እናንተ የነገዋ ቤተክርስቲያን ተስፋዎች ናችሁ:- ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሊቀ ጳጳስ አባታዊ ቡራኬ 11 ደቀመዛሙርት በዛሬው ዕለት በታላቅ ድምቀት ተመረቁ።
ሐምሌ 4 ቀን 2018 ዓመተ ምህረትበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የከምባታ ሀላባና ጠምባሮ ሀገረ ስብከት ለሁለት ተከታታይ ዓመታት በአብነት ትምህርት ቤት ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ 11 ደቀመዛሙርት በብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሊቀ ጳጳስ ቡራኬ በታላቅ ድምቀት ተመርቀዋል።
በሀገረ ስብከቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደው ይህ የምረቃ መርሐ ግብር የቤተክርስቲያንን መንፈሳዊ የትምህርት ጥራትና የሰው ኃይል ግንባታ ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር ታሪካዊ ክንውን ሆኖ አልፏል።
የምረቃ መርሐ ግብሩ በሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ኃይል ቆሞስ አባ ሚካኤል ታደሰ የመክፈቻ ንግግር የተጀመረ ሲሆን አባ ሚካኤል የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈው ባለፉት ሁለት ዓመታት ደቀ መዛሙርቱ በጽናት የያዙትን የአብነት ትምህርት ጉዞ አስመልክቶ አጠቃላይ ሪፖርት አቅርበዋል።
ለዚህ ታላቅ ዕለት መሳካት የብፁዕ አባታችንን አባታዊ ንቃትና ቀጥተኛ አስተዋጽኦ በጉልህ የጠቀሱት ዋና ሥራ አስኪያጁ ማህበረ ቅዱሳን ላደረገው የላቀ ድጋፍና ተሳትፎ በሀገረ ስብከቱ ስም ልባዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በዕለቱ የከምባታ ሀላባ ጠምባሮና የዳውሮ ኮንታ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ በሰጡት አባታዊ ቃለ ምዕዳን ምሩቃኑን “የመንፈስ ቅዱስ ልጆቼ” በማለት እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
ብፁዕነታቸው አያይዘውም “እድልን የሰጠን እግዚአብሔር ነው፤ የእግዚአብሔር የራሱ ጊዜ አለውና በራሱ ጊዜ ሁሉን ፈፅሟል በማለት ገልጸው ማህበረ ቅዱሳን ይህንን የአብነት ትምህርት ቤት ከ4 ዓመታት በኋላ ገንብተው በማጠናቀቅ ትልቅ ድጋፍ ቢያደርጉም አነሆ ህንጻውን ዛሬ ህያው ያደረጋችሁት ግን እናንተ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቼ ናችሁ” በማለት ለምሩቃኑ ያላቸውን አባታዊ አድናቆት ገልጸዋል።
ለአንድ ሀገረ ስብከት 11 ደቀ መዛሙርትን ማስመረቅ ቁጥሩ ትንሽ መስሎ ቢታይም እናንተ ግን ለእኛ ከ100 በላይ ናችሁ በማለት የገለጹ ሲሆን ምክንያቱም ብዙ የተዘጉብን አብያተ ክርስቲያናት ስላሉ እናንተ ከካህናቱ ጎን በመሆን ያንን ቤተ ክርስቲያን መክፈትና ህዝበ ክርስቲያኑን ማስተማር ይጠበቅባችኋል ሲሉ ብፁዕነታቸው አደራቸውን ጥለዋል።
ደቀ መዛሙርቱ ከቤተሰብ ተለይተው በሚኖሩበት ወቅት ክፍተት እንዳይሰማቸው ሀገረ ስብከቱ በበዓላት የጾም መዋያ ፣ የንጽህና መጠበቂያና አልባሳትን በማቅረብ ከፍተኛ ክትትል ሲያደርግ መቆየቱንም አስታውሰዋል።
በተጨማሪም ብፁዕነታቸው እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ አሜሪካ በሚገኙት የሲያትል ቅዱስ ገብርኤልና ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪዎች ክቡር መልአከ ሳህል አወቀና መልአከ ኃይል አባ ሰይፈ ገብርኤል ምዕመናንን በማስተባበር ደቀ መዛሙርቱ ወደየአጥቢያቸው ሲመሉ መብዓ ይዘው መሄድ አለባቸው በማለት መጽሐፍ ቅዱስ ፣ ዕጣን ፣ ዘቢብና ጧፍ እንዲሁም የጉዞ ብር ድጋፍ ስላደረጉ በራሳቸውና በሀገረ ስብከቱ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በዕለቱ የሪፖርት አቅራቢ የነበሩት የማህበረ ቅዱሳን ዱራሜ ማዕከል ሰብሳቢ ዲ/ን ታገሰ ሀንዴቦ ማህበሩ የቤተክርስቲያንን የአብነት ትምህርት ቤቶች ለማጠናከር ከ1991 ዓ.ም ጀምሮ ከ170 በላይ ፕሮጀክቶችን መደገፉን ገልጸው በዘንድሮው ዓመት ብቻ ለ177 የትምህርት ተቋማት፣ ለ2001 ቀሳውስትና ለ238 መምህራን ከ19 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ መደረጉንና ከ17 በላይ አዳዲስ ተቋማት በመገንባት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ዲ/ን ታገሰ ምሩቃኑ የያዙትን ዕውቀት ለቤተክርስቲያን እድገት እንዲያውሉት ጥሪ አቅርበው ማህበሩ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
በመጨረሻም ለ11ዱም ደቀ መዛሙርት የዕውቅና ሰርተፍኬት ሽልማት የተበረከተ ሲሆን ለሀገረ ስብከቱ ፣ ለመምህራንና ለዱራሜ መንበረ ጵጵስና ደብረ ፀሐይ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የዕውቅናና የምስጋና ሽልማት በመስጠት መርሐ ግብሩ በብፁዕ አባታችን ቡራኬ ፍፃሜውን አጊንቷል።
© ዜና ጎርጎርዮስ