የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአዲስ አበባ ከተማ የሚካሔደውን የኮሪደር ልማት ተከትሎ በርካታ ሥራዎችን በማከናወን ላይ ትገኛለች።

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከሚካሔደው የኮሪደር ልማት ጋር በተያያዘ ንብረትነታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሆኑ ቤቶችና ሕንጻዎች በአራት ኪሎና በፒያሳ አካባቢ እንዲፈርሱ መደረጋቸው ይታወቃል።

ቤተ ክርስቲያንም በከተማ አስተዳደሩ የሚካሔደው የልማት ሥራ የአገር ልማት መሆኑን በመገንዘብ ሁኔታዎችን በቅርበት የሚከታተል ኮሚቴ በመሰየም ብስለትና ትዕግስት በተሞላበት አኳኋን ከመከታተል ባለፈ ቋሚ ሲኖዶስ በወሰነው ውሳኔ መሠረት በብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣
የባሕር ዳርና የሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሚመራ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና የሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች የሚገኙበት የቤተ ክርስቲያናችን ልዑክ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አቤቤና ከሥራ ባልደረቦቻቸው ጋር ተወያይቷል።

በውይይቱም ቤተ ክርስቲያን በከተማ አስተዳደሩ የሚካሔደው የልማት ሥራ የአገር ልማት መሆኑን ጠንቅቃ እንደምትገነዘብ፣ ለውጤታማነቱም የበኩልዋን አስተዋጽኦ እንደምታበረክት፣ ከዚሁ ጎን ለጎንም የቤተ ክርስቲያን ይዞታዎችና መብቶች በሚከበሩበት፣ ቀደም ብለው ለቤተክርስቲያናችን እንዲመለሱ በተደረጉ ይዞታዎች፣በመከኑ ካርታዎችና በሌሎችም ጉዳዮች ጭምር ግልጽና ውጤታማ ውይይቶች ተደርገዋል።

ከከተማ አስተዳደሩ ከንቲባና ከሥራ ኃላፊዎቹ ጋር የተደረገውን ውይይትና ውጤቱን መሠረት በማድረግም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት አስተዳደር ጉባኤ የቀረበለትን ሪፖርት መነሻ በማድረግ ውሳኔና ምክረ ሀሳብ ለቋሚ ሲኖዶስ አቅርቧል።

ቋሚ ሲኖዶስ በተለይም ጽርሐ ምኒልክ ሕንጻን ወይም በተለምዶ መሐሙድ ሕንጻ በመባል የሚታወቀውን ሕንጻን በተመለከተ የከተማ አስተዳደሩ ሕንጻው እንዳይፈርስ ለማድረግ ያደረገውን ጥረት ቤተክርስቲያን እያደነቀች ሕንጻው መፍረሱ ግድ በመሆኑ ምክንያት ሕንጻው ከፈረሰበት ቦታ ብዙም ሳይርቅ በመንገድ ልማቱ ምክንያት ከሚወሰደው ይዞታ አጠገብ ባለው ቦታ ላይ የሕንጻውን ታሪካዊነትና ጥንታዊነትን መሠረት ባደረገ አግባብ የአካባቢውን የመኪና ማቆሚያ ችግር ሊፈታ የሚችል የመኪና ማቆሚያ አገልግሎት መስጫን ባካተተ መልኩ በራሱ ወጪ በአንድ ዓመት ውስጥ ገንብቶ ለማስረከብ የገባውን ቃል በመቀበልና በማጽደቅ ለከተማ አስተዳደሩ በደብዳቤ እንዲገለጽለት አድርጓል።

የከተማ አስተዳደሩም የጽርሐ ምኒሊክ ሕንጻ ግንባታ ጉዳይንም ሆነ ሌሎች ቤተ ክርስቲያን ያቀረበቻቸውን የይዞታ ይገባኛል፣የምትክ ቦታና የካሳ ክፍያ ሁኔታዎችን በተመለከተ የሰጠውን ውሳኔ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት በደብዳቤ አረጋግጦ አሳውቋል።

ከዚህ በተጨማሪ ክብርት ከንቲባዋ ቀደም ባሉ ጊዜያት ለቤተክርስቲያን የተመለሱ፣ ካርታ ወጥቶላቸው የነበሩና በተለያዩ ምክንያቶች ካርታቸው እንዲመክኑ የተደረጉ ይዞታዎችና መሰል ጥያቄዎችን በአግባቡ በመመርመር የማያዳግም ምላሽ እንዲሰጥ ለሚመለከተው አካል ግልጽ መመሪያ ሰጥተዋል። ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም በከተማ አስተዳደሩ የሚከናወነውን የልማት ሥራ ተከትሎ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በመነጋገር፣ በመመካከርና በመወያየት መፍትሔ በሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ መፍትሔ በማስቀመጥ በስምምነት እየሠራች መሆኑን ተከትሎ የከተማ አስተዳደሩ ቤተ ክርስቲያን የምታነሳቸውን ጥያቄዎችና ሃሳቦች ሁሉ በቅንነት በመመልከት እየሰጠ ላለው ዘላቂ መፍትሔ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ልባዊ ምስጋናዋን ታቀርባለች።

በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአዲስ አበባ ከተማ የሚካሔደውን የኮሪደር ልማትን መሰረት በማድረግ ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን ዋና ዋና ተግባራት ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በመወያየትና በመስማማት አከናውናለች እነርሱም፦

፩ኛ. በመንገድ ማስፋፋትና በአደባባይ ሥራ ምክንያት በፈረሱ የቤተ ክርስቲያናችን ቦታዎች ምትክ የከተማ አስተዳደሩ በሚሰጠን ካሳና ምትክ ቦታዎች ላይ ቤተ ክርስቲያናችን የልማት ሥራዎችን እንደምታከናውን፤

፪ኛ. በመንገድ ኮሪደሩ ዳርቻ አካባቢ የሚገኙ የቤተክርስቲያናችን ሕንጻዎችን በተመለከተ ሕንጻዎቻችን የከተማውን ውበት በሚመጥኑና የከተማ አስተዳደሩ ለእድሳት ያወጣውን መስፈርት መሠረት ባደረገ አግባብ ባሉበት ሆኔታ እንደሚታደሱ እንደምታደርግና ይኸው የእድሳት ሥራ መከናወን መጀመሩ፤

፫ኛ. የቤተ ክርስቲያናችንን ቤት ተከራይተው የሚኖሩ ወገኖች የሚኖሩበት ቤትና ሕንጻ በሚፈርስበት ጊዜ እንደ ማንኛውም የልማት ተነሺ ሁሉ ኮንዶሚኒየምና የቀበሌ ቤት እንደ ፍላጎታቸው እንዲሰጣቸው የሚደረግ መሆኑን ከስምምነት ላይ መደረሱና ይህንንም ቤተክርስቲያናችን በደስታ እንደምትቀበለው፤

፬ኛ. የቤተ ክርስቲያናችንን የንግድ ቤት ተከራይተው የንግድ ሥራቸውን ያከናውኑ የነበሩና ከልማቱ ጋር ተያይዞ ንግድ ቤታቸው የፈረሰባቸው ነጋዴዎች ለሌሎች ነጋዴዎች በተዘጋጀው ቦታ ላይ ምትክ ቦታ እንዲሰጣቸው እንዲደረግ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር ስምምነት ላይ መደረሱና ዝርዝር ሥራውም በሒደት ላይ የሚገኝ መሆኑ፤

፭ኛ. በፒያሳና በሌሎች አካባቢ የነበሩ የቤተ ክርስቲያናችን በርካታ የጭቃ ቤቶች የልማቱን ሥራ ተከትሎ እንዲፈርሱ የተደረጉ መሆኑን ተከትሎ ከገቢ አንጻር ለጊዜው የተጎዳን ቢመስልም በተለያዩ ቦታዎች ተቆራርጠው የነበሩ ይዞታዎች በዚያው በፈረሱበት አካባቢ ሰብሰብ ብለው በአንድ ቦታ በርከት ያሉ ካሬ ሜትር ቦታዎች እንዲሰጠን ስለሚደረግና በሚሰጠን ቦታ ላይ ዘመኑን የዋጁ በገቢም የቤተ ክርስቲያናችንን የገቢ አቅም የሚያሳድጉ ሕንጻዎችን የምንገነባበት ሁኔታ የሚፈጠር መሆኑ የከተማችንን የኮሪደር ልማት ተከትሎ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በመሆን ካከናወናቸው ዋናዋና ሥራዎች መካከል ጥቂቶቹ ናቸው።

ከፍ ሲል ከተራ ቁጥር ፩ – ፭ የተጠቀሱና በቀጣይ የልማት ሥራውን ተከትሎ የሚከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትን የሚከታተሉ፣ የቤተክርስቲያናችንን መብት በአግባቡ የሚያስከብሩና የሚያስፈጽሙ ዐቢይና ንዑሳን ኮሚቴዎች በጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደር ጉባኤ ተሰይመው ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን እየገለጽን መላው የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን የልማት ሥራውን በተመለከተ የሚከናወኑ ዝርዝር ተግባራት በየጊዜው የሚገለጹ ስለሆነ አፈጻጸማቸውን በተመለከተ ከቅድስት ቤተክርስቲያናችሁ ጎን በጽናት በመቆም መንፈሳዊ ግዴታችሁን እንድትወጡ መልዕክታችንን እናስተላልፋለን።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት
ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
ሚያዚያ ፲፱ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም.
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ