ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በባሕታዊ አባ ተስፋ ማርያም ሕልፈተ ሕይወት የተሰማቸውን ኅዘን በመግለጽ አባታዊ መልዕክት አስተላልፈዋል፤ የብፁዕነታቸው አባታዊ መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ይነበባል::
የኃዘን መግለጫ‹‹ነገረ ገድሉ መዓርዒር፣ ለተናግሮ ዕፁብ ግብር፣ ወዲበ ርእሱኒ አክሊል ዘየዐስዮ መኰንነ ጽድቅ…. የተጋድሎው ነገር ያማረ፣
ሥራውም ለመናገር ድንቅ የሆነ፣ በራሱም ላይ መኰንነ ጽድቅ እግዚአብሔር የሚያስረክበውን ድል የመንሣት አክሊል የሚቀዳጅ ነው›› (2ጢሞ 4÷8፤ቅዱስ ያሬድ ዘእምነገረ ቅዱስ አትናቴዎስ)
የላመ የጣመ ሳይቀምሱ፣የሞቀ የደመቀ ሳይለብሱ፣በዐት አጽንተው፣ሥርዓተ ምንኵስናውን አክብረው ድንቅ በሆነ
መንፈሳዊ ተጋድሎ ከ50 ዓመት በላይ የኖሩት፣ ለራያና አካባቢው
ሕዝበ ክርስቲያን የእምነትና የመንፈስ ጽናት ምሳሌ የነበሩት ባሕታዊ አባ ተስፋ ማርያም ጌታሁን ማረፋቸውን የሰማነው በከፍተኛ ኃዘን ነው፡፡
ከዓለማዊ ግብር በመለየት፣ እስከ ሞት ድረስ በታማኝነት የብሕትውናውን ሕይወት በእውነት የኖሩት እኒህ አባት ነቀፋ የሌለበት እምነታቸውና የምነና ሕይወታቸው በእግዚአብሔርና በሰው ፊት የከበረ በመሆኑ የጽድቅ ባሕርይ ምሳሌ ሆነው በምንኵስና ተጋድሎ ታሪክ በክብር ሲታወሱ ይኖራሉ፡፡
በመከራ ከተሞላው ከዚህ ክፉ ዓለም ድካም ማረፍ ለእርሳቸው የማይጠፋ የሕይወት አክሊልን የሚቀዳጁበት ቢሆንም በፍቅር የሚገሥጽ፣በመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያንጽ አባትን ማጣት ለእኛ ጉዳቱ ከፍተኛ ስለሆነ ጥላቻንና መራራቅን የሚያሰፉ ንግግሮችና ድርጊቶች በበዙበት፣ሕዝባችን በልዩ ልዩ ችግር ውስጥ ባለበት፣በዚህ ጊዜ ለእውነትና ለፍትሕ ቆመው የኖሩትን፣
በጸሎት በምክር የሚረዱንን እኒህን ደግና ታላቅ አባት በማጣታችን ኀዘናችንጥልቅ ነው፡፡
በመሆኑም በባሕታዊ አባ ተስፋ ማርያም ጌታሁን ሕልፈተ ሕይወት የተሰማንን ኃዘን እየገለጸን ለእርሳቸው ዕረፍተ ነፍስን ለመላው የራያና አካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን መጽናናትን
እንመኛለን፡፡
ነሐሴ 11 ቀን 2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ
አባ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ