ትምህርተ ሃይማኖትን የያዘ መጽሐፍ በእንግሊዝኛ ቋንቋ በአሜሪካ ታትሞ ተመረቀ፤ በሀገር ውስጥ ለሚገኙ አንባብያን በቅርቡ በኢትዮጵያ እንደሚታተም ተገለጸ።

የካቲት 20 ቀን 2017 ዓ.ም

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

የካቲት 17 ቀን 2017 ዓ.ም
ወርኀ ጾሙን የተራበውን በመመገብ የተራቈተውን በማልበስ በኃላፊነት ያለን የኅብረተሰብ መሪዎችም ፍትሕንና እኩልነትን በማስፈንና ከነገሮች ሁሉ በፊት ለሰላምና ለአንድነት ቅድሚያ በመስጠት ጾሙን እንድናሳልፍ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን::

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በእስራኤል ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የተመራ ልዑክን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ፡፡

የካቲት 6 ቀን 2017 ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የአክትስ ቸርች ኦፍ ሱዲን የሥራ ኀላፊዎችን   በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

የካቲት 1 ቀን 2017.ዓ.ም.

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ፍኖተ ጽድቅ ጠቅላላ ማኀበር ባካሔደው የነዳያን ምገባ መርሐ ግብር ላይ ተገኝተው ነዳያንን ከመገቡ በኋላ ቃለ በረከትና ቃለ ቡራኬ ሰጡ።

ጥር 29 ቀን 2016 ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የ2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ መግለጫ ሙሉ መልእክት የሚከተለው ነው፡፡

ጥር 29 ቀን 2017ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
+ + +
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ የተላለፈ የምህላ ሱባዔ፡-
‹‹ቀድሱ ጾመ ወስብኩ ምህላ አስተጋብኡ ሕዝበ ሊቃውንተ ሕዝብ፤ ጾምን ቀድሱ፣ጉባኤውንም አውጁ፤ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ ኣምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ቤት ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ (ኢዩ ፩÷፲፬)

ሁላችንም እንደምናውቀው ያለንበት ዓለም የመከራ ዓለም ነው፣ መከራው በኛ ስሕተትና ክፋት የመጣና እየሆነ ያለ መሆኑም ይታወቃል፤ እኛ የምንፈጽመው ጥቃቅንና ትላልቅ ግብረ ኃጢአት እግዚአብሔርን እንደሚያስቈጣ በቅዱስ መጽሐፍ ተረጋግጦ ያደረ ነው፤ ለዚህም ከነነዌ ነዋሪ ሕዝብ የበለጠ ማስረጃ የለንም፤ የነነዌ ከተማ ነዋሪዎች በፈጸሙት ግብረ ኃጢአት እግዚአብሔርን አስቈጥተዋል፤ ድርጊታቸው እግዚአብሔርን የሚያስቆጣ ቢሆንም እሱ ምሕረቱን ማስቀደም ስለፈለገ በዮናስ በኩል አስጠንቅቆአቸዋል፤ የነነዌ ነዋሪዎችም በዮናስ በኩል የደረሳቸውን የንስሓ ጥሪ ወዲያውኑ ተቀብለው በምህላ፣ በጾም፣ በጸሎት ንስሓ ስለገቡ እግዚአብሔር ፍጹም ይቅርታ አድርጎላቸዋል፤

• የተወደዳችሁ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያን ልጆቻችንና ወገኖቻችን !

እኛ ሰዎች ዛሬም በየሰዓቱ ብቻ ሳይሆን በየደቂቃው እግዚአብሔርን የሚያስቆጣ አበሳ እንደምንፈጽም ማወቅ ኣለብን፣ አበሳውና ኃጢኣቱ ሲበዛ እግዚአብሔር እውነተኛ ዳኛ ነውና ወደ ዳኝነት ተግባሩ ይገባል፤ይህ ደግሞ በሰብአ ትካት በሰዶምና በጎሞራ ያስተላለፈውን ዳኝነት ያስታውሰናል፤ አሁን ያለንበት ዘመን ዓመተ ምሕረት በመሆኑ እግዚአብሔር ለጊዜው ቢታገሠንም በኃጢኣታችን የምንጠየቅበት ጊዜ አዘጋጅቶአል፤ ዛሬም ቢሆን የማናስተውለው ሆነን ካልሆነ በስተቀር እግዚአብሔር ተግሣጹን ማስተላለፍ አላቆምም፤ በምድራችን ላይ በምናደርሰው የተዛባ ተግባር በጐርፍ፣ በድርቅ፣ በመሬት መንቀጥቀጥና በአየር መዛባት እየገሠጸን እንደሆነ ማስተዋል አለብን፤

እግዚአብሔር ከጥንቱ ከጠዋቱ ጀምሮ ምድርን እንድንከባከባት፤ እንድናበጃት፣ እንድናጠብቃትና እንድናለማት አዞናል፤ ሆኖም ይህን ትእዛዙን ገሸሽ አድርገን በኬሜካልና በመርዛም ጋዝ ምድርን በመበከል፣ደንዋን በመመጠርና ራቁቷን በማስቀረት በምናደርገው ድርጊት አበሳ እየፈጸምን እንደሆነ ያወቅነው አይመስልም፤ በዚህም ምክንያት በጐርፍ፣ በድርቅ ለሰው ልጆች በማይመች የኣየር ፀባይ ወዘተ . . . ስጋት ውስጥ እየወደቅን ነው፤

በሌላም በኩል በምናወሳስበው የአስተዳደር ርእዮትና መሳሳብ የእግዚአብሔር ገንዘብ የሆነውን ሕዝብ እርስ በርሱ እንዲጋጭና ያላስፈላጊ አደጋ ላይ እንድወድቅ እያደረግን ነው፤ በዚህም ጠንቅ ሰላም እየደፈረሰ፣ ፍቅርና አንድነት እየላላ የሃይማኖት ክብርና ልዕልና እየተነካ ራሳችንንም እየጐዳን ነው፤በዚህ ሁሉ ተግባራችን እግዚአብሔርን እያሳዘንን ነው፤ ይህ ሊገባንና ሊቈረቁረን ይገባል፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት
ለችግሮች ሁሉ መፍትሔ አላቸው፤ መፍትሔውም የሚገኘው ከእግዚአብሔርና ከእኛ ነው፤ ከእኛ በንስሓ ተመልሰን ከልብ እግዚአብሔርን ይቅርታ መጠየቅና ከክፉ ተግባራችን በእውነት መጸጸት ይጠበቃል፤ እግዚአብሔር ደግሞ ይህንን ዓይነቱ ንስሓ ከኛ መኖሩ ሲመለከት ምሕረትና ይቅርታን ይለግሰናል፤በዚህም መፍትሔና ፈውስ ይገኛል፤ ከዚህ አንጻር በአሁኑ ጊዜ ለሀገራችንና ለዓለማችን ስጋት የሆኑ የጦርነት ክሥተቶች፣ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ የአየር መዛባት፣የድርቅ መከሠት፣የጎርፍ መጥለቅለቅ የሰላም መደፍረስ፣ የሰላማውያን ወገኖች መጎዳት፣ የፍቅርና የአንድነት መላላት ወዘተ. . . . ከምድራችን ተወግደው ፍጹም ምሕረትና ሰላም እናገኝ ዘንድ በኃጢኣታችን ተጸጽተን በምህላ ንስሓ መግባት አለብን፤

ከዚህ አኳያ ከጥንት ጀምሮ በቤተክርስቲያናችን ቀኖናዊ ሥርዓት መሠረት በየዓመቱ የሚጾመው ጾመ ነነዌ ለዚህ አመቺ ጊዜ ስለሆነ ከየካቲት ፫ ቀን ፳፻፲፯ ዓመተ ምሕረት ጀምሮ ለሦስት ቀናት ከልኂቅ እስከ ደቂቅ ሁላችንም ጠዋትና ማታ በየቤተክርስቲያኑ ዐውደ ምሕረት እየተገኘን በንስሓ በዕንባ በጸሎት በምህላ የእግዚአብሔርን ምሕረትና ይቅርታ እንድንጠይቅ፤ እንደዚሁም በሀገራችንና በውጭ ያላችሁ ሊቃውንተ ሕዝብ ቀኖናውን ጠብቃችሁ ይህንን በማስፈጸም ምህላውን በቀኖናው መሠረት እንድታከናውኑ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፤

እግዚአብሔር አምላካችን ምሕረቱን ይቅርታውንና ሰላሙን ለሀገራችንና ለዓለማችን ይስጠን፤ ምህላችንንም ይቀበልልን፤
“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ” ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስምወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት
ጥር ፳፱ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የግብፅ  ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ልዑካንን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

ጥር 24 ቀን 2017.ዓ.ም.
=================
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በብፁዕ አቡነ አምባ ቢመን  የሚመራውን የግብፅ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያን ልዑካንን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል ።ልዑካኑ  ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዋድሮስ የግብጽ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ   የተላከ የሰላምታ መልእክት ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በማቅርብ  በሁለቱ ተቋማት መካከል  የነበረውን የጋራ ትብብር በማጠነከር ላይ ውይይት አድርጓል። እንደ ልዑካኑ ገለጻ ከዚህ በፊት በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር የሚገኙ የጋራ የመገልገያ ሥፍራዎችን  በጋራ መጠቀም የሚስችል አንድነት  የነበረን በመሆኑ አሁንም የተለመደውን ሥራ ማለትም  የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  በምትገኝበት  ቦታ ሁሉ የኮፕቲክ ቤተክርስቲያን  እንድትገለገል የኮፕትክ ቤተክርስቲያን ባለችበት ሁሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን  መገልገል እንድትችል የሚያስችል ሁኔታን ማስቀጠል ነው ብለዋል ።

ልዑካኑን በጽሕፈት ቤታቸው ያነጋገሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ይዘውት የመጡት ሐሳብ የነበረና በመገልገያ ሥፍራ በማጣት የሚቸገሩ ምዕመናን  የሚታደግ ሐሳብ ነውና በአድናቆትና በደስታ   ተቀብለነው እየተገበርነው ያለ ቢሆንም አሁንም ተጠናክሮ እንዲቀጥል  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዋድሮስም ይህንን የሰላም መልእከተኛ እና በሁለቱም ተቋማት ውስጥ የሚገለገሉ ምዕመናን ችግርን የፈታ ሐሳብ በልዑካኑ በኩል የማጠናከሪያ ሐሳብ እንድንሰጥበት ስላደረጉ እናመሰግናለን ብለዋል።

በመቀጠልም ልዑካኑ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዋድሮስ  የግብፅ ኮፕቲክ  ፓትርያርክ የተላከውን ስጦታ ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ያስረከቡ ሲሆን ቅዱስነታቸውም  ስለ ስጦታው አመስገነዋል። በመጨረሻም ልዑካኑ ስለተደረገላቸው መልካም አቀባበልና ይሁንታ መደሰታቸውን ገልጸው የቅድት ሥላሴ ካቴድራል በኢትዮጵያውያን ምዕመናን ትከሻ ተሠርቶ ማለቁ እጅግ ደስ እንዳሰኛቸው በመግለጽ የግብጽ ኮፕቲክ እንደተለመደው በካቴድራሉ መገልገል የሚችሉበት  መንገድ ስለ ተመቻቸላቸው አመስገነው የውይይቱ ፍጻሜ ሆኗል።

የ”ዝክረ ኒቅያ ዓለም አቀፍ ጉባኤ” ከሚያዚያ 20-24 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚካሔድ ሊቃውንት ጉባኤ አስታወቀ።

ጥር 23 ቀን 2017 ዓ.ም
****
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ
“”””””””””””””””””””””

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት ጉባኤ ጥር 23ቀን 2017 ዓ.ም “የዝክረ ኒቅያ ጉባኤን” ዓለም አቀፍ ጉባኤ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ለማካሔድ መርሐ ግብር መያዙ ይታወሳል።

ሆኖም ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ ማካሔድ ይቻል ዘንድ መርሐ ግብሩን ለሌላ ጊዜ ማስተላለፍ በማስፈለጉ ጉባኤው ከሚያዚያ 20-24 ቀን 2017 ዓ.ም እንዲካሔድ መወሰኑን ሊቃውንት ጉባኤ ገልጿል ስለሆነም ጉባኤው በተያዘለት መርሐ ግብር መሰረት የሚካሔድ ይሆናል።

ሊቃውንት ጉባኤ ያስተላለፈው ውሳኔ ደርሶናል እንደሚከተለው ይነበባል፦

ማሳሰቢያ
ጥር 23 ቀን 2017 ዓ.ም.
የዝክረ ኒቅያ ጉባኤ የሚካሄድበት ቀን ማስተካከልን ይመለከታል።

የቅዱስ ሲኖዶስ መጋቢ የሆነው ሊቃውንት ጉባኤ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በተወሰነለት መሠረት፦ በአሁኑ ሰዓት ውይይትና ምክክር በሚያስፈልጋቸው የትውልድ ዐበይት ጥያቄዎች ላይ በመምከር ያለፈውን
ለማጽናት፣ የሚመጣውን ለማቅናት፥ ሃይማኖትና ቀኖናን ጠብቆ ለማስጠበቅ የሊቃውንት መሰባሰብ እጅግ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፤ “ዝክረ ኒቅያ” በሚል
ዓለም ዐቀፍ ጉባኤ ሊቃውንት ከጥር 26-29 ቀን 2017 ዓ.ም. በአዲስ አበባ መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ለማካሄድ ታቅዶ እንቅስቃሴሲደረግ ቆይቷል።

ሆኖም፦
1ኛ) ጉባኤው በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የጉባኤ ቤት መምህራንና ሊቃውንት የሚታደሙበት እንደመሆኑ፥ በተለይ በጠረፉ የሀገራችን ክፍል የሚገኙ
መምህራንን በበቂ ቊጥር ለማካተት እንዲቻል፥ ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ተጨማሪ ጊዜ በማስፈለጉ፤

2ኛ) በጥር ወር በርካታ ሀገራዊ ክንውኖችና ሃይማኖታዊ ክብረ በዓላት በየአካባቢው የሚካሄዱ በመሆናቸው የጉባኤው መካሄጃ ጊዜ እንዲስተ ካከል ከአንዳንድ አህጉረ ስብከት በተደጋጋሚ አስተያየት በመሰጠቱ፤

3ኛ) ጉባኤው ከዘመናት ቆይታ በኋላ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚካሄድና በቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳዮች ዙሪያ ጠቃሚ ውይይቶችን በማካሄድ፥

ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የሚጠቅም የውሳኔ ሐሳብና አስተያየት የሚያቀርብ፥ አልፎም የአቋም መግለጫ የሚያወጣ በመሆኑ፤የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ከመካሄዱ ጥቂት ቀደም ብሎ ከሚያዝያ 20-24ቀን 2017 ዓ.ም. እንዲካሄድ በሊቃውንት ጉባኤ መወሰኑን በአክብሮትእየገለጸን፤ የአህጉረ ስብከት የሥራ ኀላፊዎች የተሳታፊዎች ልየታ መመሪያ እስከሚደርሳቸው ድረስ ለጉባኤው ይመጥናሉ የሚሏቸውን መምህራን በመለየት ዝግጅት እያደረጉ እንዲቆዩ አደራ እንላለን።

ሊቃውንት ጉባኤ