በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቦሌ ምዕራፈ ሰማዕታት ወደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል እና ቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን የተከናወነው የወንዝ ማስቀየስ ሥራ ተጠናቆ በብፁዓን አባቶች ቡራኬ ተመረቀ።
ከታህሳስ ወር 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሲገነባ በቆየው የወንዝ ማስቀየስ ሥራ በተለያየ ወረዳ ተበታትነው የነበሩ ቦታዎች ወደአንድ ወረዳ እንዲካተቱ እና ደብሩ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ እንዲያገኝ ተደርጓል።
በከፍተኛ ወጪ በአጭር ጊዜ የተከናወነው ግንባታ በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስአበባ የሀዲያ እና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የሰሜን አሜሪካ ሚኒሶታ እና ኮሎራዶ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተባርኮ ተመርቋል።
በምረቃ መርሀ ግብሩላይ ብፁዓን አባቶች እና የቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጅ መልዓከ ብርሃን ሩፋኤል የማነ ብርሃን ፣ የአድባራት እና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ሊቃውንት አባቶች የክፍለ ከተማው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አደፍርስ ሆራ እና ሌሎች የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም በርካታ ምዕመናን ተገኝተዋል።
በኩረ ትጉኀን ጸጋዬ ዓለማየሁ የሰበካ ጉባኤ ምክትል ሊቀመንበር ባቀረቡት ሪፖርት ደብሩ በ2012 ዓ.ም ከተመሠረተ ጀምሮ የተከናወኑ ሥራዎችን አብራርተዋል።
የክፍለ አተማው ሥራ አስፈፃሚ አቶ አደፍርስ ሆራ ቅድስት ቤተክርስቲያን የምታከናውነውን ሥራ አድንቀው በቀጣይም አብረው እንደሚሠሩ ቃል ገብተዋል ።
የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ብሥራት መምህር አብርሃም ዲበኩሉ በበኩላቸው በተከናወነው የልማት ሥራ አስተዋጽኦ ላበረከቱት በሙሉ ምስጋና አቅርበዋል ።
ከምስጋናውም ባሻገር በወንዝ ማስቀየስ ሥራው ላይ በተለያየ መልኩ ለተሳተፋ ወገኖች የምስጋና ስጦታ እና የምሥክር ወረቀት ተበርክቷል።©Eotc tv