የመቱ ፈለገ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ የመጀመሪያውን ዙር እጩ መምህራን በደማቅ ሥነ ሥርዓት አስመረቀ
ሐምሌ ፲፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም.| ሕዝብ ግንኙነት መምሪያከተቋቋመ ገና ሦስት ዓመታትን ያስቆጠረው የመቱ ፈለገ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ፤ ከተለያዩ አህጉረ ስብከቶች ተቀብሎ ሲያሰለጥናቸው እና ሲያስተምራቸው የቆያቸውን ፲፰ እጩ መምህራን ደቀ መዛሙርት በሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም. በደመቀ ሥነ ሥርዓት አስመርቋል።
ይህ ታሪካዊ የምረቃ በዓል የመቱ ፈለገ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ፣ ፕሬዚዳንትና የኢሉ አባ ቦር እና የምዕራብ ወለጋ አህጉረ ስብከቶች ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ዶ/ር)፣ የቡኖ በደሌ እና የቄለም ወለጋ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ትጉሃን ብርሃኑ መንገሻ፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የተመራቂ ቤተሰቦች በተገኙበት ተካሂዷል።
በመርሐ ግብሩ ላይ በረከታቸው ይደርብንና ታላቁና ጸሎተኛው የቀድሞው የሀገረስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ኮሌጁ በአፋጣኝ እንዲከፈት መመሪያ በመስጠትና ጥብቅ ክትትል በማድረግ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት መንሳዊ ኮሌጁ እንዲመሠረት ያደረጉት ጥረትና የነበራቸው አባታዊና መምህራዊ ምክር በታላቅ አክብሮት ተዘክሯል።
የኮሌጁ የበላይ ኃላፊና ፕሬዚዳንት ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ዶ/ር) ለአዲሶቹ እጩ መምህራን ባስተላለፉት አባታዊ አደራና ቃለ ቡራኬ፤ “ዛሬ የተሰበሰብነው ትምህርት ያበቃበትን ቀን ለማክበር ወይም የዲፕሎማና የዲግሪ ወረቀት ለመስጠት ሳይሆን፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ቀዳሚ ዓላማና የወንጌል አገልግሎት አደራ ለመቀበል ነው” ሲሉ ገልጸዋል።
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎችም ተመራቂዎቹ በሄዱበት ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በታማኝነትና በቅንነት እንዲያገለግሉ፣ የተማሩትን በሥራ እንዲገልጡና የተዘጉትን አብያተ ክርስቲያናት እንዲያስከፍቱ ጥብቅ አደራ አስተላልፈዋል።
ተመራቂ ደቀ መዛሙርቱም በበኩላቸው ባስተላለፉት የጋራ መልእክት፤ በኮሌጁ የቆይታ ጊዜያቸው በመንፈሳዊ ዕውቀትና በሥነ ምግባር ታንጸው፣ በሚያምኑትና በማያምኑት ዘንድ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት በመሆን በሕይወታቸው ተነባቢ መጽሐፍ ሆነው መኖርንና ሐዋርያዊ ግዴታቸውን መወጣትን እንደተረዱ ገልጸዋል። አያይዘውም “ከዚህ በኋላ የፍጥረት ሁሉ መዳኛ የሆነውን ወንጌል ይዘን የምናስተምርበት፣ ጨለማውን ዓለም የምናበራበት፣ የታመመውን የምናክምበት እንዲሁም በቃልም ሆነ በሥራ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ የምንፈጽምበት ጊዜ ነው፤ ትምህርት አላለቀም፣ በማስተማር ውስጥ መማር በመማር ውስጥ ማስተማር ይቀጥላል፤ በቀጣይ ሕይወታችን በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ፣ እንደ እባብ ልባም እንደ እርግብም የዋህ ሆነን አገልግሎታችንን እንፈጽማለን” ሲሉ ቃላቸውን አድሰዋል።
በዕለቱ መርሐ ግብር ላይ በኮሌጁ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀችው “መጽሔተ ጥበብ ቁጥር ፩” የተሰኘችው መጽሔት ተመርቃ ለአገልግሎት የበቃች ሲሆን፤ በኮሌጁ የሚገኙ የአስተዳደር፣ የመምህራንና የድጋፍ ሰጪ አካላት ደቀ መዛሙርቱ በውጤታማነት እንዲመረቁ ላደረጉት ታላቅ አስተዋጽኦ ዕውቅና ተሰጥቷል። በሥነ ሥርዓቱ ማጠቃለያ ላይም ለኮሌጁ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት፣ ለደቀ መዛሙርቱና በከፍተኛ ውጤት ለተመረቁ ተመራቂዎች የምስክር ወረቀትና የክብር ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ዘገባው፦ የኢሉ አባ ቦር ሀገረ ስብከት ሚዲያ