የማጣራት ሥራው መሰረታዊ ዓላማ ግለሰቦችን ማሳደድ ሳይሆን ተቋምን መታደግ ነው።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚስተዋለው የመልካም አስተዳደር ችግር ከዚህ በላይ ሥር ሳይሰድና ለቅድስት ቤተክርስቲያን ሕልውና አደጋ በመሆን ጉዳት ከማድረሱ በፊት ችግሩን ከመሰረቱ በማጥናት ከመፍትሔ ሐሳብ ጭምር የሚያቀርብ ሰባት አባላት ያሉት ኮሚቴ በማቋቋም ወደ ሥራ እንዲገባ አድርጓል።

ችግሩን ለማጥናት የሚደረገው ጥረትም ችግሩ የተፈጠረበት፣ ያደገበትና የጎለበተበት ቦታ ላይ መሆን እንዳለበት በሚገባ የሚያምነው ጠቅላይ ቤተክህነቱ አምስት መሰረታዊ ነጥቦችን በመለየት ማለትም፦

1. በሀገረ ስብከቱ የበጀት ዓመቱ ዓመታዊ እቅድና ሪፖርት ከገንዘብ ኃይል ቅጽ ጋር
2. የአስተዳዳሪዎች ዝውውር ዶክሜንት
3. የሰው ኃይል ቅጥር ፣ዝውውር፣እድገትና ስንብት
4. የፋይናንስ ሪፖርት የሀገረ ስብከትና የክፍለ ከተሞች
5. ከዚሁ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ሰነዶችን ማግኘት የሚሉት ትኩረት ተደርጎባቸው እንዲጣሩ በአስተዳደር ጉባኤው በኩል ወስኗል።

ይሁን እንጂ ይህ የማጣራት ሥራው ትኩረት የሆነው
ባለ አምስት ነጥብ የትኩረት አቅጣጫ በቀጥታ የሚመለከታቸው የሀገረ ስብከቱ ባለሦልጣናት የጥናት አቅጣጫው ወደ አድባራትና ገዳማት የተነጣጠረና በአጥቢያ የሚገኙ የሥራ ኃላፊዎችን የግል የባንክ ሒሳባቸውን እስከ ማስመርመር የሚደርስ አደገኛ አካሔድ በጠቅላይ ቤተክህነቱ እየተሄደ በማስመሰል ደጋፊ ለማሰባሰብና አቅጣጫ ለማስቀየር በመጣር ላይ እንደሚገኙ የተለያዩ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ይህን ፍፁም ሐሰትና መሰረተ ቢስ አሉባልታ በመንዛት የማጣራት ሂደቱን ለማወክ የሚጥሩ ወገኖች የሚሉትን የሚያምኑ አካላትም የማንም ሰው የሒሳብ ደብተር ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ ውጭ ሊመረመር እንደማይችል ከመረዳት ጋር ጠቅላይ ቤተክህነቱ የግለሰቦችን የባንክ ሒሳብ የመመርመርና የማስመርመር ሥራ የመስራት ሃሳብ የሌለው መሆኑን እየገለጸ በዚህ አይነቱ አሰራር ዘላቂ የመልካም አስተዳደርና የሙስና ችግር ይፈታል የሚል የየዋሆች ስሌት ውስጥ የሚገባ እንዳልሆነ ለመግለጽ ይወዳል።

ስለሆነም አጣሪ ኮሚቴው ትኩረት ሰጥቶ የማጣራት ሥራውን የሚሰራው በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተክህነት አሰራርና አሰራሩን ተከትሎ በተፈጠሩት የመልካም አስተዳደር ችግሮች ላይ ብቻ መሆኑንም በአጽንኦት ይገልጻል።

ይሁን እንጂ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችን፣ ጸሐፊዎችን፣ሒሳብ ሹሞችን፣ቁጥጥሮችንና ገንዘብ ቤቶችን በተለየ መልኩ የባንክ ሒሳባቸው እንዲመረመር በማድረግ ለመወንጀል እየተንቀሳቀሰ ነው የሚባለው ጉዳይ ፍጹም መሰረተ ቢስና የማጣራት ሂደቱን በማጠልሸት ማጣራቱ ተቃውሞ እንዲገጥመው በማድረግ በውጤቱ ተጠያቂ ሊሆኑ የሚችሉ ሰዎችን ለመከላከል የተፈበረከ ወሬ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን።

በመጨረሻም ጠቅላይ ቤተክህነቱ ቤተክርስቲያን የቀደመ ክብሯን ለማስመለስ፣ከዘረኝነት፣ከሙስናና ከብልሹ አሰራር ጸድታ ለዓለሙ ተቋማት የተግባር ማሳያና ማስተማሪያ መሆን ትችል ዘንድ ብፁእ ወቅዱስ ፓትርያርካችን የሰጡንን አቅጣጫ መሰረት በማድረግ በፍጹም ጽናትና ትጋት የተጣለበትን ኃላፊነት በመወጣት ብልሹ አሰራሩ ያስለቀሰና ያሳዘናቸውን ካህናት፣የካህናት ቤተሰቦች፣ ምዕመናንና ምዕመናትን የሚያስደስት፣እንባቸውን የሚያብስና ፍጹም የሚመኩበትን ተቋም ለመፍጠር እንደምንሰራና ለዚህም እግዚአብሔር አምላክ እንደሚረዳን እምነታችን የጸና ነው።

መስከረም ፳፬ ቀን ፳፻ ፲ወ፯ ዓ.ም
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ