ትምህርተ ሃይማኖትን ዚያዘ መጜሐፍ በእንግሊዝኛ ቋንቋ በአሜሪካ ታትሞ ተመሚቀፀ በሀገር ውስጥ ለሚገኙ አንባብያን በቅርቡ በኢትዮጵያ እንደሚታተም ተገለጞ።

ዚካቲት 20 ቀን 2017 ዓ.ም

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

ዚካቲት 17 ቀን 2017 ዓ.ም
ወርኀ ጟሙን ዚተራበውን በመመገብ ዚተራቈተውን በማልበስ በኃላፊነት ያለን ዚኅብሚተሰብ መሪዎቜም ፍትሕንና እኩልነትን በማስፈንና ኚነገሮቜ ሁሉ በፊት ለሰላምና ለአንድነት ቅድሚያ በመስጠት ጟሙን እንድናሳልፍ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታቜንን እናስተላልፋለን::

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጹጌ ዘመንበሹ ተክለ ሃይማኖት በእስራኀል ምክትል ዹውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዚተመራ ልዑክን በጜ/ቀታ቞ው ተቀብለው አነጋገሩ፡፡

ዚካቲት 6 ቀን 2017 ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት ዚአክትስ ቞ርቜ ኩፍ ሱዲን ዚሥራ ኀላፊዎቜን   በጜ/ቀታ቞ው ተቀብለው አነጋገሩ።

ዚካቲት 1 ቀን 2017.ዓ.ም.

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ፍኖተ ጜድቅ ጠቅላላ ማኀበር ባካሔደው ዚነዳያን ምገባ መርሐ ግብር ላይ ተገኝተው ነዳያንን ኚመገቡ በኋላ ቃለ በሚኚትና ቃለ ቡራኬ ሰጡ።

ጥር 29 ቀን 2016 ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት ዹ2017 ዓ.ም ዚጟመ ነነዌ ዹሰላምና ዚጞሎት አዋጅ መግለጫ ሙሉ መልእክት ዹሚኹተለው ነው፡፡

ጥር 29 ቀን 2017ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
+ + +
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ኚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ ዹተላለፈ ዹምህላ ሱባዔ፡-
‹‹ቀድሱ ጟመ ወስብኩ ምህላ አስተጋብኡ ሕዝበ ሊቃውንተ ሕዝብፀ ጟምን ቀድሱ፣ጉባኀውንም አውጁፀሜማግሌዎቜንና በምድር ዚሚኖሩትን ሁሉ ወደ ኣምላካቜሁ ወደ እግዚአብሔር ቀት ሰብስቡፀ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ (ኢዩ ፩÷፲፬)

ሁላቜንም እንደምናውቀው ያለንበት ዓለም ዚመኚራ ዓለም ነው፣ መኚራው በኛ ስሕተትና ክፋት ዚመጣና እዚሆነ ያለ መሆኑም ይታወቃልፀ እኛ ዚምንፈጜመው ጥቃቅንና ትላልቅ ግብሚ ኃጢአት እግዚአብሔርን እንደሚያስቈጣ በቅዱስ መጜሐፍ ተሹጋግጩ ያደሚ ነውፀ ለዚህም ኹነነዌ ነዋሪ ሕዝብ ዹበለጠ ማስሚጃ ዚለንምፀ ዹነነዌ ኹተማ ነዋሪዎቜ በፈጞሙት ግብሚ ኃጢአት እግዚአብሔርን አስቈጥተዋልፀ ድርጊታ቞ው እግዚአብሔርን ዚሚያስቆጣ ቢሆንም እሱ ምሕሚቱን ማስቀደም ስለፈለገ በዮናስ በኩል አስጠንቅቆአ቞ዋልፀ ዹነነዌ ነዋሪዎቜም በዮናስ በኩል ዚደሚሳ቞ውን ዚንስሓ ጥሪ ወዲያውኑ ተቀብለው በምህላ፣ በጟም፣ በጞሎት ንስሓ ስለገቡ እግዚአብሔር ፍጹም ይቅርታ አድርጎላ቞ዋልፀ

• ዚተወደዳቜሁ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያን ልጆቻቜንና ወገኖቻቜን !

እኛ ሰዎቜ ዛሬም በዚሰዓቱ ብቻ ሳይሆን በዹደቂቃው እግዚአብሔርን ዚሚያስቆጣ አበሳ እንደምንፈጜም ማወቅ ኣለብን፣ አበሳውና ኃጢኣቱ ሲበዛ እግዚአብሔር እውነተኛ ዳኛ ነውና ወደ ዳኝነት ተግባሩ ይገባልፀይህ ደግሞ በሰብአ ትካት በሰዶምና በጎሞራ ያስተላለፈውን ዳኝነት ያስታውሰናልፀ አሁን ያለንበት ዘመን ዓመተ ምሕሚት በመሆኑ እግዚአብሔር ለጊዜው ቢታገሠንም በኃጢኣታቜን ዚምንጠዚቅበት ጊዜ አዘጋጅቶአልፀ ዛሬም ቢሆን ዚማናስተውለው ሆነን ካልሆነ በስተቀር እግዚአብሔር ተግሣጹን ማስተላለፍ አላቆምምፀ በምድራቜን ላይ በምናደርሰው ዚተዛባ ተግባር በጐርፍ፣ በድርቅ፣ በመሬት መንቀጥቀጥና በአዹር መዛባት እዚገሠጞን እንደሆነ ማስተዋል አለብንፀ

እግዚአብሔር ኚጥንቱ ኚጠዋቱ ጀምሮ ምድርን እንድንኚባኚባትፀ እንድናበጃት፣ እንድናጠብቃትና እንድናለማት አዞናልፀ ሆኖም ይህን ትእዛዙን ገሞሜ አድርገን በኬሜካልና በመርዛም ጋዝ ምድርን በመበኚል፣ደንዋን በመመጠርና ራቁቷን በማስቀሚት በምናደርገው ድርጊት አበሳ እዚፈጞምን እንደሆነ ያወቅነው አይመስልምፀ በዚህም ምክንያት በጐርፍ፣ በድርቅ ለሰው ልጆቜ በማይመቜ ዚኣዚር ፀባይ ወዘተ . . . ስጋት ውስጥ እዚወደቅን ነውፀ

በሌላም በኩል በምናወሳስበው ዚአስተዳደር ርእዮትና መሳሳብ ዚእግዚአብሔር ገንዘብ ዹሆነውን ሕዝብ እርስ በርሱ እንዲጋጭና ያላስፈላጊ አደጋ ላይ እንድወድቅ እያደሚግን ነውፀ በዚህም ጠንቅ ሰላም እዚደፈሚሰ፣ ፍቅርና አንድነት እዚላላ ዚሃይማኖት ክብርና ልዕልና እዚተነካ ራሳቜንንም እዚጐዳን ነውፀበዚህ ሁሉ ተግባራቜን እግዚአብሔርን እያሳዘንን ነውፀ ይህ ሊገባንና ሊቈሹቁሹን ይገባልፀ

ዚተወደዳቜሁ ዚመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቜን ምእመናንና ምእመናት
ለቜግሮቜ ሁሉ መፍትሔ አላ቞ውፀ መፍትሔውም ዹሚገኘው ኚእግዚአብሔርና ኚእኛ ነውፀ ኚእኛ በንስሓ ተመልሰን ኚልብ እግዚአብሔርን ይቅርታ መጠዹቅና ኹክፉ ተግባራቜን በእውነት መጞጞት ይጠበቃልፀ እግዚአብሔር ደግሞ ይህንን ዓይነቱ ንስሓ ኹኛ መኖሩ ሲመለኚት ምሕሚትና ይቅርታን ይለግሰናልፀበዚህም መፍትሔና ፈውስ ይገኛልፀ ኹዚህ አንጻር በአሁኑ ጊዜ ለሀገራቜንና ለዓለማቜን ስጋት ዹሆኑ ዚጊርነት ክሥተቶቜ፣ ዚመሬት መንቀጥቀጥ፣ ዹአዹር መዛባት፣ዚድርቅ መኚሠት፣ዚጎርፍ መጥለቅለቅ ዹሰላም መደፍሚስ፣ ዚሰላማውያን ወገኖቜ መጎዳት፣ ዹፍቅርና ዚአንድነት መላላት ወዘተ. . . . ኚምድራቜን ተወግደው ፍጹም ምሕሚትና ሰላም እናገኝ ዘንድ በኃጢኣታቜን ተጞጜተን በምህላ ንስሓ መግባት አለብንፀ

ኹዚህ አኳያ ኚጥንት ጀምሮ በቀተክርስቲያናቜን ቀኖናዊ ሥርዓት መሠሚት በዚዓመቱ ዚሚጟመው ጟመ ነነዌ ለዚህ አመቺ ጊዜ ስለሆነ ኚዚካቲት ፫ ቀን ፳፻፲፯ ዓመተ ምሕሚት ጀምሮ ለሊስት ቀናት ኹልኂቅ እስኚ ደቂቅ ሁላቜንም ጠዋትና ማታ በዚቀተክርስቲያኑ ዐውደ ምሕሚት እዚተገኘን በንስሓ በዕንባ በጞሎት በምህላ ዚእግዚአብሔርን ምሕሚትና ይቅርታ እንድንጠይቅፀ እንደዚሁም በሀገራቜንና በውጭ ያላቜሁ ሊቃውንተ ሕዝብ ቀኖናውን ጠብቃቜሁ ይህንን በማስፈጞም ምህላውን በቀኖናው መሠሚት እንድታኚናውኑ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታቜንን እናስተላልፋለንፀ

እግዚአብሔር አምላካቜን ምሕሚቱን ይቅርታውንና ሰላሙን ለሀገራቜንና ለዓለማቜን ይስጠንፀ ምህላቜንንም ይቀበልልንፀ
“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቊቿን ይባርክ” ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስምወዕጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት
ጥር ፳፱ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት ዚግብፅ  ኊርቶዶክስ ቀተክርስቲያን ልዑካንን በጜ/ቀታ቞ው ተቀብለው አነጋገሩ።

ጥር 24 ቀን 2017.ዓ.ም.
=================
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት በብፁዕ አቡነ አምባ ቢመን  ዚሚመራውን ዚግብፅ ኮፕቲክ ቀተክርስቲያን ልዑካንን በጜ/ቀታ቞ው ተቀብለው አነጋግሹዋል ።ልዑካኑ  ኚብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዋድሮስ ዚግብጜ ኮፕቲክ ቀተክርስቲያን ፓትርያርክ   ዹተላኹ ዚሰላምታ መልእክት ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በማቅርብ  በሁለቱ ተቋማት መካኚል  ዹነበሹውን ዚጋራ ትብብር በማጠነኹር ላይ ውይይት አድርጓል። እንደ ልዑካኑ ገለጻ ኹዚህ በፊት በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ዹሚገኙ ዚጋራ ዚመገልገያ ሥፍራዎቜን  በጋራ መጠቀም ዚሚስቜል አንድነት  ዹነበሹን በመሆኑ አሁንም ዹተለመደውን ሥራ ማለትም  ዚኢትዮጵያ  ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ  በምትገኝበት  ቊታ ሁሉ ዚኮፕቲክ ቀተክርስቲያን  እንድትገለገል ዚኮፕትክ ቀተክርስቲያን ባለቜበት ሁሉ ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ቀተክርስቲያን  መገልገል እንድትቜል ዚሚያስቜል ሁኔታን ማስቀጠል ነው ብለዋል ።

ልዑካኑን በጜሕፈት ቀታ቞ው ያነጋገሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ይዘውት ዚመጡት ሐሳብ ዹነበሹና በመገልገያ ሥፍራ በማጣት ዚሚ቞ገሩ ምዕመናን  ዚሚታደግ ሐሳብ ነውና በአድናቆትና በደስታ   ተቀብለነው እዚተገበርነው ያለ ቢሆንም አሁንም ተጠናክሮ እንዲቀጥል  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዋድሮስም ይህንን ዹሰላም መልእኚተኛ እና በሁለቱም ተቋማት ውስጥ ዹሚገለገሉ ምዕመናን ቜግርን ዚፈታ ሐሳብ በልዑካኑ በኩል ዚማጠናኚሪያ ሐሳብ እንድንሰጥበት ስላደሚጉ እናመሰግናለን ብለዋል።

በመቀጠልም ልዑካኑ ኚብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዋድሮስ  ዚግብፅ ኮፕቲክ  ፓትርያርክ ዹተላኹውን ስጊታ ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጚጌ ዘመንበሹ ተክለሃይማኖት ያስሚኚቡ ሲሆን ቅዱስነታ቞ውም  ስለ ስጊታው አመስገነዋል። በመጚሚሻም ልዑካኑ ስለተደሚገላ቞ው መልካም አቀባበልና ይሁንታ መደሰታ቞ውን ገልጾው ዚቅድት ሥላሎ ካ቎ድራል በኢትዮጵያውያን ምዕመናን ትኚሻ ተሠርቶ ማለቁ እጅግ ደስ እንዳሰኛ቞ው በመግለጜ ዚግብጜ ኮፕቲክ እንደተለመደው በካ቎ድራሉ መገልገል ዚሚቜሉበት  መንገድ ስለ ተመቻ቞ላ቞ው አመስገነው ዚውይይቱ ፍጻሜ ሆኗል።

ዹ”ዝክሹ ኒቅያ ዓለም አቀፍ ጉባኀ” ኚሚያዚያ 20-24 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚካሔድ ሊቃውንት ጉባኀ አስታወቀ።

ጥር 23 ቀን 2017 ዓ.ም
****
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“”””””””””””””””””””””

ዚኢትዮጵያ ኊርቶዶክስ ተዋሕዶ ቀተክርስቲያን ሊቃውንት ጉባኀ ጥር 23ቀን 2017 ዓ.ም “ዹዝክሹ ኒቅያ ጉባኀን” ዓለም አቀፍ ጉባኀ በመንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጜሕፈት ቀት ለማካሔድ መርሐ ግብር መያዙ ይታወሳል።

ሆኖም ጉባኀውን በተሳካ ሁኔታ ማካሔድ ይቻል ዘንድ መርሐ ግብሩን ለሌላ ጊዜ ማስተላለፍ በማስፈለጉ ጉባኀው ኚሚያዚያ 20-24 ቀን 2017 ዓ.ም እንዲካሔድ መወሰኑን ሊቃውንት ጉባኀ ገልጿል ስለሆነም ጉባኀው በተያዘለት መርሐ ግብር መሰሚት ዚሚካሔድ ይሆናል።

ሊቃውንት ጉባኀ ያስተላለፈው ውሳኔ ደርሶናል እንደሚኚተለው ይነበባልፊ

ማሳሰቢያ
ጥር 23 ቀን 2017 ዓ.ም.
ዹዝክሹ ኒቅያ ጉባኀ ዚሚካሄድበት ቀን ማስተካኚልን ይመለኚታል።

ዚቅዱስ ሲኖዶስ መጋቢ ዹሆነው ሊቃውንት ጉባኀ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ በተወሰነለት መሠሚትፊ በአሁኑ ሰዓት ውይይትና ምክክር በሚያስፈልጋ቞ው ዚትውልድ ዐበይት ጥያቄዎቜ ላይ በመምኹር ያለፈውን
ለማጜናት፣ ዚሚመጣውን ለማቅናት፥ ሃይማኖትና ቀኖናን ጠብቆ ለማስጠበቅ ዚሊቃውንት መሰባሰብ እጅግ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱፀ “ዝክሹ ኒቅያ” በሚል
ዓለም ዐቀፍ ጉባኀ ሊቃውንት ኚጥር 26-29 ቀን 2017 ዓ.ም. በአዲስ አበባ መንበሹ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቀተ ክህነት ለማካሄድ ታቅዶ እንቅስቃሎሲደሚግ ቆይቷል።

ሆኖም፩
1ኛ) ጉባኀው በመላ ሀገሪቱ ዹሚገኙ ዚጉባኀ ቀት መምህራንና ሊቃውንት ዚሚታደሙበት እንደመሆኑ፥ በተለይ በጠሹፉ ዚሀገራቜን ክፍል ዹሚገኙ
መምህራንን በበቂ ቊጥር ለማካተት እንዲቻል፥ ባለው ተጚባጭ ሁኔታ ተጚማሪ ጊዜ በማስፈለጉፀ

2ኛ) በጥር ወር በርካታ ሀገራዊ ክንውኖቜና ሃይማኖታዊ ክብሚ በዓላት በዚአካባቢው ዚሚካሄዱ በመሆናቾው ዚጉባኀው መካሄጃ ጊዜ እንዲስተ ካኚል ኚአንዳንድ አህጉሹ ስብኚት በተደጋጋሚ አስተያዚት በመሰጠቱፀ

3ኛ) ጉባኀው ኚዘመናት ቆይታ በኋላ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ዚሚካሄድና በቀተ ክርስቲያኒቱ ጉዳዮቜ ዙሪያ ጠቃሚ ውይይቶቜን በማካሄድ፥

ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኀ ዹሚጠቅም ዚውሳኔ ሐሳብና አስተያዚት ዚሚያቀርብ፥ አልፎም ዹአቋም መግለጫ ዚሚያወጣ በመሆኑፀዚቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ኚመካሄዱ ጥቂት ቀደም ብሎ ኚሚያዝያ 20-24ቀን 2017 ዓ.ም. እንዲካሄድ በሊቃውንት ጉባኀ መወሰኑን በአክብሮትእዚገለጞንፀ ዹአህጉሹ ስብኚት ዚሥራ ኀላፊዎቜ ዚተሳታፊዎቜ ልዚታ መመሪያ እስኚሚደርሳ቞ው ድሚስ ለጉባኀው ይመጥናሉ ዹሚሏቾውን መምህራን በመለዚት ዝግጅት እያደሚጉ እንዲቆዩ አደራ እንላለን።

ሊቃውንት ጉባኀ