ቅዱስ ሲኖዶስ በልማትና ዘመናዊ አሠራር ላይ ያተኮሩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ለ6 ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን የ2018 ዓ.ም የርክበ ካህናት ጉባኤውን አጠናቀቀ
ግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን መደበኛ የምልኣተ ጉባኤ ስብሰባውን በ22 አጀንዳዎች ላይ በመወያየትና ለቤተክርስቲያናችን ቀጣይ ጉዞ ወሳኝ የሆኑ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ማጠናቀቁን የቅዱስ ሲኖዶስ የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ፣ ረዳት ፕሮፌሰር ቀሲስ ዳንኤል ሰይፈ-ሚካኤል ለEOTCTV በሰጡት ዕለታዊ መግለጫ አስታውዋል።
ኃላፊው በሰጡት ማብራርያ፣ ጉባኤው በተለይም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት እየተከናወኑ ያሉትን የልማት፣ የዘመናዊ አሠራር እና የቴክኖሎጂ ሽግግር ሥራዎች በዝርዝር ከገመገመ በኋላ ከፍተኛ አድናቆቱን መግለጹን ተናግረዋል።
በጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሆኑት በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ አመራር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት በምስል እና ድምፅ የተደገፈ ሰፊ ሪፖርት ለምልአተ ጉባኤው መቅረቡን የጠቀሱት ረዳት ፕሮፌሰር ቀሲስ ዳንኤል፣ ሪፖርቱ “ቤተክርስቲያናችን ለዘመናት ያላትን ታሪካዊ አስተዋጽኦ እያስጠበቀች፣ ከዘመኑ ጋር የሚራመድ አሠራርን ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ርብርብ በጉልህ አሳይቷል” ሲሉ ገልጸዋል።
በሪፖርቱ ከቀረቡት ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል በመንበረ ፓትርያርክ ግቢ እና “በኮሪደር ልማት” በተገኙ መሬቶች ላይ የተጀመሩ የግንባታ ፕሮጀክቶች እንዲሁም ግቢውን የማስዋብና ምቹ የማድረግ ሥራዎች እንደሚገኙበት የገለጹ ሲሆን ረዳት ፕሮፌሰር ቀሲስ ዳንኤል እንዳብራሩት፣ “ምልአተ ጉባኤው በአጭር ጊዜ ውስጥ የተገኙትን እነዚህን ተጨባጭ ውጤቶች በማየት ሥራዎቹን በከፍተኛ አድናቆት ምልዓተ ጉባኤው ተቀብሏቸዋል።” ብለዋል።
ከዚህም በተጨማሪ፣ ለዘመናት ተቀምጠው የነበሩ ታሪካዊ የሰነድ መዛግብትን በዲጂታል ቴክኖሎጂ የማስቀመጥ ሥራ መጀመሩና
አስተዳደራዊ መዋቅሩን በማዘመን የአገልግሎት አሰጣጥን ቀልጣፋ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑ ተብራርቷል።
ለረጅም ጊዜ በመጋዘን የቆዩ ቅዱሳት መጻሕፍትን በማሳተም ለምዕመናን ተደራሽ የማድረግ ሥራም በስፋት መከናወኑን ኃላፊው አክለው ገልጸዋል።
ብፁዓን አባቶች በቀረበው ሪፖርት ላይ ሰፊ ውይይት ካደረጉ በኋላ፣ “የተጀመሩት ስራዎች የቤተክርስቲያኒቱን ክብርና ልዕልና
የሚያስጠብቁ፣ ተቋማዊ ህልውናዋን የሚያጠናክሩና ለምዕመናን የሚሰጠውን አገልግሎት የሚያዘምኑ ናቸው” በማለት ሙሉ ድጋፋቸውን መግለጻቸውን ረዳት ፕሮፌሰር ቀሲስ ዳንኤል አስረድተዋል።
በዚህም መሠረት ምልኣተ ጉባኤው የተጀመሩት የልማትና የማዘመን ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ከመወሰኑም በላይ፣ ሌሎች አባቶችም በየአህጉረ ስብከታቸው ተመሳሳይ ማሻሻያዎችን እንዲተገብሩ ጥሪ ማቅረቡን ገልጸዋል።
ጉባኤው ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጀመሩትን ሥራ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ሙሉ ድጋፍ እንደሚሰጥም አረጋግጧል ተብለዋል ።
ጉባኤው በሌሎች አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ ከመከረ በኋላም፣ በቀጣዮቹ ስድስት ወራት በቋሚ ሲኖዶስ ውስጥ የሚያገለግሉ ብፁዓን አባቶችን ምርጫ ማካሄዱን የኮሙኒኬሽን ኃላፊው ተናግረዋል።
በመጨረሻም፣ “ለቀናት በተለያዩ አገራዊና ሃይማኖታዊ አጀንዳዎች ላይ ሲመክር የቆየው የቅዱስ ሲኖዶሱ ምልኣተ ጉባኤ፣ በነገው
ዕለት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሚሰጡት ቃለ ምዕዳንና አባታዊ ቡራኬ በይፋ ይጠናቀቃል” ሲሉ ረዳት ፕሮፌሰር ቀሲስ ዳንኤል ሰይፈ-ሚካኤል ማብራርያቸውን አጠቃለዋል።©EOTc tv