“የማይኾን ጸጸት እንዳንጸጸት በሰዓቱ እና በጊዜው ንስሐ እንግባ” ብጹዕ አቡነ አብርሃም ፤

ባሕር ዳር-ኢትዮጵያ

ሚያዚያ ፳፭ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲን የጠቅላይ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ የባሕር ዳር እና ሰሜን ጎጃም ሀገረ ሰብክት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ አብርሃም የስቅለት በዓልን ምክንያት በማድረግ ትምህርት እና አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

ብጹእነታቸው እግዚአብሔር የተናቁትን ከፍ ያደርጋል፤ የተረሱትን ያስታውሳል ብለዋል፡፡ በሰው ዘንድ ነውረኛ የተባሉትን ከነውር አንጽቶ እና ቀድሶ ልጁ ያደርጋል ነው ያሉት፡፡ ጌታውን የሸጠው ይሁዳ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ለታላቅ ነገር መርጦት ሳለ ጌታውን አሳልፎ ሰጥቷል ያሉት ብጽዑነታቸው ንስሐ፣ መጸጸት፣ በድያለሁ፣ አጥፍቻለሁ ብሎ በሰዓቱ እና በጊዜው ወደ እግዚአብሔር መቅረብ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

ንስሐ ሰዓቱ ካለፈ፣ ጊዜው ከባከነ፣ በሩ ከተዘጋ ለምንም አይጠቅምም ነው ያሉት፡፡ የይሁዳ ጸጸት ከተዘጋና ሁሉንም ነገር ካከተመ በኋላ እንደነበርም አስታውሰዋል፡፡ የማይኾን ጸጸት እንዳንጸጸት በሰዓቱ እና በጊዜው ንስሃ እንግባ ነው ያሉት፡፡ ይሁዳ ልቡ የነበረው ከገንዘብ ጋር ነበርና ሲያንገላቱት፣ ሲያዳፉት፣ መከራዎች ሲበዙበት ተጸጸተ፤ ጌታውን ያሸጠውን ገንዘቡንም በተነ፤ የዓለም ነገር ሁሉ ከንቱ እንደኾነ ተመለከተ፤ ጸጸቱ ግን የማይጠቅም፣ ንስሃውም ውኃ የማያነሳ ነበር ይላሉ፡፡

ከፍ ከፍ ያደረገውን አሳልፎ ሰጠው፣ ስጋዊ ምኞቱ ለክብር ሳያበቃው ቀረ፣ ንጹሕ ደም ያስፈሰስኩ፣ ጻድቅ ሰው ያስገደልኩ ነኝ አለ፣ ጸጸቱ ግን ጊዜ ካለፈ በኋላ ነበር፡፡ ራሳቸውን የማያድኑ፣ ለራሳቸው ማየት የተሳናቸው፣ የሚናገሩትን የማይሠሩ፣ የማያደርጉ ብዙዎችን በማያውቁት አሳሳቷቸው፤ እናም በጌታቸው ላይ፤ በመድኃኒታቸው ላይ ሆ! ብለው ተነሱ፡፡ ንጹህ የኾነውን ገደሉ፡፡ ዛሬም እንደዚያ ዘመን ኾነናል፤ ሆ! ብሎ የሚነሳው በዝቷል፤ ሕዝብን የሚያደናግረው ብዙ ነው ብለዋል፡፡

ብጽዕነታቸው በይሁዳ አሳልፎ ሰጭነት፣ በጸሐፍት ፈሪሳውያን ጩኸት እና በሕዝቡ ተባባሪነት የማይገረፍ ተገረፈ፣ የማይንገላታ ተንገላታ፣ የማይሰቃይ ተሰቃየ፣ የማይሞትም እነኾ ሞተ፣ እርሱ ግን በሞቱ ሞትን ያጠፋ ዘንድ ነው፡፡ የሌላው ሞት ግን ትርጉም የለውም፤ ተናበን በሃይማኖት ጸንተን እምንናገረውን አውቀን እንድንኖር ከይሁዳ እንማራለን ነው ያሉት፡፡

ወገኖቼ እንማርና እናስተምር፣ ወንጀልን እንጸየፈው፣ እንጥላው፣ ወንጀልን ተጸይፈን ወንጌልን እንውደደው፣ በወንጌል እንኑር፣ ወንጌል ሕጓም ስርዓቷም ያማረች ናት፤ ወንጌላዊ መኾን መልካም ነው፣ ወንጀለኛ መኾን ግን ሐጥያት ነው ብለዋል፡፡ እህትና ወንድም፣ እናትና አባትን አጎሳቁሎ ገንዘብ መውሰድ ለምንም አይጠቅም፣ ከእግዚአብሔር ጋር ያጣላል ነው ያሉት፡፡

ትናንት በክርስቶስ ላይ በሀሰት እንደመሰከሩበት ሁሉ ዛሬም ክርስቶስን በሚመስሉ ላይ በሃሰት የሚመሰክሩ፣ አሳልፈው የሚሰጡ ሞልተዋል፡፡ በሃሰት ወንጀል መፈጸም፣ በሃሰት መመስከር ክርስቶስን ከሸጠው ይሁዳ ጋር አለመለየት ነው ብለዋል፡፡

ዛሬ ለእኛ ድኅነት ነው፣ ለእኛ ክብር ነው፣ ለእኛ ልጅነት ነው፣ ለኛ ነጻነት ነው፣ አባቶቻችን የዛሬዋን ቀን ሲጠባበቋት ኖረዋል፤ በዚህች እለት የሚጠቅም ጸጸት የተጸጹት ድነዋል፤ የሚገባ ጸጸት የተጸጸተ ገነት ገብቷል፤ የመንግሥቱ ወራሽ እንዲኾን የሚገባውን ጸጸት እንጸጸት፣ በሰዓቱ ንስሃ እንግባ ነው ያሉት፡፡

በሰዓቱ ንስሃ ከገባን እግዚአብሔር በምህረቱ ይጎበኘናል፤ ሰላሙንም ያበዛልናል፤ ሰላም ትልቅ ዋጋ አለው፤ ንስሃ ለመግባት ሰላማዊ መኾን ያስፈልጋል፤ ንስሃ ለመግባት የፍቅር ሰው መኾን ያስፈልጋል፤ ንስሃ ለመግባት ከክፉ ነገር መራቅ ያስፈልጋል፤ ንስሃ ለመግባት ንጹሕ ልብ ያስፈልጋል፤ ቂም በቀል የቋጠረ ልብ ይዞ ንስሃ መግባት አይቻልም፤ ከእግዚአብሔርም ጋር መገናኘት አይቻልም ብለዋል፡፡ እውነት ስንናገር፣ በእውነት ስንኖር፣ ለወገን ስንራራ የዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ይኾናል፤ ሰላሙንም ያበዛልናል ይላሉ፡፡

በዓሉን ስናከብር ከማንኛውም ወገን ጋር በመጠያየቅ፣ በመከባበር፣ በመንከባከብ ይሁን፣ የጋራ ሀገር አለን፣ የጋራ ሀገራችን ላይ የጋራ የኾነ ሕዝብ ኾነን በሰላም ከየትኛውም ሃይማኖት ተከታይ ጋር አብሮ መኖርን ገንዘብ እናደርግ ብለዋል፡፡ ዛሬ ዛሬ ሰይጣን በእምነትም ሊያዋጋን ይፈልጋል፤ ግራ ሊያጋባን ይፈልጋል፤ በእምነትም ጥላቻ ፈጥሮ እርስ በእርስ እንድንጠፋፋም ለማድረግ እየሞከረ ነው ብለዋል፡፡ በፍቅር፣ በሰላም ስንኖር የጋራ ኖሮ እንኖራለን፣ የጋራ ሀገራችንን ከፍ ከፍ ማድረግ እንችላለን ነው ያሉት ብጹዕነታቸው፡፡

©አሚኮ