የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ እንኳን አደረሰዎ መርሐግብር በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሐፈት ቤት በደማቅ መንፈሳዊ ስነስርዓት ተካሄደ

ሚያዚያ ፭ ቀን ፪፻ ፲ወ፰ዓ.ም.
ኢኦተቤክ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
አዲስአበባ , ኢትዮጵያ
በየዓመቱ በትንሣኤ ማግስት ፣ በአዲስ ዓመት ማግስትና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ማግስት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ጀምሮ እስከ አዲስአበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት አገልጋዮች በመሰባሰብ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የእንኳን አደረሰዎ መርሐግብር ይካሄዳል።
በዚሁ መሠረት የዘንድሮ የ2018ዓ.ም የትንሣኤ በዓል ምክንያት በማድረግ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የምስካየ ኅዙናን መድኀኔዓለም ገዳም የበላይ ኀላፊ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ የራያ ስድስቱ ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅርሳቅርስ ወመዘክርና ቤተመጻሕፍት ፣ የማሕበራት ምዝገባ ፣ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያዎች የበላይ ኀላፊ፣
ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስአበባ፣ የሐድያና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዓን አበው ለቃነ ጳጳሳት፣
ንቡረእድ ኤልያስ አብርሃ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት በመንፈሳዊ ዘርፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ
ረ/ፕ ግርማ ባቱ (ቀሲስ) የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ፣
መ/ም አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ የአዲስአበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክልነት ጽሕፈት ቤት ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎችና ሠራተኞች ፣የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎችና ሠራተኞች፣የአዲስአበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ፣የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ፣ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት መርሐግብሩ ተካሂዷል።
መርሐግብሩ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃና ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት መሪነት የደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን አገልጋይ ካህናት ጸሎተ ወንጌል አድራሽነት በጸሎት የተከፈተ ሲሆን የበርካታ ሊቃውንት መፍለቂያ በሆነውና በአንጋፋው በሰዋስዋወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርትና መምህራን አማካኝነት ያሬዳዊ ዜማ መነሻነት የእለቱ ተከታታይ መርሐግብራት መቅረብ ጀምረዋል።
ከሊቃውንቱ ያሬዳዊ ዜማ በመቀጠል የአዲስአበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት ተወካዮች የትንሣኤውን ምስጢር በሚያብራራ መቅድም በመነሣት በልጅነት መታዘዝ ለቅዱስነታቸው የእንኳን አደረሰዎ መልእክት በጽሑፍ አቅርበው በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማዕከላውያን የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና የጋሞኛ ዘማርያን በያሬዳዊ ዜማ ቅዱስነታቸውን እንኳን አደረሰዎ ብለዋል።
በመቀጠልም ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እለቱን የሚመለከት ቅኔ በማቅረብ መርሐግብሩ ቀጥሏል። ከሊቃውንቱ ቅኔ በመቀጠል ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ ለቅዱስነታቸው የእንኳን አደረሰዎ መልእክት ሲያቀርቡ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው በሚል ሐይለ ቃል በመነሳት የአሮጌው ዘመን ልዩ መገለጫ የሆነውን ስንፍና በሥራ ጥላቻን በፍቅር በመተካትና ዛሬን የሰጡንን የአባቶቻችንን ውለታ ባለመርሳት የቅድስት ቤተክርስቲያንን ይዞታዋን ማስከበር፣ የተጀመሩ ሕንጻዎችን ማስፈፀም፣ ቅጥር ጊቢውን ውብና ጽዱ ለማድረግ የቅዱስነታቸው ጸሎትና አባታዊ መመሪያ ዋጋው ላቅ ያለ መሆኑን ገልጸው ቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ እንዲሰጡ ጋብዘዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ በዚህ መልኩ በተዘጋጀው የእንኳን አደረሰዎ መርሐግብር ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው ጌታችን እና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር በሥጋ ማርያም በመገለጥ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሥጋውን የቅረሰውና ደሙን ያፈሰሰው ይህንን ዓለም ለማዳንና ለማደስ ነው።
እግዚአብሔር ይህንን ዓለም አመቻችቶ ክቡር ለሆነው ለሰው ልጅ ሲሰጥ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ያለውን የጥል ግድግዳ በማፍረስና የዲያብሎስን ስልጣን በመሻር ነበር። ነገር ግን የተከፈለልንን የክርስቶስ ዋጋ የረሳ በሚመስል መልኩ እርስ በእርሳችን እየተበላላን እንገኛለን በማለት ማንኛውም አማኝ በተከፈለለት ልክ እንዲኖር አባታዊ መመሪያ ሰጥተው በቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ በ2018 ዓ.ም የትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሰዎ መርሐ ግብር ላይ ያስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ይነበባል

“ወይእዜሰ በክርስቶስ ተሐድሰ ኵሉ ወኃለፈ ዘትካት ወናሁ ኮነ ሐዲስ ኵሉ … ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፏል እነሆ ሁሉም አዲስ ሆኗል” (2.ቆሮ 5÷17)
❖ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤
❖ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤
❖ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ፣ የሐዲያና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
❖ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት
ክቡር ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ በመንበረ ፓትርያርክ ጠ/ቤ/ክ የመንፈሳዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ፤
ክቡር ረዳት ፕሮፌሰር ግርማ ባቱ በመንበረ ፓትርያርክ ጠ/ቤ/ክ የማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ፤
ክቡራን የመንበረ ፓትርያርክ ጠ/ቤ/ክ የየመምሪያውና የየድርጅቱ ኃላፊዎች፤
ክቡራን የመንበረ ፓትርያርክ ጠ/ቤ/ክ ሠራተኞች፤
ክቡራንና ክቡራት በዚህ መንፈሳዊ መርሐ ግብር የተገኛችሁ በሙሉ
በአምላካዊ ሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ፣ ብርሃንን ተጎናጽፎ፣ ከሙታን የተነሣው፣ ሕያው እግዚአብሔር ቅዱስነታቸውን በሕይወት ጠብቆ አሮጌው ነገር አልፎ የአዲስ ሕይወት ኑሮ ለተጀመረበት በዓለ ትንሣኤ እንኳን አደረሰዎ በማለት ለቅዱስነትዎ ያለኝን ክብር በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሠራተኞች ስም ስገልጽ ምሉዕና ፍጹም በሆነ ደስታ ነው። (1.ቆሮ 15÷54)
የአዲስ ፍጥረት ምሥጢር ሰው ትንሣኤ ልቡና አግኝቶ በኢየሱስ ክርስቶስ ሲያምን የሚኖረውን አዲስ ሕይወትና ከአሮጌው ማንነቱ መለየቱን የሚያረጋግጥ ጥልቅ የሆነ ትርጉም ያለው በመሆኑ ትንሣኤውን እንደ ኃላፊ ኩነት ብቻ አስበን የምናልፈው አይደለም።
የክፋት ሁሉ ምንጭ የሆነው ዲያብሎስ በመሻሩ የሰው ልጅ ውጫዊ የሕይወት ለውጥን ብቻ ሳይሆን ፍጹም የሆነ ውስጣዊ ለውጥን ስላገኘ ትንሣኤው በዕለት ተዕለት የክርስትና ሕይወት ውስጥ ሁል ጊዜ የሚገለጥ አሁናዊ ጉዳይ ነው።
ከሞት በኋላ በሚቀጥል ሕይወት፣ አዲስ ፍጥረት ሆነን ለነፍሳችን ድኅነት ያገኘንበት የክርስቶስ ትንሣኤ በድካም ጊዜ ብርታት፣ በፈተና ጊዜ ሕያው ተስፋ፣ በጭንቀት ጊዜ ሰላም ከመሆኑም በላይ ክርስቶስ እኛን የወደደበት የታላቅ ፍቅሩ መገለጫ ነው።
በመሆኑም ክርስትና ሃይማኖታችን እርሱን መሠረት አድርጎ የቆመበት ትንሣኤው ታሪክ ብቻ ሳይሆን ዛሬም በሕይወታችን ላይ የሚሠራ ኃይል፣ የጨለማው መጨረሻ፣ ከጥፋት መንገድ የወጣንበት የንጋቱ መጀመሪያ መሆኑ አያጠያይቅም።
የመልእክታችን መነሻ የሆነው ሐዋርያዊ ቃልም «አሮጌው ነገር አልፎ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆኗል» የሚል ነው። የክርስቶስ ትንሣኤና የምሥራቹ ዜና እስኪሰማ ድረስ የሰው ልጅ ያሳለፈው የመከራ ዘመን የሚረሳ አይደለምና አዲስ የሆነው ነገር ከአሮጌው ጋር መነጻጸሩ የማይቀር ነው።
በክርስቶስ ቤዛነት የተደረገልን ድንቅ ነገር ለመረዳትም ከአለፈው መነሣት የግድ ነው። የሐሳብ ቅንነት የጠፋበት፣ የመንፈስ ድካም የነበረበት ያ! አሮጌው ነገር በክርስቶስ አልፎ ዛሬ አዲስ የትንሣኤ ሕይወት አግኝተናል። በዚህም ሰው ሆኖ ያዳነን፣ በትንሣኤው አዲስ ሕይወት የሰጠንን አምላክ እናመሰግናለን።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን፤
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤
ክቡራንና ክቡራት በዚህ የእንኳን አደረሳችሁ መርሐ ግብር የተገኛችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤
ክርስቶስ ላንቀላፉት ሁሉ በኩራት ሆኖ በመነሣቱ በሰው ልጅ ሕይወት የነበረው ሥቃይና መከራ አልፎ፤ ሁሉም ነገር አዲስ በሆነበት የምሕረት ዘመን፤ የአሮጌው ማንነት መገለጫ ስንፍና፣ በሥራ ሲሸነፍ፣ ጥላቻ በፍቅርና በልማት ሊተካ አልቻለም ባይነት፣ አይቻልም ማለት በትንሣኤ ሕይወት ውስጥ ቦታ የላቸውም። (1.ቆሮ 15÷20)
በዚህ የሕይወት ጉዞ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሁለንተናዊ ተልዕኮና ራስን የመቻል ሁኔታ የተሟላ እንዲሆን የደከሙ፤ እነርሱ እየተራቡና እየተጠሙ የእኛ የልጆቻቸው ኑሮ እንዲሻሻል በመታመን አክብረው የሠሩ ቀደምት አባቶቻችንን የሚያስታውሱ በርካታ የልማት ሥራዎች በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በቅዱስነትዎ ጸሎትና አመራር ሰጪነት እየተከናወኑ ይገኛሉ።
ቀደም ሲል ተጀምረው ያልተጠናቀቁ የሕንፃ ግንባታዎችና በአዲስ መልክ የሚሠሩ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች በታቀደላቸው ጊዜ ተጠናቅቀው መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲሰጡ ለማድረግ ተግተን በመሥራት ላይ እንገኛለን።
ከዚህም ጋር የተቋማት ማንነትና አሠራር የሚለካው በሚገለገሉባቸው ጽ/ቤቶች አያያዝና በሥራ አፈጻጸማቸው ስለሆነ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላላ ቤተ ክህነት ይዞታን በማስከበር ጽዱና ውብ ሥፍራ የማድረግ ሥራው በመገባደድ ላይ ይገኛል።
ያለ አግባብ የተከማቹ ንብረቶችም ተገቢውን መፍትሔ እንዲያገኙ፤ የግቢው ጽዳትና ውበት እንዲጠበቅ የማድረግ ሥራ ብዙ ጊዜና ጉልበት የሚጠይቅ የነበረ ቢሆንም በሁሉም የቤተ ክህነታችን የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች ተሳትፎ በአግባቡ ተከናውኗል።
በመሆኑም ሥልጣነ ሞት የተሻረበትን የክርስቶስ ትንሣኤ ዛሬ በዚህ መልኩ ተሰብስበን በቅዱስነትዎ በራሄ የምናከብረው ከፍተኛ በሆነ የሥራ መነቃቃት ነው።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን፤
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤
ክቡራንና ክቡራት፤
ትንሣኤ የሥጋ መነሣት ብቻ አይደለም በእግዚአብሔር ቤት ሊሠራ የሚገባውን ሥራ በመሥራት ለኃጢአት ሞቶ፣ በአዲስ ሕይወት መኖር ማለት ነው። ትንሣኤ ልዩነትን ይሻገራል፣ በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባር የሚታይ አንድነትንም ይፈጥራል። ከኃጢአት መራቅን፣ በፍቅር መኖርንና በተስፋ መጓዝን ያጎናጽፋል። ሰው ብቻውን ሲሠራ ውጤቱ ውስን ነው፤ በጋራ መሥራት ግን እጅግ ከፍተኛ ዋጋ ያለው በትንሣኤው የተገኘ የሕይወት መርሕ ነው።
ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬ ያለችበት ደረጃ ላይ እንዲሁ በቀላሉ አልደረሰችም። በትንሣኤው የተገኘው አንድነት የበጎ ሥራ ሁሉ መሠረት መሆኑን በተረዱት፣ ለክብረ ስማቸው ይህን መታሰቢያ ትተውልን ባለፉት አባቶቻችንና እናቶቻችን ከፍተኛ ጥረት ነው። ዛሬ እኛ እየገነባን ያለነው እነርሱ ባኖሩት መሠረት ላይ ነው።
በመሆኑም ጊዜው የሥራ ጊዜ ነውና አሁን ያለነው የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምዕመናን የእምነታችንን ታሪክ ከሥርዓተ አምልኮው ጋር የመጠበቅና የማስጠበቅ፣ ለመንፈሳዊና ማኅበራዊ ዕድገት ልማትን አስፋፍቶ የመሥራት ኃላፊነት አለብን።
ስለዚህ በአዲስ መንፈስና በአዲስ ሕይወት እየተመላለስን የትንሣኤውን ብርሃን በማውጅ ለሀገር ሰላም፣ ለቤተ ክርስቲያን አንድነትና ለሐዋርያዊ ተልዕኮ መስፋፋት ሁሉም የቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎቶች ለጥንታዊ ታሪካችን በሚመጥን መልኩ ድርሻችንን ልንወጣ ይገባል።
በታላቁ ዐቢይ ጾም ለሃምሳ አምስት ቀናት ያለ ዕረፍት ስታገለግሉ ከርማችሁ ደከመን ሳትሉ በተቀደሰው ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት መሠረት ቅዱስ አባታችንን እንኳን አደረሰዎት ለማለት የሁላችን ማዕከል ወደ ሆነው መንበረ ፓትርያርክ መጥታችሁ የበረከቱ ተካፋዮች የሆናችሁትን ሁሉ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ስም ከልብ እናመሰግናችኋለን።
በመጨረሻም ቅዱስ አባታችን በልጁ ሞት ይቅር ያለን አምላካችን እግዚአብሔር በጸሎት፣ በሐሳብ ካልተለየዎትና ሁልጊዜም ከማይለየዎት ሕዝበ ክርስቲያን ጋር በሰላም፣ በጤና ጠብቆ እንኳን ለ2018 ዓ/ም በዓለ ትንሣኤ በድጋሚ አደረሰዎ እያልኩ መልእክቴን በዚህ አጠቃልላለሁ።
የቅዱስነትዎ ቡራኬ አይለየን
አባ ሳዊሮስ
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላላ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤
የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤
የምስካዬ ኅዙናን ገዳም የበላይ ኃላፊ፤
ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ/ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንና ዳሽን ባንክ አከሰስዮን ማኅበር ሦስት መቶ ለሚሆኑ ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ምዕመናን የበዓል መዋያ ድጋፍ አደረጉ

ሚያዚያ፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ገቅላይ ጽሕፈት ቤት ከዳሽን ባንክ አክስዮን ማኅበር ጋር በመተባበር ሦስት መቶ ለሚሆኑ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ ምዕመናን የ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም የትንሣኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ ለእያንዳንዳቸው አምስት ሌትር ዘይትና አሥር ኪሎ ዱቄት በዛሬው ዕለት በጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ቅጽር ጊቢ በተከናወነ የልገሳ መርሐ ግብር ድጋፍ አድርገዋል።
በዚሁ ጊዜ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት እንደ ትንሣኤ ያሉ ሃይማኖታዊ በዓላትን በምናከብርበት ጊዜ ያለንን ለሌላቸው በማካፈልና ጌታችን፣አምላካችን፣መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረንን በመተግበር መሆን ስላለበት ዳሽን ባንክ አክሲዮን ማኅበር ይህን መርሐ ግብር እንዲዘጋጅ በማድረጉ ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርባለን በማለት በዓሉ የደስታና የበረከት በዓል እንዲሆን መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበዓል ወቅት አቅመ ደካሞችን ማገዝ ተገቢ መሆኑን ጉግጸው ዳሽን ባንክን አመሰግነዋለሁ ግነዋል።
የዳሽን ባንክ አክስዩን ማኅበር የማርኬቲንግና ብራንዲንግ ዳይሬክተር አቶ እንዳለ ገብረስላሴ ባስተላለፉት መልዕክት
ባንኩ በዚህ ዓይነት ማኅበራዊ አገልግሎት ዙሪያ በመሰማራቱ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማው ገልጸዋል።የልገሳ መርሐ ግቤሩ ተጠቃሚ የሆኑ ምዕመናንም ለተደረገላቸው ድጋፍ ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤን በማስመልከት የእንኳን አደረሳችሁ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ

የቅዱስነታቸው አባታዊ መልዕክት እንደሚከተለው ይነበባል።
ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ ኣቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት፤
በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ ኣምላክ ኣሜን፡-
በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
በሕመም ምክንያት በየፀበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣
እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፣
በቤዛዊ መሥዋዕትነቱ ከሞተ ኃጢኣት ታድጎ የትንሣኤ ሙታንን በር የከፈተልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም ኣደረሰን ኣደረሳችሁ!
‹‹ወኣነ እሜጡ ነፍስየ ቤዛ ኣባግዕየ ከመ ካዕበ ኣንሥኣ፤
ዳግመኛ ኣነሣት ዘንድ ነፍሴን የበጎቼ ቤዛ ኣድርጌ እሰጣለሁ (ዮሓ 10÷17)
ጌታችን ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰብኣዊ ክዋኔው ሰው ቢሆንም በመለኮታዊ ክዋኔው የኣብና የመንፈስ ቅዱስ ቃል ወይም ወልደ እግዚአብሔር ነው፤
በመሆኑም በሰብኣዊ ክዋኔው መዋች ሲሆን በመለኮታዊ ክዋኔው ተነሽና ኣንሺ ነው፤ ከዚህ ኣንጻር ሥግው ቃል ሁለቱንም ተግባራት በኣንድ ኣካልና ክዋኔ የመፈጸም ሥልጣን ኣለው፤ ይህም በመሆኑ ራሴን የማኖርና የማንሣት ሥልጣን ኣለኝ በማለት እውነታውንና ምንነቱን ኣሳየ፤
ጌታችን ይህንን ኣስመልክቶ ከመሞቱና ከመነሣቱ በፊት ለቅዱሳን ሓዋርያት በተደጋጋሚ ኣስረድቶኣል፤ ስለሆነም የጌታችን ሞትና ትንሣኤ ድንገተኛና የግድ ሳይሆን ታውቆ ያደረና የውድ እንደሆነ ከዚህ እውነታ እንረዳለን፤
ጌታችን ይህንን ተግባር በውድ ፈቃዱ የፈጸመው በእግዚአብሔር ኣሰራር ከዚህ ውጭ የዓለም ድኅነት የሚከናወንበት ዕድል ስለሌለ ነው፤ በእግዚአብሔር ኣሰራር ኃጢኣትና በደል የሚሰረዘው በቤዛዊ መሥዋዕት ብቻ እንደሆነ ከብሉይ ኪዳን ጀምሮ በነበረው የቤዛዊ መሥዋዕት ኣቀራረብ የታወቀ ነው፤
በመሆኑም የሰውን ምልኣተ ኃጢኣት ሙሉ በሙሉ ሰርዞ ሰውን ከሞት ቅጣት ነጻ ለማውጣት ብቃት ያለው ቤዛዊ መሥዋዕት ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ነበረበት፤ ይሁን እንጂ ለዚህ ዓይነቱ ቤዛዊ መሥዋዕት ብቁ የሆነ ከፍጡራን ወገን ስላልተገኘ ‹‹ለሊሁ መሥዋዕት፣ ወለሊሁ ሠዋዒ፣ ወለሊሁ ተወካፌ መሥዋዕት ማለትም›› ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ መሥዋዕት ኣቅራቢ ሊቀ ካህናት፣ ራሱ ተወካፌ መሥዋዕት ኣምላክ ሆኖ የቤዛነታችንን መሥዋዕት ራሱ በራሱ ለራሱ ኣቀረበ››፤
በዚህ ቤዛዊ መሥዋዕትም እኛን ከሞት ቅጣት ነጻ ኣደረገን፤ትንሣኤያችንንም በትንሣኤው ኣበሰረ፤ በክርስትና ሃይማኖት የሚገኝ ፍጹም ድኅነትና ነጻነት በዚህ ቤዛዊ መሥዋዕት ላይ የተመሠረተ ነው፤
የተወዳደችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን
ምእመናንና ምእመናት!
ጌታችን በትንሣኤው ትንሣኤያችንን ሲያበስረን የትንሣኤ ሰዎች ሆነን በመንፈስና በሞራል በማደግ ብርሃናተ ዓለም ልንሆን እንጂ እንደገና የጨለማው ኃይል መሳሪያዎች ልንሆን ኣይደለም፤ የሞቱና የትንሣኤው ምስጢር በንጹሁ ኅሊናችን ካስተዋልነው ውስጣችን እሱን ለመቀበል የሚያዳግተው ኣይደለም፤
ከዚህ ኣንጻር በትንሣኤው ኣምነን ትንሣኤያችንን እየተጠባበቅን የምንገኝ ሕዝበ ክርስቲያን በቅን ኣስተሳሰብ፣በርቱዕ ኣእምሮና በኃይለ ሃይማኖት እየታገዝን ጨለማውን ዓለም ወደብርሃን ለመለወጥ መጣርና መትጋት ይጠበቅብናል፤
የጨለማው ዓለም መንፈስ ሊያጠፋን ካልሆነ በቀር እንደማይጠቅመን በተጨባጭ የምናውቀው ነው፤ወደድንም ጠላንም ያለን ብቸኛ ኣማራጭ ብርሃንን መከተል ነው፤ እሱም እግዚአብሔር ነው፤በብርሃን የሚመላለስ እንደማይጐዳ በእግዚአብሔር የሚኖርም ተጐድቶ ኣያውቅምና ነው፤
ዓለም እንደ ኣጠቃላይ በጨለማ ተውጦ ሲተረማመስ የሚታየው ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ምርጫው ስላደረገ ነው፤ ስለሆነም የኛ ምርጫ ብርሃን የሆነውን እግዚአብሔር እንዲሆን የቤተ ክርስቲያን የዘወትር ጥሪ ነው፤
በመጨረሻም፡-
የትንሣኤ በዓላችንን ስናከብር ዓለም በክፋቱ ያጨለመባቸውን ወገኖች ጦማችው እንዳይውሉ ካለን ከፍለን የተራቡትን በማብላት፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ የታረዙትን በማልበስና የዕለቱ ደስታ ተካፋይ እንዲሆኑ በማድረግ ቀኑ ለሁላችንም ፍጹም ብርሃን ሆኖ ይውል ዘንድ ክርስቲያናዊ ግዴታችንን እንድንወጣ ጥሪያችንን በእግዚአብሑር ስም እናስተላልፋለን፤
መልካም የትንሣኤ በዓል ያድርግልን!!
“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ”
“ወስብሐት ለእግዚአብሔር”
ኣሜን!!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ
ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣
ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ከጠቅላይ ቤተክህነት ዙሪያ በልማት ምክንያት ለተነሱ ምዕመናን የበዓል መዋያ ድጋፍ አደረጉ

ሚያዚያ፫ ቀን ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ገቅላይ ጽሕፈት ቤት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት አካባቢ በልማት ምክንያት ተነስተው በልደታና በፒያሳ አካባቢ ወደ ተሰራላቸው ቤት ለገቡ ምዕመናን የ፳፻ ፲ወ፰ ዓ.ም የትንሣኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ ለእያንዳንዳቸው አምስት ሌትር ዘይትና አሥር ኪሎ ዱቄት በመስጠት እንኳን አደረሳችሁ በማለት ድጋፍ አድርገዋል።
በዚሁ ጊዜ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት እንደ ትንሣኤ ያሉ ሃይማኖታዊ በዓላትን በምናከብርበት ጊዜ ያለንን ለሌላቸው በማካፈልና ጌታችን፣አምላካችን፣መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረንን በመተግበር መሆን ስላለበት ልጆቻችንን እንኳን አደረሳችሁ ለማለት በመካከላችሁ ተገኝተናል ብለዋል።
አያይዘውም ቤተክርስቲያን የልማት ሥራዎቿን በማስፋፋት አሰራሯን ለማዘመን በምታደርገው ጥረት በልማት ምክንያት ከጊቢው ተነስታችሁ ቤተክርስቲያን ባዘጋጀችላችሁ ቦታ
መኖር በመጀመራችሁ እንኳን ደስ አላችሁ እንኳንም ለጌታችን፣ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል
በሰላም አደረሳችሁ ብለዋል።
የልገሳ መርሐ ግቤሩ ተጠቃሚ የሆኑ ምዕመናንም ለተደረገላቸው ድጋፍ ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ጸሎተ ቡራኬ መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።

ብፁዓን አባቶች በጥቁር አንበሳ እስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በመገኘት ሕሙማንን ጎበኙ

መጋቢት 30/7/2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የትንሳኤ በዓልን በማስመልከት በጥቁር አንበሳ እስፔሻላይዝድ ኦስፒታል በመገኘት በእመም ላይ ያሉ ሕሙማንን ጎብኝተው ማዕድ አጋሩ፣የቁሳቁስና የገንዘብ ድጋፋ አደረጉ።
ጉብኝቱ የተካሄደው የትንሳኤ በዓል መንፈሳዊ ትርጉምን በተግባር ለማሳየት ሲሆን፣ በበዓሉ ወቅት በሕክምና ላይ ያሉ ወገኖች እንዳይረሱ እና ከማህበረሰቡ ጋር እንደተገናኙ እንዲሰማቸው የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል።ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት ሕሙማኑን በማበረታታት፣ የህክምና ባለሙያዎችን ማመስገንና መንፈሳዊ ድጋፍ ማድረግ የቤተክርስቲያን ተቀዳሚ ተግባሯ መሆኑን ገልጸዋል።
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት
ዋና ሥራ አስኪያጅ በበኩላቸው የታመመውን መጠየቅና የታረዘውን ማልበስ ክርስቲያናዊ አስተምህሮ መሆኑን ገልጸው፣ ሕሙማኑ ፈጣን ፈውስ እንዲያገኙ እግዚአብሔርን በጸሎት ጠይቀዋል። የእንኳን አደረሳችሁ መልህክታቸውንም አስተላልፈዋል።ዶክተር ራኤል የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አመሰራረት እና የሚሰጡትን አገልግሎቶች በመግለጽ፣ “አባቶቻችን በተጣበበ ሰዓት በዚህ ስፍራ መገኘታቸው ለታካሚዎቻችን ተስፋ ሲሆን ለእኛ ደግሞ ታላቅ ማበረታቻ ነው” ብለዋል።
በዚሁ ጊዜ ለበዓል መዋያ የሚሆን 500,000 (አምስት መቶ ሺህ) ብር እና የተለያዩ የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁሶች ድጋፍና ከማድረጋቸውም በላይ ለሕሙማኑ ማዕድ አጋርተዋል።
በጉብኝቱ ወቅት ከብፁዓን አባቶች ጋር ዶክተር አካለ ወልድ ተሰማ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙሃን ሥራ አስኪያጅ፣ ሊቀ ስዩማን እስክንድር ገብረ ክርስቶስ የቤቶችና ሕንፃዎች አስተዳደር ዋና ሥራ አስኪያጅና የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ፣መጋቤ ካህናት አባ ሃብተጊዮርጊስ አስራት የገዳማት መምሪያ ኃላፊ እንዲሁም መላከ ኃይል አባ አፈወርቅ ዮሐንስ የሦስቱ ክፍላተ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ተገኝተዋል።
የጥቁር አንበሳ ኦስፒታል አስተዳደር በተደረገው ጉብኝትና ድጋፍ ከፍተኛ ደስታ እንዳላቸው ገልጸው፣ ይህ ዓይነት ማህበራዊና መንፈሳዊ ድጋፍ ለሕሙማን ትልቅ ኃይል እንደሚሰጥ አመልክተዋል።
በመጨረሻምብፁዓን አባቶች እና የመንበረ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ልዑካን በሕመምላይ የሚገኙትን ታማምዎችን ተዘዋውረው በመጠየቅና ለሁሉም ፀሎት በማድረግ ጉብኝቱ ፍጻሜውን አግኝቶአል ።

የጌታችን የአምላካችን የመድኃኔዓለም ጥንተ ስቅለት በዓል በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት በከታ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ካቴድራል በታላቅ ድምቀት ተከበረ፡

መጋቢት 27 ቀን 2018 ዓ.ም
በየዓመቱ መጋቢት 27 ቀን የሚከበረውን የመድኃኔዓለም ጥንተ ስቅለት በዓል በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት በከታ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ካቴድራል በታላቅ ድምቀት የተከበረ ሲሆን በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ መጋቤ ሐዲስ ለማ በየነ የኦሮምኛ ቋንቋ መገናኛ ብዙኃን ድርጅት (የEOTC AON) ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣መልአከ ሰላም ቀሲስ ዓለማየሁ ተፈራ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ መልአከ ኃይል ቆሞስ አባ አፈወርቅ ዮሐንስ የለሚ ኩራ ፣ የለገ ጣፎ ፣ ለገ ዳዲ ፣ ኩራ ጅዳና ቡራዩ ሶስቱ ክፍለተ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የሀገረ ስብከቱ የሥራ ኃላፊዎች ፣ የክፍለ ከተማው የልዩ ልዩ የሥራ ኃላፊዎች ፣ የደብሩ ዋና አስተዳደሪ መልአከ አእላፍ ጥዑመ ልሳን ቢሻው ፣የገዳማትና የአድባራት አስተዳዳሪዎች ፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም እጅግ በርካታ ሕዝበ ክርስቲያን ተገኝተዋል።
የቃል ኪዳኑ ታቦት ዑደት በማድረግ ሕዝበ ክርስቲያኑን ከባረከ በኃላ የካቴድራሉ ሊቃውንት እና የካቴድራሉ ፎኖተ ሰላም ሰንበት ትምህርት ወጣቶች የቅዱስ ያሬድን ዜማ አቅርበዋል፡፡
በመቀጠልም መልአከ ሕይወት ደረጄ ሥዩም የዕለቱን ትምህረተ ወንጌል አስተምረዋል።
በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቃለ ምዕዳንና አባታዊ ቡራኬ የሰጡ ሱባኤያችንን ያስፋጸመን አምላካችንን እየመስገንን ሰሙነ ሕማማትን በስግደት ልናስብ ይገባል ብለዋል።በብፁዕነታቸው ቡራኬም የበዓሉ ፍጻሜ ሆነዋል።© EOTC tv