018 ዓ.ም ዚትንሣኀ በዓል ዚእንኳን አደሹሰዎ መርሐ ግብር ላይ ያስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚኚተለው ይነበባል

“ወይእዜሰ በክርስቶስ ተሐድሰ ኵሉ ወኃለፈ ዘትካት ወናሁ ኮነ ሐዲስ ኵሉ 
 ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥሚት ነውፀ አሮጌው ነገር አልፏል እነሆ ሁሉም አዲስ ሆኗል” (2.ቆሮ 5÷17)
❖ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖትፀ
❖ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚራያ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስፀ
❖ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ዚአዲስ አበባ፣ ዚሐዲያና ስልጀ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ
❖ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት
ክቡር ንቡሚ ዕድ ኀልያስ አብርሃ በመንበሹ ፓትርያርክ ጠ/ቀ/ክ ዚመንፈሳዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅፀ
ክቡር ሚዳት ፕሮፌሰር ግርማ ባቱ በመንበሹ ፓትርያርክ ጠ/ቀ/ክ ዚማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅፀ
ክቡራን ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠ/ቀ/ክ ዚዚመምሪያውና ዚዚድርጅቱ ኃላፊዎቜፀ
ክቡራን ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠ/ቀ/ክ ሠራተኞቜፀ
ክቡራንና ክቡራት በዚህ መንፈሳዊ መርሐ ግብር ዚተገኛቜሁ በሙሉ
በአምላካዊ ሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ፣ ብርሃንን ተጎናጜፎ፣ ኚሙታን ዚተነሣው፣ ሕያው እግዚአብሔር ቅዱስነታ቞ውን በሕይወት ጠብቆ አሮጌው ነገር አልፎ ዚአዲስ ሕይወት ኑሮ ለተጀመሚበት በዓለ ትንሣኀ እንኳን አደሹሰዎ በማለት ለቅዱስነትዎ ያለኝን ክብር በመላው ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተ ክርስቲያን ሠራተኞቜ ስም ስገልጜ ምሉዕና ፍጹም በሆነ ደስታ ነው። (1.ቆሮ 15÷54)
ዚአዲስ ፍጥሚት ምሥጢር ሰው ትንሣኀ ልቡና አግኝቶ በኢዚሱስ ክርስቶስ ሲያምን ዹሚኖሹውን አዲስ ሕይወትና ኚአሮጌው ማንነቱ መለዚቱን ዚሚያሚጋግጥ ጥልቅ ዹሆነ ትርጉም ያለው በመሆኑ ትንሣኀውን እንደ ኃላፊ ኩነት ብቻ አስበን ዹምናልፈው አይደለም።
ዚክፋት ሁሉ ምንጭ ዹሆነው ዲያብሎስ በመሻሩ ዹሰው ልጅ ውጫዊ ዚሕይወት ለውጥን ብቻ ሳይሆን ፍጹም ዹሆነ ውስጣዊ ለውጥን ስላገኘ ትንሣኀው በዕለት ተዕለት ዚክርስትና ሕይወት ውስጥ ሁል ጊዜ ዚሚገለጥ አሁናዊ ጉዳይ ነው።
ኚሞት በኋላ በሚቀጥል ሕይወት፣ አዲስ ፍጥሚት ሆነን ለነፍሳቜን ድኅነት ያገኘንበት ዚክርስቶስ ትንሣኀ በድካም ጊዜ ብርታት፣ በፈተና ጊዜ ሕያው ተስፋ፣ በጭንቀት ጊዜ ሰላም ኹመሆኑም በላይ ክርስቶስ እኛን ዚወደደበት ዚታላቅ ፍቅሩ መገለጫ ነው።
በመሆኑም ክርስትና ሃይማኖታቜን እርሱን መሠሚት አድርጎ ዚቆመበት ትንሣኀው ታሪክ ብቻ ሳይሆን ዛሬም በሕይወታቜን ላይ ዚሚሠራ ኃይል፣ ዹጹለማው መጚሚሻ፣ ኚጥፋት መንገድ ዚወጣንበት ዚንጋቱ መጀመሪያ መሆኑ አያጠያይቅም።
ዚመልእክታቜን መነሻ ዹሆነው ሐዋርያዊ ቃልም «አሮጌው ነገር አልፎ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆኗል» ዹሚል ነው። ዚክርስቶስ ትንሣኀና ዚምሥራቹ ዜና እስኪሰማ ድሚስ ዹሰው ልጅ ያሳለፈው ዚመኚራ ዘመን ዚሚሚሳ አይደለምና አዲስ ዹሆነው ነገር ኚአሮጌው ጋር መነጻጞሩ ዹማይቀር ነው።
በክርስቶስ ቀዛነት ዹተደሹገልን ድንቅ ነገር ለመሚዳትም ኹአለፈው መነሣት ዚግድ ነው። ዚሐሳብ ቅንነት ዚጠፋበት፣ ዚመንፈስ ድካም ዚነበሚበት ያ! አሮጌው ነገር በክርስቶስ አልፎ ዛሬ አዲስ ዚትንሣኀ ሕይወት አግኝተናል። በዚህም ሰው ሆኖ ያዳነን፣ በትንሣኀው አዲስ ሕይወት ዹሰጠንን አምላክ እናመሰግናለን።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታቜንፀ
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትፀ
ክቡራንና ክቡራት በዚህ ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መርሐ ግብር ዚተገኛቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜንፀ
ክርስቶስ ላንቀላፉት ሁሉ በኩራት ሆኖ በመነሣቱ በሰው ልጅ ሕይወት ዹነበሹው ሥቃይና መኚራ አልፎፀ ሁሉም ነገር አዲስ በሆነበት ዚምሕሚት ዘመንፀ ዚአሮጌው ማንነት መገለጫ ስንፍና፣ በሥራ ሲሞነፍ፣ ጥላቻ በፍቅርና በልማት ሊተካ አልቻለም ባይነት፣ አይቻልም ማለት በትንሣኀ ሕይወት ውስጥ ቊታ ዚላ቞ውም። (1.ቆሮ 15÷20)
በዚህ ዚሕይወት ጉዞ ዚቅድስት ቀተ ክርስቲያናቜን ሁለንተናዊ ተልዕኮና ራስን ዚመቻል ሁኔታ ዹተሟላ እንዲሆን ዚደኚሙፀ እነርሱ እዚተራቡና እዚተጠሙ ዚእኛ ዚልጆቻ቞ው ኑሮ እንዲሻሻል በመታመን አክብሚው ዚሠሩ ቀደምት አባቶቻቜንን ዚሚያስታውሱ በርካታ ዚልማት ሥራዎቜ በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በቅዱስነትዎ ጞሎትና አመራር ሰጪነት እዚተኚናወኑ ይገኛሉ።
ቀደም ሲል ተጀምሹው ያልተጠናቀቁ ዹሕንፃ ግንባታዎቜና በአዲስ መልክ ዚሚሠሩ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶቜ በታቀደላ቞ው ጊዜ ተጠናቅቀው መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲሰጡ ለማድሚግ ተግተን በመሥራት ላይ እንገኛለን።
ኹዚህም ጋር ዚተቋማት ማንነትና አሠራር ዚሚለካው በሚገለገሉባ቞ው ጜ/ቀቶቜ አያያዝና በሥራ አፈጻጞማ቞ው ስለሆነ ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላላ ቀተ ክህነት ይዞታን በማስኚበር ጜዱና ውብ ሥፍራ ዚማድሚግ ሥራው በመገባደድ ላይ ይገኛል።
ያለ አግባብ ዚተኚማቹ ንብሚቶቜም ተገቢውን መፍትሔ እንዲያገኙፀ ዚግቢው ጜዳትና ውበት እንዲጠበቅ ዚማድሚግ ሥራ ብዙ ጊዜና ጉልበት ዹሚጠይቅ ዹነበሹ ቢሆንም በሁሉም ዚቀተ ክህነታቜን ዚሥራ ኃላፊዎቜና ሠራተኞቜ ተሳትፎ በአግባቡ ተኚናውኗል።
በመሆኑም ሥልጣነ ሞት ዚተሻሚበትን ዚክርስቶስ ትንሣኀ ዛሬ በዚህ መልኩ ተሰብስበን በቅዱስነትዎ በራሄ ዚምናኚብሚው ኹፍተኛ በሆነ ዚሥራ መነቃቃት ነው።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታቜንፀ
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትፀ
ክቡራንና ክቡራትፀ
ትንሣኀ ዚሥጋ መነሣት ብቻ አይደለም በእግዚአብሔር ቀት ሊሠራ ዚሚገባውን ሥራ በመሥራት ለኃጢአት ሞቶ፣ በአዲስ ሕይወት መኖር ማለት ነው። ትንሣኀ ልዩነትን ይሻገራል፣ በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባር ዚሚታይ አንድነትንም ይፈጥራል። ኚኃጢአት መራቅን፣ በፍቅር መኖርንና በተስፋ መጓዝን ያጎናጜፋል። ሰው ብቻውን ሲሠራ ውጀቱ ውስን ነውፀ በጋራ መሥራት ግን እጅግ ኹፍተኛ ዋጋ ያለው በትንሣኀው ዹተገኘ ዚሕይወት መርሕ ነው።
ቅድስት ቀተ ክርስቲያናቜን ዛሬ ያለቜበት ደሹጃ ላይ እንዲሁ በቀላሉ አልደሚሰቜም። በትንሣኀው ዹተገኘው አንድነት ዹበጎ ሥራ ሁሉ መሠሚት መሆኑን በተሚዱት፣ ለክብሚ ስማ቞ው ይህን መታሰቢያ ትተውልን ባለፉት አባቶቻቜንና እናቶቻቜን ኹፍተኛ ጥሚት ነው። ዛሬ እኛ እዚገነባን ያለነው እነርሱ ባኖሩት መሠሚት ላይ ነው።
በመሆኑም ጊዜው ዚሥራ ጊዜ ነውና አሁን ያለነው ዚቀተ ክርስቲያን አባቶቜና ምዕመናን ዚእምነታቜንን ታሪክ ኚሥርዓተ አምልኮው ጋር ዹመጠበቅና ዚማስጠበቅ፣ ለመንፈሳዊና ማኅበራዊ ዕድገት ልማትን አስፋፍቶ ዚመሥራት ኃላፊነት አለብን።
ስለዚህ በአዲስ መንፈስና በአዲስ ሕይወት እዚተመላለስን ዚትንሣኀውን ብርሃን በማውጅ ለሀገር ሰላም፣ ለቀተ ክርስቲያን አንድነትና ለሐዋርያዊ ተልዕኮ መስፋፋት ሁሉም ዚቀተ ክርስቲያናቜን አገልግሎቶቜ ለጥንታዊ ታሪካቜን በሚመጥን መልኩ ድርሻቜንን ልንወጣ ይገባል።
በታላቁ ዐቢይ ጟም ለሃምሳ አምስት ቀናት ያለ ዕሚፍት ስታገለግሉ ኚርማቜሁ ደኹመን ሳትሉ በተቀደሰው ኊርቶዶክሳዊ ትውፊት መሠሚት ቅዱስ አባታቜንን እንኳን አደሚሰዎት ለማለት ዚሁላቜን ማዕኹል ወደ ሆነው መንበሹ ፓትርያርክ መጥታቜሁ ዚበሚኚቱ ተካፋዮቜ ዚሆናቜሁትን ሁሉ በቅድስት ቀተ ክርስቲያናቜን ስም ኚልብ እናመሰግናቜኋለን።
በመጚሚሻም ቅዱስ አባታቜን በልጁ ሞት ይቅር ያለን አምላካቜን እግዚአብሔር በጞሎት፣ በሐሳብ ካልተለዚዎትና ሁልጊዜም ኚማይለዚዎት ሕዝበ ክርስቲያን ጋር በሰላም፣ በጀና ጠብቆ እንኳን ለ2018 ዓ/ም በዓለ ትንሣኀ በድጋሚ አደሹሰዎ እያልኩ መልእክ቎ን በዚህ አጠቃልላለሁ።
ዚቅዱስነትዎ ቡራኬ አይለዹን
አባ ሳዊሮስ
ዹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላላ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅፀ
ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስፀ
ዚምስካዬ ኅዙናን ገዳም ዹበላይ ኃላፊፀ
ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ/ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያንና ዳሜን ባንክ አኚሰስዮን ማኅበር ሊስት መቶ ለሚሆኑ ዝቅተኛ ገቢ ላላቾው ምዕመናን ዹበዓል መዋያ ድጋፍ አደሹጉ

ሚያዚያ፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ገቅላይ ጜሕፈት ቀት ኚዳሜን ባንክ አክስዮን ማኅበር ጋር በመተባበር ሊስት መቶ ለሚሆኑ በዝቅተኛ ዚኑሮ ደሹጃ ላይ ለሚገኙ ምዕመናን ዚ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም ዚትንሣኀ በዓልን ምክንያት በማድሚግ ለእያንዳንዳ቞ው አምስት ሌትር ዘይትና አሥር ኪሎ ዱቄት በዛሬው ዕለት በጠቅላይ ቀተክህነት ጜሕፈት ቀት ቅጜር ጊቢ በተኹናወነ ዚልገሳ መርሐ ግብር ድጋፍ አድርገዋል።
በዚሁ ጊዜ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት እንደ ትንሣኀ ያሉ ሃይማኖታዊ በዓላትን በምናኚብርበት ጊዜ ያለንን ለሌላቾው በማካፈልና ጌታቜን፣አምላካቜን፣መድሃኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ያስተማሚንን በመተግበር መሆን ስላለበት ዳሜን ባንክ አክሲዮን ማኅበር ይህን መርሐ ግብር እንዲዘጋጅ በማድሚጉ ልባዊ ምስጋናቜንን እናቀርባለን በማለት በዓሉ ዚደስታና ዚበሚኚት በዓል እንዲሆን መልካም ምኞታ቞ውን ገልጞዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ ዚተገኙት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚራያ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ በበዓል ወቅት አቅመ ደካሞቜን ማገዝ ተገቢ መሆኑን ጉግጾው ዳሜን ባንክን አመሰግነዋለሁ ግነዋል።
ዚዳሜን ባንክ አክስዩን ማኅበር ዚማርኬቲንግና ብራንዲንግ ዳይሬክተር አቶ እንዳለ ገብሚስላሎ ባስተላለፉት መልዕክት
ባንኩ በዚህ ዓይነት ማኅበራዊ አገልግሎት ዙሪያ በመሰማራቱ ኹፍተኛ ደስታ እንደተሰማው ገልጞዋል።ዚልገሳ መርሐ ግቀሩ ተጠቃሚ ዹሆኑ ምዕመናንም ለተደሹገላቾው ድጋፍ ምስጋና቞ውን ያቀሚቡ ሲሆን በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ጾሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት፣ዚጌታቜን ዚአምላካቜን ዚመድኃኒታቜን ዚኢዚሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኀን በማስመልኚት ዚእንኳን አደሚሳቜሁ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ

ዚቅዱስነታ቞ው አባታዊ መልዕክት እንደሚኚተለው ይነበባል።
ቃለ በሚኚት ዘብፁዕ ወቅዱስ ኣቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገሹ በበዓለ ትንሣኀሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢዚሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕሚትፀ
በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ ኣምላክ ኣሜን፡-
በሀገራቜን በኢትዮጵያ በገጠርና በኹተማ ዚምትኖሩ፣
ኹሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር ዚምትገኙ፣
ዚሀገራቜንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስኚበር በዹጠሹፉ ዚቆማቜሁ፣
በሕመም ምክንያት በዹፀበሉና በዚሆስፒታሉ ያላቜሁ፣
እንዲሁም ዹሕግ ታራሚዎቜ ሆናቜሁ በዚማሚሚያ ቀቱ ዚምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፣
በቀዛዊ መሥዋዕትነቱ ኹሞተ ኃጢኣት ታድጎ ዚትንሣኀ ሙታንን በር ዹኹፈተልን ጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኀው በሰላም ኣደሚሰን ኣደሚሳቜሁ!
‹‹ወኣነ እሜጡ ነፍስዚ ቀዛ ኣባግዕዚ ኹመ ካዕበ ኣንሥኣፀ
ዳግመኛ ኣነሣት ዘንድ ነፍሮን ዚበጎቌ ቀዛ ኣድርጌ እሰጣለሁ (ዮሓ 10÷17)
ጌታቜን ኣምላካቜንና መድኃኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ በሰብኣዊ ክዋኔው ሰው ቢሆንም በመለኮታዊ ክዋኔው ዚኣብና ዚመንፈስ ቅዱስ ቃል ወይም ወልደ እግዚአብሔር ነውፀ
በመሆኑም በሰብኣዊ ክዋኔው መዋቜ ሲሆን በመለኮታዊ ክዋኔው ተነሜና ኣንሺ ነውፀ ኹዚህ ኣንጻር ሥግው ቃል ሁለቱንም ተግባራት በኣንድ ኣካልና ክዋኔ ዹመፈጾም ሥልጣን ኣለውፀ ይህም በመሆኑ ራሎን ዹማኖርና ዚማንሣት ሥልጣን ኣለኝ በማለት እውነታውንና ምንነቱን ኣሳዚፀ
ጌታቜን ይህንን ኣስመልክቶ ኚመሞቱና ኚመነሣቱ በፊት ለቅዱሳን ሓዋርያት በተደጋጋሚ ኣስሚድቶኣልፀ ስለሆነም ዚጌታቜን ሞትና ትንሣኀ ድንገተኛና ዚግድ ሳይሆን ታውቆ ያደሚና ዚውድ እንደሆነ ኹዚህ እውነታ እንሚዳለንፀ
ጌታቜን ይህንን ተግባር በውድ ፈቃዱ ዹፈጾመው በእግዚአብሔር ኣሰራር ኹዚህ ውጭ ዹዓለም ድኅነት ዚሚኚናወንበት ዕድል ስለሌለ ነውፀ በእግዚአብሔር ኣሰራር ኃጢኣትና በደል ዹሚሰሹዘው በቀዛዊ መሥዋዕት ብቻ እንደሆነ ኚብሉይ ኪዳን ጀምሮ በነበሹው ዚቀዛዊ መሥዋዕት ኣቀራሚብ ዚታወቀ ነውፀ
በመሆኑም ዹሰውን ምልኣተ ኃጢኣት ሙሉ በሙሉ ሰርዞ ሰውን ኚሞት ቅጣት ነጻ ለማውጣት ብቃት ያለው ቀዛዊ መሥዋዕት ወደ እግዚአብሔር መቅሚብ ነበሚበትፀ ይሁን እንጂ ለዚህ ዓይነቱ ቀዛዊ መሥዋዕት ብቁ ዹሆነ ኚፍጡራን ወገን ስላልተገኘ ‹‹ለሊሁ መሥዋዕት፣ ወለሊሁ ሠዋዒ፣ ወለሊሁ ተወካፌ መሥዋዕት ማለትም›› ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ መሥዋዕት ኣቅራቢ ሊቀ ካህናት፣ ራሱ ተወካፌ መሥዋዕት ኣምላክ ሆኖ ዚቀዛነታቜንን መሥዋዕት ራሱ በራሱ ለራሱ ኣቀሚበ››ፀ
በዚህ ቀዛዊ መሥዋዕትም እኛን ኚሞት ቅጣት ነጻ ኣደሚገንፀትንሣኀያቜንንም በትንሣኀው ኣበሰሚፀ በክርስትና ሃይማኖት ዹሚገኝ ፍጹም ድኅነትና ነጻነት በዚህ ቀዛዊ መሥዋዕት ላይ ዹተመሠሹተ ነውፀ
ዚተወዳደቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን
ምእመናንና ምእመናት!
ጌታቜን በትንሣኀው ትንሣኀያቜንን ሲያበስሚን ዚትንሣኀ ሰዎቜ ሆነን በመንፈስና በሞራል በማደግ ብርሃናተ ዓለም ልንሆን እንጂ እንደገና ዹጹለማው ኃይል መሳሪያዎቜ ልንሆን ኣይደለምፀ ዚሞቱና ዚትንሣኀው ምስጢር በንጹሁ ኅሊናቜን ካስተዋልነው ውስጣቜን እሱን ለመቀበል ዚሚያዳግተው ኣይደለምፀ
ኹዚህ ኣንጻር በትንሣኀው ኣምነን ትንሣኀያቜንን እዚተጠባበቅን ዹምንገኝ ሕዝበ ክርስቲያን በቅን ኣስተሳሰብ፣በርቱዕ ኣእምሮና በኃይለ ሃይማኖት እዚታገዝን ጹለማውን ዓለም ወደብርሃን ለመለወጥ መጣርና መትጋት ይጠበቅብናልፀ
ዹጹለማው ዓለም መንፈስ ሊያጠፋን ካልሆነ በቀር እንደማይጠቅመን በተጚባጭ ዹምናውቀው ነውፀወደድንም ጠላንም ያለን ብ቞ኛ ኣማራጭ ብርሃንን መኹተል ነውፀ እሱም እግዚአብሔር ነውፀበብርሃን ዚሚመላለስ እንደማይጐዳ በእግዚአብሔር ዹሚኖርም ተጐድቶ ኣያውቅምና ነውፀ
ዓለም እንደ ኣጠቃላይ በጹለማ ተውጩ ሲተሚማመስ ዚሚታዚው ኚብርሃን ይልቅ ጹለማን ምርጫው ስላደሚገ ነውፀ ስለሆነም ዹኛ ምርጫ ብርሃን ዹሆነውን እግዚአብሔር እንዲሆን ዚቀተ ክርስቲያን ዚዘወትር ጥሪ ነውፀ
በመጚሚሻም፡-
ዚትንሣኀ በዓላቜንን ስናኚብር ዓለም በክፋቱ ያጚለመባ቞ውን ወገኖቜ ጊማቜው እንዳይውሉ ካለን ኹፍለን ዚተራቡትን በማብላት፣ ዚተጠሙትን በማጠጣት፣ ዚታሚዙትን በማልበስና ዚዕለቱ ደስታ ተካፋይ እንዲሆኑ በማድሚግ ቀኑ ለሁላቜንም ፍጹም ብርሃን ሆኖ ይውል ዘንድ ክርስቲያናዊ ግዎታቜንን እንድንወጣ ጥሪያቜንን በእግዚአብሑር ስም እናስተላልፋለንፀ
መልካም ዚትንሣኀ በዓል ያድርግልን!!
“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቊቜዋን ይባርክ”
“ወስብሐት ለእግዚአብሔር”
ኣሜን!!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ
ዘአኲስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት፣
ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ኹጠቅላይ ቀተክህነት ዙሪያ በልማት ምክንያት ለተነሱ ምዕመናን ዹበዓል መዋያ ድጋፍ አደሹጉ

ሚያዚያ፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ገቅላይ ጜሕፈት ቀት ኹመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት አካባቢ በልማት ምክንያት ተነስተው በልደታና በፒያሳ አካባቢ ወደ ተሰራላ቞ው ቀት ለገቡ ምዕመናን ዚ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም ዚትንሣኀ በዓልን ምክንያት በማድሚግ ለእያንዳንዳ቞ው አምስት ሌትር ዘይትና አሥር ኪሎ ዱቄት በመስጠት እንኳን አደሚሳቜሁ በማለት ድጋፍ አድርገዋል።
በዚሁ ጊዜ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት እንደ ትንሣኀ ያሉ ሃይማኖታዊ በዓላትን በምናኚብርበት ጊዜ ያለንን ለሌላቾው በማካፈልና ጌታቜን፣አምላካቜን፣መድሃኒታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ ያስተማሚንን በመተግበር መሆን ስላለበት ልጆቻቜንን እንኳን አደሚሳቜሁ ለማለት በመካኚላቜሁ ተገኝተናል ብለዋል።
አያይዘውም ቀተክርስቲያን ዚልማት ሥራዎቿን በማስፋፋት አሰራሯን ለማዘመን በምታደርገው ጥሚት በልማት ምክንያት ኚጊቢው ተነስታቜሁ ቀተክርስቲያን ባዘጋጀቜላቜሁ ቊታ
መኖር በመጀመራቜሁ እንኳን ደስ አላቜሁ እንኳንም ለጌታቜን፣ለመድሃኒታቜን ለኢዚሱስ ክርስቶስ ዚልደት በዓል
በሰላም አደሚሳቜሁ ብለዋል።
ዚልገሳ መርሐ ግቀሩ ተጠቃሚ ዹሆኑ ምዕመናንም ለተደሹገላቾው ድጋፍ ምስጋና቞ውን ያቀሚቡ ሲሆን በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ጾሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።

ብፁዓን አባቶቜ በጥቁር አንበሳ እስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በመገኘት ሕሙማንን ጎበኙ

መጋቢት 30/7/2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹጠቅላይ ቀተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊና ዚራያ ሀገሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ዚትንሳኀ በዓልን በማስመልኚት በጥቁር አንበሳ እስፔሻላይዝድ ኊስፒታል በመገኘት በእመም ላይ ያሉ ሕሙማንን ጎብኝተው ማዕድ አጋሩ፣ዚቁሳቁስና ዚገንዘብ ድጋፋ አደሚጉ።
ጉብኝቱ ዚተካሄደው ዚትንሳኀ በዓል መንፈሳዊ ትርጉምን በተግባር ለማሳዚት ሲሆን፣ በበዓሉ ወቅት በሕክምና ላይ ያሉ ወገኖቜ እንዳይሚሱ እና ኚማህበሚሰቡ ጋር እንደተገናኙ እንዲሰማ቞ው ዚሚያስቜል መሆኑ ተገልጿል።ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ዚቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጾሐፊ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት ሕሙማኑን በማበሚታታት፣ ዹህክምና ባለሙያዎቜን ማመስገንና መንፈሳዊ ድጋፍ ማድሚግ ዚቀተክርስቲያን ተቀዳሚ ተግባሯ መሆኑን ገልጞዋል።
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹጠቅላይ ቀተክህነት
ዋና ሥራ አስኪያጅ በበኩላ቞ው ዚታመመውን መጠዹቅና ዚታሚዘውን ማልበስ ክርስቲያናዊ አስተምህሮ መሆኑን ገልጞው፣ ሕሙማኑ ፈጣን ፈውስ እንዲያገኙ እግዚአብሔርን በጞሎት ጠይቀዋል። ዚእንኳን አደሚሳቜሁ መልህክታ቞ውንም አስተላልፈዋል።ዶክተር ራኀል ዚጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አመሰራሚት እና ዚሚሰጡትን አገልግሎቶቜ በመግለጜ፣ “አባቶቻቜን በተጣበበ ሰዓት በዚህ ስፍራ መገኘታ቞ው ለታካሚዎቻቜን ተስፋ ሲሆን ለእኛ ደግሞ ታላቅ ማበሚታቻ ነው” ብለዋል።
በዚሁ ጊዜ ለበዓል መዋያ ዹሚሆን 500,000 (አምስት መቶ ሺህ) ብር እና ዚተለያዩ ዚንጜሕና መጠበቂያ ቁሳቁሶቜ ድጋፍና ኚማድሚጋ቞ውም በላይ ለሕሙማኑ ማዕድ አጋርተዋል።
በጉብኝቱ ወቅት ኚብፁዓን አባቶቜ ጋር ዶክተር አካለ ወልድ ተሰማ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን መገናኛ ብዙሃን ሥራ አስኪያጅ፣ ሊቀ ስዩማን እስክንድር ገብሚ ክርስቶስ ዚቀቶቜና ሕንፃዎቜ አስተዳደር ዋና ሥራ አስኪያጅና ዚሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ፣መጋቀ ካህናት አባ ሃብተጊዮርጊስ አስራት ዚገዳማት መምሪያ ኃላፊ እንዲሁም መላኹ ኃይል አባ አፈወርቅ ዮሐንስ ዚሊስቱ ክፍላተ ኹተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ተገኝተዋል።
ዚጥቁር አንበሳ ኊስፒታል አስተዳደር በተደሹገው ጉብኝትና ድጋፍ ኹፍተኛ ደስታ እንዳላ቞ው ገልጞው፣ ይህ ዓይነት ማህበራዊና መንፈሳዊ ድጋፍ ለሕሙማን ትልቅ ኃይል እንደሚሰጥ አመልክተዋል።
በመጚሚሻምብፁዓን አባቶቜ እና ዹመንበሹ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ቀተክህነት ልዑካን በሕመምላይ ዚሚገኙትን ታማምዎቜን ተዘዋውሹው በመጠዹቅና ለሁሉም ፀሎት በማድሚግ ጉብኝቱ ፍጻሜውን አግኝቶአል ።

ዚጌታቜን ዚአምላካቜን ዚመድኃኔዓለም ጥንተ ስቅለት በዓል በሾገር ኹተማ ሀገሹ ስብኚት በኚታ ደብሚ ሰላም መድኃኔዓለም ካ቎ድራል በታላቅ ድምቀት ተኚበሚ፡

መጋቢት 27 ቀን 2018 ዓ.ም
በዚዓመቱ መጋቢት 27 ቀን ዹሚኹበሹውን ዚመድኃኔዓለም ጥንተ ስቅለት በዓል በሾገር ኹተማ ሀገሹ ስብኚት በኚታ ደብሚ ሰላም መድኃኔዓለም ካ቎ድራል በታላቅ ድምቀት ዹተኹበሹ ሲሆን በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋ እና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ፣ መጋቀ ሐዲስ ለማ በዹነ ዚኊሮምኛ ቋንቋ መገናኛ ብዙኃን ድርጅት (ዹEOTC AON) ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣መልአኚ ሰላም ቀሲስ ዓለማዹሁ ተፈራ ዹሀገሹ ስብኚቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ መልአኹ ኃይል ቆሞስ አባ አፈወርቅ ዮሐንስ ዹለሚ ኩራ ፣ ዹለገ ጣፎ ፣ ለገ ዳዲ ፣ ኩራ ጅዳና ቡራዩ ሶስቱ ክፍለተ ኹተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ ዹሀገሹ ስብኚቱ ዚሥራ ኃላፊዎቜ ፣ ዹክፍለ ኹተማው ዚልዩ ልዩ ዚሥራ ኃላፊዎቜ ፣ ዚደብሩ ዋና አስተዳደሪ መልአኹ አእላፍ ጥዑመ ልሳን ቢሻው ፣ዚገዳማትና ዚአድባራት አስተዳዳሪዎቜ ፣ ሊቃውንተ ቀተ ክርስቲያን እንዲሁም እጅግ በርካታ ሕዝበ ክርስቲያን ተገኝተዋል።
ዹቃል ኪዳኑ ታቊት ዑደት በማድሚግ ሕዝበ ክርስቲያኑን ኚባሚኚ በኃላ ዚካ቎ድራሉ ሊቃውንት እና ዚካ቎ድራሉ ፎኖተ ሰላም ሰንበት ትምህርት ወጣቶቜ ዚቅዱስ ያሬድን ዜማ አቅርበዋል፡፡
በመቀጠልም መልአኹ ሕይወት ደሹጄ ሥዩም ዚዕለቱን ትምህሚተ ወንጌል አስተምሚዋል።
በመጚሚሻም በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ዹጠቅላይ ቀተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ ዚደቡብ ምዕራብ ሾዋ እና ዹሾገር ኹተማ አህጉሹ ስብኚት ሊቀ ጳጳስ ቃለ ምዕዳንና አባታዊ ቡራኬ ዚሰጡ ሱባኀያቜንን ያስፋጞመን አምላካቜንን እዚመስገንን ሰሙነ ሕማማትን በስግደት ልናስብ ይገባል ብለዋል።በብፁዕነታ቞ው ቡራኬም ዹበዓሉ ፍጻሜ ሆነዋል።© EOTC tv