ስምከ ሕያው ዘኢመውት ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
አምስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚደንት፤ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም ምክር ቤት የክብር ፕሬዚደንትና የዓለም የሰላም አምባሳደር ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ከተለዩን እነሆ አሥራ አራት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡እነዚህ አሥራ አራት ዓመታት ውስጥ ቅዱስነታቸውንና ሥራዎቻቸውን የሚዘክሩ በተቋም ደረጃ የተጻፉም ሆነ ዝክረ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን በተመለከተ የተከናወነ ምንም ዓይነት ሥነ ሥርዓት አለመደረጉ ዘወትር የሚያስቆጭና በምክንያትነት የሚገለጽ አንዳች ነገር አለመኖሩ ደግሞ በእጅጉ የሚያሳዝን ነው፡፡ እዚህ ላይ በወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ አማካኝነት በየዓመቱ የሚደረገውን ዝክረ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን አለማድነቅና ምስጋና አለመቸር ትዝብት ላይ ይጥላልና ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነን በማመስገን ረጅም ዕድሜ ከሙሉ ጤንነት ጋር ስንመኝላቸው የቅዱስነታቸው በረከት እንዳይለያቸው ከመጸለይ ጋር ነው፡፡ እናም በዚህ ጽሑፍ ላይ ቅዱስነታቸውን እንደሚከተለው እንዘክራቸዋለን፡፡
ቅዱስነታቸው ከሐምሌ 5 ቀን 1986ዓ.ም. ጀምሮ ለ20 ዓመታት ቤተ ክርስቲያንን በርእሰ አበውነት ሲመሩ ከቆዩ በኋላ በ76 ዓመት ዕድሜያቸው ነሐሴ 10 ቀን 2004 ዓ.ም. ሐሙስ ከንጋቱ 11 ስዓት ላይ በደጃዝማች ባልቻ ሆስፒታል የሕክምና ርዳታ ሲደረግላቸው ከቆዩ በኋላ የዘመናት ባለቤት እግዚአብሔር የመደበላቸውን ጊዜ በታማኝነትና ይህ ቀረው በማይባል ስኬት አጠናቀው ከዚህዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡ ቅዱስነታቸው በጾመ ማርያም የመጀመሪያውን ሳምንት ሱባኤ በመንበረ ፓትርያርክቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ቀድሰው በማቊረብና በማስተማር መሰንበታቸውና የመጀመሪያው ሳምንት ሱባኤ በተጠናቀቀበት ወቅት፦ “አባቶች ሱባኤው ተጠናቋል” በማለት በወቅቱ አብረዋቸው ለነበሩ ብፁዓን አባቶችመግለጻቸውና አባቶችም፦ “ቅዱስ አባታችን ገና እኮ ሳምንት ይቀራል” ሲሏቸው “የእኔን አጠናቅቄአለሁ”
ማለታቸውን ብፁዓን አባቶች ያስታውሳሉ፡፡ እንዳሉትም በነጋታው ሆስፒታል ገብተው ለሦስት ቀናት ሕክምናቸውን ሲከታተሉ ከቆዩ በኋላ ነሐሴ 10 ቀን 2004 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም ድካም ማረፋቸውን በከፍተኛ ኃዘን በማስታወስ ቅዱስነታቸውን መዘከራችንን እንጀምር
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በ1928 ዓ.ም. በትግራይ ክፍለ ሀገር በአድዋ አውራጃ ተወለዱ፡፡ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በአቅራቢያቸው በሚገኘው የአባ ገሪማ ገዳም መንፈሳዊ ትምህርታቸውን በመጀመርበዚሁ ገዳም ከዲቁና እስከ ምንኩስና መዓርግ የደረሱ ሲሆን፤ በመቀጠል የቤተ ክርስቲያንን ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶች አጠናቀው ወደ አዲስ አበባ በመግባት በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ጨርሰዋል፡፡
በነበራቸው ትጋትና ልዩ የመማር ፍላጎት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ መልካም ፈቃድ ወደ አሜሪካ ለከፍተኛ ትምህርት ተልከው በሴንት ቭላዲሚ ርኦርቶዶክስ መንፈሳዊ ኮሌጅና በሌሎችም የትምህርት ተቋማት በመማር ተደራራቢ ዲግሪዎችን አግኝተዋል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በጵጵስና ጊዜያቸው በደርግ አገዛዝ ለ7 ዓመታት በእስር ቤት ቆይተዋል፡፡ ከዚያም ከእስር ቤት ከተፈቱ በኋላ ወደ አሜሪካ በመመለስ የጀመሩትን ትምህርት በመቀጠል በታላቁ በፕሪስቶን ዩኒቨርሲቲ ፒኤች.ዲ. ዲድግሪያቸውን ሠርተዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከሕፃንነት ዕድሜያቸው ጀምረው በገዳማዊ ሥርዓትና ሕግ ያደጉ፤ በክርስቶስ ወንጌል ምክንያት የታሠሩ፤ በአጠቃላይ እንደ ወርቅ ተፈትኖ ያለፈ ሕይወት የነበራቸውና በመንፈሳዊውም ሆነ በዓለማዊው ዕውቀት በጣምራ ችሎታዎች የተካኑ ዓለም አቀፍ አባት ነበሩ፡፡
ቅዱስነታቸው ረቡዕ ነሐሴ 9 ቀን 2004 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን የሱባዔውን ጸሎት ሲመሩ ከቆዩ በኋላ በተሰማቸው ሕመም ምክንያት ወደ ሆስፒታል እንደተወሰዱና ያለምንም ስቃይና ጻዕረ ሞት እንዳረፉ ይነገራል፡፡ ይህም ቅዱስነታቸው “እኔ የምፈልገው እንደ አባቶቼ በሰላም ማንቀላፋት ነው” በማለት ዘወትር ፈጣሪያቸውን ሲለምኑ የነበረው ልመናቸው በፈጣሪ ዘንድ ተቀባይነት እንዳገኘ ነው፡፡ በሌላ በኩልም የቅዱስነታቸውን ጻድቅነትና ከአምላካቸው ጋር ያላቸውን ቀረቤታ ይመሰክራል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በመንፈሳዊውም ሆነ በዓለማዊው ዕውታቸው ጣምራ ችሎታ የነበራቸው ለመንበረ ማርቆስ የተገቡ ዓለም አቀፋዊ የጥበብ ሰው እንደነበሩ፡፡ የውጭ ምሁራን ሳይቀሩ “ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በጣት ከሚቆጠሩ ጥቂት ታላላቅ ምሁራን ውስጥ አንዱ የሆኑና በኢትዮጵያ አርእስተ አበው (ፓትርያርኮች) ታሪክ ውስጥ ወደር ያልተገኘላቸው ብቸኛው ፓትርያርክ ናቸው” በማለት ምስክርነታቸውን ሰጥተውላቸው ነበር። ስም ወደ ሥራ ይመራል እንዲሉ፥ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የመናገር ተሰጥዖ የነበራቸው፥ በወንጌል ስብከታቸው የብዙኃኑን ልቡና የዳሰሱና አጥንትን የሚያለመልም አንደበት የነበራቸው የወንጌል ገበሬ ነበሩ፡፡ ቅዱስነታቸው በፓትርያርክነት ዘመናቸው ያስመዘገቡት አስደናቂ ታሪክ ሁሉ በተጋድሎና በፍጹም የእምነት ጽናታቸው መሥዋዕትን ከፍለው የሠሩት እንጂ ነገሮች ሁሉ ቀና ሆነው የአልጋ በአልጋ የሆነ ውጤት የተመዘገበበት አልነበረም፡፡ በዚህም ኢትዮጵያውያን ምሁራን “ሰማዕት ዘእንበለ ደም” በማለት ለሠሩት መልካም ሥራ በመመስገን ፈንታ ይወረወርባቸው የነበረውን የቃላት ሰይፍ ለመግለጽ እንደተጠቀሙበት በወቅቱ ተመልክተናል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንና ለኢትዮጵያውያን ፥ ከዚያም አልፎ ለአፍሪካ ብቻ ሳይሆን ሰብአዊ ፍጡር ሁሉ በሰላምና በመተሳሰብ በእግዚአብሔር ዓለም በፍቅርና በአንድነት እንዲኖርበማስተማርና እንዲቀራረብ በማድረጉ ሥራ ታሪክየማይዘነጋ ውጤትን አስገኝተዋል፡፡
በሀገር ውስጥና በአፍሪካም፥ በኢትዮጵያና በኤርትራ˖ እንዲሁም በሱማሌ የእርስበርስ ጦርነትን ለማስቆም፥ _ በጦርነቱ የተጎዱትንም በመርዳት፥ በደርግ ዘመን ያሰሯቸውን የደርግ ባለሥልጣናት በማስፈታትና ግብረ ሰዶማዊነትን በግልጽ በአደባባይ በመቃወም ሌት ከቀን በትጋት ሠርተዋል፡፡
ቅዱስነታቸው “ከአፍሪካውያን የበለጠ አፍሪካን የሚወድ ማንም የለም” ስለዚህ በአፍሪካ ላለው የሰላም ችግር“አፍሪካዊ መፍትሄ ማግኘቱ ወሳኝ ነው” በሚሉት ስሜት ቀስቃሽና በጥበብ የተቀመሙ አነጋገራቸው በብዙኃኑ የውጪውን ብረተሰብ ጭምር ይታወቃሉ ::
በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የልዩ ልዩ ሃይማኖት ተቋማት መሪዎች የሆኑ ኢትዮጵያውያን ወገኖች ለሀገር ሰላምና ዕድገት ከመቸውም ጊዜ በበለጠ መልኩ በሀገራዊ ፍቅር በመተሳሰር በሰላምና በፍቅርበጋራ እንዲሠሩና ሀገራቸውን እንዲገነቡ በኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት የበላይ ጠባቂነታቸው አማካኝነት ከፍተኛ ጥረትን አድርገዋል፤ ተጨባጭ ውጤትም አስመዝግበዋል፡፡ በተቋሙ ውስጥም በሁሉም የሃይማኖት አባቶች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያተረፉ አባትም ነበሩ፡፡
የቅዱስነታቸውን ታላቅ የሥራ የሰላምና የፍቅርሰውነት በሀገር ውስጥና _ በውጪው ዓለም የሚገኙ መንግሥታዊና ሕዝባዊ ድርጅቶች፡ እንዲሁም የልዩ ልዩ እምነት ተከታይ መሪዎች በኃዘን መግለጫቸው ደጋግመው በመዘገብ የቅዱስነታቸውን ታላቅ ሰብእና በማጉላት መስክረውላቸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ለዓለም ሰላምና ለሰብአዊ ርኅራኄ ሥራዎች ባደረጓቸው ጉልህ ዓለም አቀፍ ውጤቶች በተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ጉዳይኮሚሽን የናንሰን (Nansen) ሜዳልን ተሸልመዋል፡፡ ኤችአይቪ ኤድስን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ባደረጉት አስተዋጽኦም ዓለም አቀፍ ተሸላሚ ነበሩ፡፡ ቅዱስነታቸው ዓለም የፍቅር ዐይኑን ያሳረፈባቸው፥ በታላቅ መንፈሳዊ አባትነታቸው ያመነባቸው የሰላምና የመቀራረብ ማሳያ የነበሩ መሆናቸውን ያለ ልዩነት የሚስማማበት ሀቅ ነው፡፡
ለዚህም ምስክሩ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክርቤት ፕሬዚደንት አድርጎ የመረጣቸው መሆኑ፤ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚደንት ሆነው እንዲሠሩ ያደረጋቸው መሆኑ፤ የዓለም የሰላም አምባሳደርነትን ሥልጣን በማግኘት የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊና የመጀመሪያው ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ _ መሆናቸው ለማሳያነት በቂ ይሆናሉ፡፡ ሌላው ቅዱስነታቸውን ልዩ የሚያደርጋቸው ለዚህ ታላቅ መንፈሳዊ ሥልጣን ከበቁበት ዕለት ጀምረው የእረፍት ጊዜ ሳይኖራቸው በየሆስፒታሉ፥ በየእስር ቤቱ እየሄዱ በመጠየቅ ለሞቱት ወገኖቻችን ከካህናት ጋርእኩል ቆመው ጸሎተ ፍትሃትን በማድረግ የኅብረተሰቡን የዕለት ተዕለት ሕይወት የሚጋሩ ትሑትና ሰው አክባሪ አባት ነበሩ፡፡ ቅዱስነታቸው የበደላቸውን ይቅር የሚሉና የሚሾሙ፥ ከዚህ በፊት በድሎኛልና ልበቀለው የማይሉ ፍጹም የይቅርታ አባትም ነበሩ።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በተጠሩበት ከፍተኛ የፓትርያርክነት ሥልጣን በሥራቸው የሚተማመኑ የሚወሰኑና በሚያደርጉት ሁሉ በልበ ሙሉነት ሃላፊነትን ለመውሰድ ወደኋላ የማያፈገፍጉ ፍጹም የአመራርና የእውነት ሰው ነበሩ ለዚህም ችሎታቸው በሀገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደረጃ ያከናወኗቸው ሥራዎች ሕያውና ቋሚ ምስክሮች ናቸው፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በዘመነ ሢመታቸው ያለ ዕረፍት በመሥራት ጽሑፍ የማይወስነው ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍ ከቤተ ክርስቲያናችን አልፎ ለመላው ኢትዮጵያዊ ኩራት የሆነ ሕያው ሥራን በማከናወን ተጨባጭ ውጤቶችን ያስመዘገቡ ፓትርያርክ ነበሩ ቢባሉ የሚበዛባቸው አይሆንም፡፡
በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዘመነ ሢመት ቤተ ክርስቲያን የተረሣውን ታሪኳን አድሳ˖ የተወረሰውን ንብረቷን አስመልሳ፥ እንደገና በሕያውነት የተንቀሳቀሰችበት˖ በዓለም _ አቀፍ ደረጃ የታሪክና የሉአላዊነት ብኩርናዋን ያረጋገጠችበት፥ ድምፅዋ በዓለም ጆሮ ተሰሚነትን፥ ሥራዋ ትኩረትን ያገኘበት ዘመን ነበረ፡፡ ይህም በመሆኑ ቤተ ክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መልኩ ዓለም አቀፋዊ ቅርጽን የያዘችበት ወቅት እንደነበር ታሪክ መዝግቦታል፡፡ በየአብያተ ክርስቲያናት ዙሪያ ሊኖሩን የሚገባ ተቋማት ቢኖሩ ትምህርት ቤቶች ናቸው በማለት ቅዱስነታቸው የሰጡትን አባታዊ መመሪያ ተከትሎ መክነው የነበሩ ጥቅም አልባ ቦታዎች ዛሬ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፤ የሕክምናና ሌሎች ለኅብረተሰቡ ጥቅም የሚሰጡና ለቤተ ክርስቲያናችን የገቢ ምንጭ በመሆን የሚያገለግሉ ተቋማትን ማስገኘት ችለዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እስከአሁን ድረስ በሀገርውስጥ ካከናወኗቸው ዐበይት የሥራ ውጤቶች መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
ከ50 በላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተተኪ የሆኑ አባቶች ኤጲስቆጶሳትን ሹመዋል፤ ለብዙ ዓመታት ተወርሰው የቆዩትን የቤተ ክርስቲያን ሀብታት አስመልሰው የቤተ ክርስቲያንን _ መብት በማስከበር ቤተ ክርስቲያናችን በሀብቷ እንድትጠቀም አድርገዋል፤
ታላቁ የቤተ ክርስቲያን የከፍተኛ ትምህርት ተቋም የሆነውንና በደርግ ዘመን ተወርሶ የነበረውን የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን አስመልሰው _ አገልግሎት እንዲሰጥ አድርገዋል፤ አዳዲስ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትንም አቋቁመዋል፤
ቀደም ባሉት ዘመናት የቤተ ክርስቲያኒቱ የገቢ ምንጭ የነበሩና በደርግ ዘመን የተወረሱትን ታላላቅ _ ሕንጻዎች አስመልሰዋል፤
በደርግ ዘመን ተዘግተው የነበሩትን የአብያተ ክርስቲያናት ዋና በሮች እንዲከፈቱ በማድረግ ምእመናን እንደ ልብ በሚቀርባቸው የመግቢያ በርበነፃነት ገብተው ጸሎታቸውን ማድረስ እንዲችሉ አድርገዋል፤
ቤተ ክርስቲያን የልዩ ልዩ ከፍተኛ መንፈሳዊና ሕዝባዊ ትምህርት ቤቶች፥ የሕክምና፥ የተግባረ ዕድና የሌሎችም የመሳሰሉት ከፍተኛ ተቋማት ባለቤት በመሆን ራሷን መቻል የምትችልበትን ሁኔታ አመቻችተዋል፤ ይህ በመሆኑም ዛሬ አብዛኛዎቹ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የ1ኛና የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ባለቤት እንዲሆኑ አድርገዋል፤ ሌሎቹ ደግሞ የኮሌጆች˖ የክሊኒኮች፥ እንዲሁም ልዩ ልዩ አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ታላላቅ ሕንጻዎች ባለንብረት እንዲሆኑ አድርገዋል፡፡
ሥራ ታዲያ ለቤተ ክርስቲያን የተሟላ ሕይወት የጀርባ አጥንት የሆነ ተግባር በመሆኑ በመላዋ ቤተ ክርስቲያን ሥር የሚገኙ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ይህንኑ ልምድ በመውሰድ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡
ቅዱስነታቸው ለቀደምት አባቶቻችን ታላቅ ክብርን የሚሰጡ፥ ለቅርሶች መጠበቅ ቅድሚያ የሚሰጡ አባት በመሆናቸው በውጭ መንግሥታት ተዘርፈው የነበሩ የታሪክ ቅርሶችና ቅዱሳት መጻሕፍት እንዲመለሱ ባደረጉት ከፍተኛ ጥረት ስኬታማ በመሆን የሀገሪቱንና የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብት የሆኑ ቅርሶች እንዲመለሱ አድርገዋል ከእነዚህ መካከልም የአክሱም ሐውልትና አፍሮ አይገባ መስቀል ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በመላው ኢትዮጵያ የሚገኘው ጥንታዊ ቅርስም በአንድ ማዕከል በዘመናዊ አደረጃጀት ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ በነበራቸው ጽኑ አቋምም የቤተ ክርስቲያንና የሀገሪቱ አኩሪ የሆኑ ታሪካዊ ቅርሶችን ዓለም አቀፋዊ በሆነ ደረጃ ለሀገር ውስጥም ሆነ ለውጪ ሀገርጎብኝዎች ዝግጁ ሆኖ መቅረብ እንዲችል የአክሱም ጽዮን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክርን በዘመናዊ መንገድ ማስገንባት ጀምረው ፍጻሜውን ሳያዩ ቀርተዋል፡፡ ፕሮጀክቱም የቅዱስነታቸውን ሕልፈት ተከትሎ ቆሟል ለማለትያስደፍራል፡፡
አማርኛ ቋንቋ እንዲተረጎሙ የተደረገ ሲሆን፤ ሌሎች በሌላ በኩል የቤተ ክርስቲያናችን የእምነትና የታሪክምንጭ የሆኑ ልዩ ልዩ መጻሕፍት ከግእዝ ቋንቋ ወደ አዳዲስ መጻሕፍትም እንዲዘጋጁ የተመቻቸ ዕድል እንዲፈጠር በማድረጋቸው በዘመነ ሢመታቸው 81ዱ መጽሐፍ ቅዱስን ጨምሮ አያሌ መጻሕፍት ታትመው አገልግሎት ላይ ውለዋል፡፡
አምስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚደንት፤ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚደንትና ባለፉት ሃያ ዓመታት አገልግሎታቸው ያከናወናቸውን ሐዋርያዊ አገልግሎት በዚህ አጭር ጽሑፍ ቀርቶ ራሱን በቻለ መድብልም መግለጽ አይቻልም ለበረከትና ቅዱስነታቸውን ለመዘከር ያህል በመጠኑ ይህን ካቀረብን ወደፊት በዝርዝር የቅዱስነታቸውን ሐዋርያዊ አገልግሎት በመዘገብ የቤተ ክርስቲያናችንን ውጤታማ ተግባራት ለመግለጽ የምንሞክር ሲሆን፤ የእውነት አምላክ እግዚአብሔር የቅዱሱን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን አባት የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን ነፍስ ከወዳጆቹ ከአብርሃም ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጎን ያኑርልን የቅዱስነታቸው በረከትና ረድኤት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን፡፡