ለብፁዕ አቡነ ኤፍሬም በደምቢ ዶሎ ከተማ ደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው
ሰኔ 6/10/2018
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን፣ የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን በማገልገል ላይ የሚገኙት ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፣በግንቦት 2018 ዓ በተካሔደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የቄለም ወለጋን ሀገረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ መወሰኑ ይታወቃል።
በዚህም መሰረት ብፁዕነታቸው ይህንኑ ኃላፊነት ለመረከብ ሰኔ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ወደ ደቢዶሎ ከተማ ሲያቀኑ፣በከተሣው ነዋሪዎች ምዕመናንና ምዕመናት ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል ።
ብፁዕነታቸው ወደ ቄለም ወለጋ ሀገረ ስብከት በተጓዙበት ጊዜ
ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ዶ/ር)፦ የኢሉ አባቦርና የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም የመቱ ፈለገ ሕይወት መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ፣ መላከ ምሕረት ቆሞስ አባ ገብረ እግዚአብሔር፦ የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ።በኩረ ትጉህ ቀሲስ ምትኩ ከንቲባ፦ የጠቅላይ ቤተክህነት የቅርስ ጥበቃ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ኃላፊ ሊቀ ልሳናት ቀሲስ በዳሳ ቶላ፦ የጠቅላይ ቤተክህነት የሊቃውንት ጉባኤና የኮዬ ፈጬ ክፍላተ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ላዕከ ወንጌል ኃይሉ አየለ፦ የጠቅላይ ቤተክህነት ሕዝብ ግንኙነት ምክትል መምሪያ ኃላፊ፣ መጋቤ ብሉይ ሣህለ ማርያም፦ የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ።
መላከ ሄዶም ቀሲስ ግርማ ኢማና፦ የደቢዶሎ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ተገኝተዋል ።
ብፁዕነታቸው ደቢዶሎ ደብረ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን እንደደረሱ፤ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የማህበራት ተወካዮች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፣ የነገረ መለኮት ምሩቃን እና ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣናት ደማቅ አቀባበል ያደረጉላቸው ሲሆን በስነ-ስርዓቱ ላይም የደብረ ፀሐይ ደንቢዶሎ መድኃኔዓለም ሰንበት ተማሪዎችና የአዲስ አበባና የሸገር ሀገረ ስብከት ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ያሬዳዊ ዜማ አቅርበዋል።
በዚሁ መርሐ ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ዶ/ር) ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት አንድነት ለቤተክርስቲያን ሁለንተናዊ ልማት ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ በሁሉም ቋንቋ በቀረበው አገልግሎት መደሰታቸውንና ይህን የመሰለ ሁሉን አቀፍ አገልግሎት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ገልጸዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ለተደረገላቸው ደማቅ አቀባበል ምስጋ አቅርበው ስለ ወለጋ ክልል ሰላም የሚነገረውና በተጨባጭ ያዩት እጅግ የተለየ መሆኑን በመጠቆም የሕዝቡ አንድነትና ፍቅር ልባቸውን እንደነካው ከገለጹ በኋላ ይህ መርሐ ግብር በሰላም እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉት ሁሉ ምስጋናቸውን በማቅረብ ቃለ ምዕዳንና ቃለ በረከት አስተላልፈው የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል።
ዘጋቢ የላዕከ ወንጌል ኃይሉ አየለ ነው፤