ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በዛሬው ዕለት በተደረገው የአቀባበል ሥነሥርዓት ላይ ያስተላለፉት አባታዊ መልዕክት

‹‹ወዝንቱ ሕጉ ለቤት ዘዲበ ርእሰ ደብር
በተራራው ራስ ላይ ያለው የቤቱ ሕግና ሥርዓት ይህ ነው››
(ሕዝ.43+10)
‹‹አይድዖሙ ሥዕለ ዝንቱ ቤት ይዕቀቡ ኵሎ ሥዕሎ ወትእዛዞ ወይግበርዎ ወዝንቱ ሕጉ ለቤት ዘዲበ ርእሰ ደብር ሥርዓቱንና ሕጉን ይጠብቁና ያደርጉትም ዘንድ የዚህን ቤት ክብርና መልክ ንገራቸው›› በሚለው ቃል ክብሩ የተገለጠው፣የአገልግሎታችን መዳረሻ የሆነው የቤታችን ሕግና ሥርዓት በርቱዕ እምነት ማንነታችንን ቀርጾ፣ ከምግባረ ሃይማኖት ጋር አዋሕዶ ወደ እውነተኛ ወደባችን (ወደክርስቶስ) ለመድረስ የሚያበቃ ከውድቀት የምንጠበቅበት ሕገ ርትዕ መሆኑ የታመነነው፡፡

ከዓለም ሁሉ ከፍ ብሎ የከበረውና የተቀደሰው የእግዚአብሔር ቤት እውነተኛ መልክም የተጨነቁትን ማረጋጋት፣ ተሰፋ ላጡ ወገኖች ተሰፋ መሆን፣ በሕዝቡ መካከል መተማመንን ማስፈን፣ ፍቅርን፣ አንድነትንና ሰላምን ማወጅ ነው፡፡ የዚህን ቤት ትክክለኛ መልክ፣ መውጫውንና መግቢያውን፣ሥርዓቱንና ሕጉን ተረድተን በማስተዋል እንድንኖርበትም የቤቱ ባለቤት “ቅዱሰ ቅዱሳን” ብሎ ሰይሞታል፡፡ነገር ግን ‹‹እለ አልቦሙ ኀሊና ወልብ የዐቅቡ ግብሮሙ ወሥርቶሙ በዘተአዘዙ ናሁ ሌሊት ትዴግኖ ለመዓልት ፣ ወፀሐይ ይዴግኖ ለወርኀ በከመ ተአዘዘ። አእምሮ የሌላቸው ማሰብ የማይችሉ ግዑዛን ፍጥረታት ከእግዚአብሕር በታዘዙት መሰረት ግብራቸውንና ወሰናቸውን ይጠብቃሉ ፤ሌሊት ትእዛዙንና ሥራዋን ጠብቃ ቀንን ትከተለዋለች፡፡ ፀሐይም በታዘዘው መሰረት ጨረቃን ይከተለዋል፡፡ እያንዳንዳቸውም በሕግና በሥርዓት መኖር ተስኖት ሕግን ሲተላለፍ፣ ሥርዓትን ሲያፍርስ ይታያል፡፡መጽ ሲኖዶስ አንቀጽ 45 ገጽ 22)

በእኛም የአገልግሎት ዘመን የዚህ ቤት ሠሪና አስገኝ የሆነው አምላከ ምሕረት እግዚአብሔር በሚደንቀው የፍቅሩ ዝምታ ታግሶን ነው እንጂ ዓለሙን ሁሉ አቅፎ በሚይዝ ልባቸውና በሰፊ ትክሻቸው ሁሉን ተሸክመው፣ ሕይወታቸው የመላእክት ያህልሆኖላቸው ለደካሞቹ ሲተጉ በኖሩት፣የቤቱን ሕግና ሥርዓት በሚያውቁት አባቶቻችን መንፈሳዊ ተጋድሎ ተጠብቆ የኖረውን የቤቱን ጥንታዊ መልክ የሚለወጡ፣ ከምግባረ ሃይማኖት የሚያድጡ አንዳንድ ጉደለቶቻችን መታያት ከጀመሩ ዋል አደር ብለዋል፡፡

በመሆኑም የቤቱ መልክና ሥርዓት የተዋበ እጅግ ከፍ ያለ ስለሆነ እኛን በክብር ከፍ የሚያደርግ መሆኑን መረዳት አቅቶን ከዓለም ሕግ፣ ከሥነ ፍጥረት ሥርዓት በታች አሳንሰን ካየነው የቤታችንን ውበት በራሳችን እናጣዋለን፡፡

የልዩነት፣ የጠብ፣ የጭቅጭቅ ቤትም ካደረግነው በክብር ፈንታ ሐሳር፣ በከፍታ ፈንታ ውድቀት በራሳችን ላይ እንዳናመጣ የቤቱን ሥርዓትና ሕግ በጋራ ትብብር ወደነበረበት መመለስ ግድ ይለናል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር የሠራው፣ አባቶቻችን የደከሙበት
የቤታችን ጥንታዊ መልክ ሰላምና ፍቅር፣ስምምነትና አንድነት፣ቅንነትና አስተዋይነት ጽናትና ደግነት ነው:: እንዲህ ያለ መልክና ውበት ባለው ቤት ስንኖር ደግሞ የዓለም መልክ ሊታይብን አይገባምና መልካችን አምላካዊ፣ አለባበሳችን ሃይማኖታዊ፣አኗኗራችን ሰማያዊ መሆን ይኖርበታል፡፡

ከቤቱ መልክ ወጥተን እርስ በእርሳችን ከተለያየን ለማይጠገን ስብራት፣ለማይታረም ስሕተት የምንዳረግ እንሆናለንና አንድም ነገር ሳይጎድልብን በፍጹም ደስታ የሚያኖረንን ይህን ቤት በክብር እንጠብቀው፡፡ወደፊትም ከአለፈው ታሪካችን እየተማርን፣ በቤቱ ሕግና ሥርዓት፣ በጋራ ውይይት ስሕተቶቻችንን እያረምን ትውልዱ ከእውነትና ከታሪካዊ መረጃ የራቀ እንዳይሆን መሥራት የመሪነት ተግባራችን ነው፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት
ክቡራንና ክቡራት ልጆቻችን!

“ከሁሉ በተቀደሰው፣ በዙሪያው ካሉት ሀሉ ከፍ ባለው” የእግዚአብሔር ቤት እንደየደረጃችን ለአገልግሎት ስንጠራ መዐርጉንና ሀብቱን፣ የመከበር ዕሴቱንና ዐስቡን ብቻ ሳይሆን የሥልጣኑ ምንጭ፣ የተልእኮው ሥምረት፣ የማዕረጉ ድምቀት ለሆነው የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ቦታ አሠራር በሚያመች ሕይወት ካገለገልን አገልግሎታችን በፍቅር ይጸናል፡፡ የሚማርክ መዓዛ ቅድስና ያለው ሕይወት፣የሚዘከር ማንነት ይኖረናል።

በመሆኑም ‹‹ከመንፈስ ቅዱስ ተለይተን እኛ ለእግዚአብሔር እንግዶች ነንና››በእርሱ እየተመራን በተሠጠን የአገልግሎት ጊዜ እንቅፋቶችን ሁሉ በጋራ በማስወገድ ሐዋርያዊ መሠረት ያለውን አንድነታችንንና ሰላማችንን በማጽናት፣ በምድር ሆነን በሰማይ ሥርዓት እየኖርን ለሀገራችን እድገት፣ ለቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት መስፋፋት ከልብ መሥራት ይገባናል ፡፡ (ቅዱስ አትናቴዎስ)

ሁላችሁም እንደምታስታውሱት እኔና ወንድሜ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ከአሁን በፊት በዚሁ ቤት አብረን አገልግለናል፡፡ ሰውንና እግዚአብሔርን ለማገልገል ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠን የሦስቱ ዓመታት የአገልግሎት ዘመንም የልባችንን እልፍኝ ሰፋ አድርገን የሚጠበቅብንን ለመሥራት፣ የሁሉም ልጆቻችን አባቶች ሆነን ሁሉንም በእኩልነት ለማገልገል እንሠራለን ብለን እናምናለን፡፡
ለቤቱ ክብር በሚመጥን በመልካም ምግባር በተጌጠ ሕይወት በዚህ መንገድ መሥራትና ማስተዳደር ከቻልን ከየት ተነሥተን ወዴት እንደምንሄድ ስለምናውቅ የተቀበልነውን አደራ ለመወጣት የቤተ ክርስቲያናችንን እውነት ከሕዝባችን ጋር ሆነን ለዓለሙ ሁሉ
አሰምተን በመናገር ታሪካዊ ክብሯን መጠበቅና ማስጠበቅ እንደምንችል ምንም ጥርጥር
የለውም፡፡

‹‹ቢቻላችሁ ከሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ›› ተብሎ እንደተጻፈው የቤተ ክርስቲያናችንን ልዕልና፣መንፈሳዊ ተልእኳዋንና ክብሯን በጠበቀ መልኩ ከመንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማት ጋር በትብብር መሥራት ጉዳት ስለሌለው ከሁሉም ጋር መልካም ግንኙት በመፍጠር የቀደሙትን ባለውለታዎች ሳንረሳ ለሠሩት ሥራ ዕውቅና በመስጠት የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን በማስፈጸም ሀገራችንንና ቤተ ክርስቲያናችንን ወደ ከፍታ
የሚያወጣ፣በዓለም ዙሪያ ለሚገኙት ምእመናንና ለሌሎቹም የሚጠቅም ሥራ በመሥራት ለተሻለ ውጤት እንበቃለን፡፡

ነገር ግን የማገዝ አቅም የሌለው ሰው ያማል፣የማረም አቅም የሌለው ይሳደባል የመደገፍ አቅም የሌለው ሰው ይጠልፋል፡፡ በመጨረሻም ሁሉም አብሮ ይወድቃል፡፡ እንደሚሉት ምሁራን አብሮ ላለመውደቅ ከመጠላለፍና ከመተማማት ይልቅ መተባበር በመካከላችን እንዲኖር ሁላችሁም በጸሎትና በሐሳብ እንድታግዙን አበትእግሥት በሆኑት ቅዱስ አባታችን ፊት አደራ እንላለን ፡፡ (ሮሜ 12፡18)

ያለ ትብብር ምንም ነገር ማድረግ አይቻልም እና የቤቱ ጥንታዊ መልክ አንዱ ያንዱ ምልዐት መሆኑን ተረድተን ‹‹ከወራጁ ከፍ ያለ ማድጋ አይሞላም ዝቅ ያለ ማሰሮ ግን
ይሞላል›› እንደሚባለው በጎውን ምክር ለመምከር
ራሳችን ዝቅ በማድረግ ከቅዱስ አባታችን፣ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰጠውን መመሪያ እየተቀበልን በሞቱ የዳነውን በደሙ የከበረውን ሕዝበ ክርስቲያን መጠበቅና በአግባቡ ማገልገል ይኖርብናል።

የመንፈስ ቅዱስ ልጅነትን ከማግኘት ጀምሮ ከንዑሳን መዐርጋት እስከ ዐበይት መዐርጋት የደረስነው አባቶችና በውስጥም በውጪም ያላችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ራስን ለቤተ ክርስቲያን ቀኖና ማስገዛት፣ከሐዋርያዊ መንበር የሚወስነውን ውሳኔ የሚሰጠውን መመሪያ አክብሮ መቀበል ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓት እንጂ ባርነት አይደለምና እርስ በእርሳችን መነቃቀፉን ትተን ሰላማችን በማጽናት አንድ እንሁን፡፡ የቤቱ መልክ ሰላም፣ፍቅርና አንድነት ነውና ለክፉ ሳይሆን ለበጎ እንፈላለግ።

በመጨረሻም ባልተገባ ሥዕለ ሕሊና የሚያየን ዓለም በመካከላቸው እንደ ገነት በተተከለች ቤተ ክርስቲያን እየኖሩ ‹‹እፎ ኮኑ ለሙስና…እንዴት ለጥፋት ሆኑ›› እንዳይለን ክፉኛ ከሚጎዱ የእርሰ በእርስ ልዩነቶች የሚጠብቀን የጋራ የሆነ የትኩረት አቅጣጫ እንዲኖረንና ነባሩን የቤታችንን መልክ እግዚአብሔር በሰጠን በቤቱ ሕግ ማስቀጠል እንድንችል ለሁሉም ውሉደ ቤተ ክርስቲያን ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡ (መዝ.73፥18)
አግልግሎታችን ሰማያዊና ምድራዊ መግቦት ስለሆነ መጪውን ዘመን ከሩቅ ተመልክተን ላለውና ለሚመጣው ትውልድ የሚሆን በጎ ሥራ የምንሠራበት በአንድ ልብ ሆነን ለተጠራንበት መንፈሳዊ ተልእኮ የምንተጋበት ጊዜ ያድርግልን የቅዱስ አባታችን ቡራኬ ይድረሰን አሜን ፡፡

‹‹ወስብሐት ለእግዚአብሔር››

ግንቦት 25 ቀን 2017 ዓ.ም
አባ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና
የራያ ሀገረ ሰብከት ሊቀ ጳጳስ