የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሁለተኛውን ዙር የነገረ መለኮት ደቀ መዛሙርት በታላቅ ድምቀት አስመረቀ።
ሰኔ ፳ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ምበብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ሣልሳይ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተመሠረተው የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ ለሦስት ተከታታይ ዓመታት በነገረ መለኮት ትምህርት ዘርፍ ሲያስተምራቸው የነበሩ የሁለተኛ ዙር ደቀ መዛሙርት በዛሬው ዕለት በታላቅ ድምቀት አስመርቋል።
የሀገርና የቅድስት ቤተክርስቲያን ተተኪ አገልጋዮችንና ምሁራንን በማፍራት ላይ የሚገኘው የዚህ ኮሌጅ ታሪካዊ የምረቃ ሥነ-ሥርዓት በከፍተኛ መንፈሳዊ ድምቀትና ሥርዓት የተከናወነ ሲሆን፤ በበዓሉ ላይ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ሣልሳይ (የኮሌጁ መሥራችና የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ)፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ (የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የታቦር ፍኖተ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ) እና ብፁዕ አቡነ መቃሪዎስ (የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ) ተገኝተዋል። በተጨማሪም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ከፍተኛ ልዑካን እና የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አመራር አካላት፣ ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት አካላት በክብር እንግድነት በመገኘት የሥነ-ሥርዓቱ ተካፋይ ሆነዋል።
በዛሬው የምረቃ መርሐ ግብር ላይ መደበኛ የነገረ መለኮት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ 19 ደቀ መዛሙርት እንዲሁም ለአንድ ወር ተከታታይ የአጭር ጊዜ የአቅም ማጠናከሪያ ሥልጠና ሲከታተሉ የነበሩ 30 ካህናትና አገልጋዮች በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እጅ የዲፕሎማና የሰርተፍኬት የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል። ይህ የምረቃ በዓል ኮሌጁ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ዘርፍ እያበረከተ ያለውን ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያሳይ ሲሆን፤ ተመራቂዎቹም ላለፉት ሦስት ዓመታት የቀሰሙትን ዕውቀት መሠረት በማድረግ ኦርቶዶክሳዊነትን ለማስፋፋትና ቅድስት ቤተክርስቲያንን በዕውቀት ለማገልገል የሚሰማሩበት ልዩ ምዕራፍ መሆኑ ተገልጿል።
ኮሌጁ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ዘርፍ እያበረከተ ያለው ይህ ከፍተኛ አስተዋጽኦ፣ በሀገረ ስብከቱም ሆነ በቤተክርስቲያኗ ውስጥ የሚታየውን የአገልጋይ እጥረት ለመቅረፍ ትልቅ ተስፋ የሰነቀ መሆኑም በዕለቱ ተነግሯል።
በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ሰፋ ያለና ጥልቅ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል።
ለአጠቃላዩ ተመራቂዎች መንፈሳዊ መመሪያና አባታዊ መልዕክት ያስተላለፉት ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ ሣልሳይ፤ መነሻቸውን “ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ ኑሩ” (ፊል 1፥27) በሚለው የቅዱስ መጽሐፍ ቃል ላይ በማድረግ ይህ ዕለት የትምህርታቸው ማብቂያ ሳይሆን የአገልግሎታቸው ጅማሬ መሆኑን ተመራቂዎቹ አውቀው ሊያስቡበት እንደሚገባ አሳስበዋል።
በጉባኤው ውስጥ የተማሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምዕመናንን የሚጠብቁበት ክንድ በመሆኑ፣ የተቀሰመው ዕውቀት ከአገልግሎት የተለየ እንዳይሆንና በትምህርት ደረጃ ብቻ ሳይቀረጽ በተግባር ላይ ሊውል እንደሚገባም መመሪያ ሰጥተዋል። ተመራቂዎቹ ለምዕመናን ምሳሌ በመሆን መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን በሓላፊነት ስሜትና በትጋት ሊወጡ እንደሚገባ የገለጹት ብፁዕነታቸው፣ የክህነት አገልግሎት ልዩ ክብር ያለው ቢሆንም ከሁሉ በላይ የመስዋዕትነትና የኃላፊነት ዋጋ መሆኑን፣ ያላችሁበት ዘመንም በብዙ ፈተናዎች የተከበበ መሆኑን በተለየ ሁኔታ መገንዘብና ማወቅ እንደሚገባ በጥብቅ አሳስበዋል። ታሪካዊው የምረቃ ሥነ-ሥርዓት በብፁዕ አቡነ መቃርዮስ ቃለ ምዕዳንና አባታዊ ቡራኬ ተጠናቋል። © ሣሌም የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሚዲያ