የራሺያ ቤተክርስቲያን ልኡካን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጉብኝት አደረጉ።
ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም
ልኡካኑ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት እና ከብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ የራያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ከብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጋር ሰፊ ውይይት አድርገዋል ።
ከልኡካኑ መካከል የሞስኮ ፓትርያርክ የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መምሪያ ሊቀመንበር የሆኑት የቮሎኮላምስክ ሜትሮፖሊታን አንቶኒ የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጋር ያላትን መንፈሳዊ አና ታሪካዊ ግንኙነት አንስተው በቀጣይም የጋራ ሥራዎች እንዳሏቸው ገልጸዋል ።
አያይዘውም በሩሲያ የቲዎሎጂ አካዳሚዎች ከፍተኛ ትምህርታቸውን ለመከታተል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች ወደ ራሺያ ማቅናታቸው በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር መቻሉን ገልጸዋል።
ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፣የደቡብ ኦሞ እና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በበኩላቸው የራሺያ ቤተክርስቲያን እና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያለፋበት መንገድ ተመሣሣይነት ያለው መሆኑን አንስተው በበርካታ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት መወያየታቸውን ተናግረዋል ።©Eotc tv