የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ በመሆን ለተመደቡት ለመልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ በሀገረ ስብከቱ አዳራሽ በደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው ።
ነሐሴ 19 ቀን 2018 ዓ.ምበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ ከነሐሴ 8 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ በመሆን ለተመደቡት ለመልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ አቀባበል ተደረገላቸው ።
በአቀባበሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የዳውሮ ኮንታ ከንባታና አላባ ጠንባሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት መምሪያ ኃላፊዎች የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ክፍል ኃላፊዎችና ሠራተኞች የክፍላተ ከተማ ኃላፊዎችና ልዩ ልዩ ሠራተኞች የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችና አገልጋዮች ተገኝተዋል ።
መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተጀመረ ሲሆን ለሥራ አስኪያጁ የሥራ ዘመን መመሪያ ይሆን ዘንድ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 20 ከቁጥር 26 ጀምሮ ተነቦ ለመርሐ ግብሩ ተስማሚ የሆነ ወረብ በቦሌ ኆኅተ ብርሃን ቅድስት ማርያም ሊቃውንት መዘምራን
ቀርቧል ።
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ክቡር መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ የሢመት ደብዴቤ ከተነበበ በኋላ የሀገረ ስብከቱ ክፍል ኃላፊዎች እና የክፍላተ ከተማ ቤተክህነት ሊቃነ ካህናት በጉባኤው ፊት ቀርበው ትውውቅ ተደርጓል ። በሊቃውንትም ቅኔ ተበርክቷል ።
የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ስብከተ ወንጌልን፣ ሰበካ ጉባኤን ፣ሰንበት ትምህርት ቤትን በማደራጀትና በማስፋፋት ፣ ቤተክርስቲያንን ጠብቆ በማስጠበቅ ሁለንተናዊ ልማትን እንዲያጠናክሩ ፣ ሕገ ቤተክርስቲያንን ጠብቀው የመልካም አስተዳደር ችግርና ሙስናን እንዲቀርፉ ኃላፊነት ተሰጥቶአቸዋል።
ክቡር ሊቀ ሊቃውንት ቆሞስ አባ ተ/ሃይማኖት ወልዱ ሰለ ሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ያላቸውን የሥራ ክህሎት በመግለጽ ቤተ ክርስቲያንን አብረን እናሻግራት ማሻገር ባንችል ባለቤት ሆኖ የመሠረታት ክርስቶስ ያሻግራታል እኛ ሰጥመን እንዳንቀር ሲሉ ማስጠንቀቂያ አዘል ምክራቸውን ለግሰዋል።
የቦሌ ኆኅተ ብርሃን ቅድስት ማርያም ተወካይ ክቡር መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በደብራችን ዘርፈ ብዙ ሰዋዊ እና የመሠረተ ልማት ተግባሮችን አከናውነዋል በማለት በዝርዝር የሠሯቸውን ሥራዎች አቅርበዋል።
መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጣቸውን ኃላፊነት በታማኝነት እንደሚወጡ በሢመቱ ላይ የተነበበውን ዝርዝር መመሪያ በማንሳት አሁን ላይ ሀገረ ስብከቱን የተጋረጡበትን ተግዳሮቶች በጋራ እንቀርፋለን ብለዋል።
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ በሮሜ 3፣ 11 በመጥቀስ ወንጌል የሰውን ልጅ በኃጢአቱ እንደምትከስ በመጥቀስ ከውድቀታችን በንስሐ ልንመለስ ይገባል ብለዋል።
ብፁዕነታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጥንታዊነትና ታሪካዊ መሆኗን በመጥቀስ
” ተሿሚው ወንድምና ልጃችን ወደፊት በሚያከናውኗቸው ተግባራት ከብሔርና ከቡድን አሠራር ነጻ የሆነ መዋቅር ቤተክርስቲያንን ብቻ ማዕከል ያደረገ አድሏዊ ያልሆነና እውነተኛ የመንፈስ ቅዱስ ሀሳብን በአሠራር በመዘርጋት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔና ልዕልና በማክበር የበላይ አካል መመሪያና ለሀገረ ስብከቱ የተሰጠውን ደንብ ጠብቀው በቴክኖሎጂ የታገዘ አሠራር የፋይናንስና ንብረት አስተዳደሩን ግልጽ፣ ዘመናዊና ቁጥጥር የሚደረግበት በማድረግ ሙስናንና ብልሹ አሠራርን ፈጽመው እንደሚያጠፉ ትልቅ ተስፋና አደራ ጭምር ጥለንባቸዋል።”
ብለዋል።
©የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/