“የአበው ሥርዓት ለቤተ ክርስቲያን አንድነት” በሚል መሪ ቃል ሲካሄድ የቆየውን የገዳማት አበምኔቶችና እመምኔቶች አገር አቀፍ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ሚያዚያ ፳፫ ቀን ፳፻፲ወ፰ዓ.ም
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የገዳማት አስተዳደር መምሪያ ባዘጋጀው መርሐ ግብር፤ ከመላው ኢትዮጵያ የአንድነት ገዳማት ለተውጣጡ አበምኔቶች እና እመምኔቶች “የአበው ሥርዓት ለቤተ ክርስቲያን አንድነት” በሚል ርዕስ ሲሰጥ የነበረው የሥልጠና እና የምክክር ጉባኤ ፍጻሜውን አግኝቷል።
ከሚያዝያ ፳፪ እስከ ሚያዚያ ፳፫ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም
ድረስ ለሁለት ተከታታይ ቀናት በተካሄደው በዚህ ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ፤ የገዳማቱን አስተዳደራዊ እና መንፈሳዊ አቅም የሚያጎለብቱ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል። ከዚህም ባለፈ ተሳታፊዎቹ አባቶች እና እናቶች እርስ በርስ የልምድ ልውውጥና ጥልቅ ምክክር ያደረጉ ሲሆን፣ ከብፁዓን አባቶችም አባታዊ ቃለ ምዕዳን ተሰጥቷቸዋል።
በጉባኤው ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የደቡብ ምዕራብና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፣
የመንበረ ፓትርያርክ የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ብፁዕ አቡነ ቶማስ የምሥራቅ ጎጃም፣ የመተከል እና አዊ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተዋል። በተጨማሪም
የገዳማት መምሪያ ዋና ኃላፊ መጋቤ ካህናት አባ ሀብተ ጊዮርጊስ ዓሥራትን ጨምሮ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የመጡ የገዳማት
አበምኔቶች (አባቶች) እና እመምኔቶች (እናቶች) የጉባኤው ተካፋይ ነበሩ።
በመዝጊያው መርሐ ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ሰፋ ያለ አባታዊ መልእክትና መመሪያ አስተላልፈዋል። ብፁዕነታቸው በንግግራቸው “ገዳማት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጽናት መሠረቶች ናቸው” በማለት አጽንዖት ሰጥተው፣ አባቶችና እናቶች በአንድነት መሰባሰባቸውና መወያየታቸው ትልቅ ውጤት ያመጣ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። አክለውም “ለገጠሙን ችግሮች በጋራ ባደረግነው ውይይት መፍትሔ አግኝተናል፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሁን ካለችበት ሁኔታ አኳያ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የጸኑ ጠንካራ
መነኮሳት በእጅጉ ያስፈልጓታል። ስለዚህም ወደ ቀደመው እና ወደ ጥንታዊው የአበው መንፈሳዊ ሕይወት መመለስ ግድ ይለናል”
ብለዋል።
ከተሳታፊዎች ለተነሳው የማረፊያ ቦታ ጥያቄ በተመለከተም፣ ጉዳዩን አጥንተው ለቅዱስ ሲኖዶስ እንደሚያቀርቡ ብፁዕነታቸው ቃል ገብተዋል።
በመጨረሻም ገዳማውያኑ የቅዱስ ሲኖዶስ የጸሎት መሠረት መሆናቸውን በማስታወስ፣ “ጾምና ጸሎት ትልልቅ
መንፈሳዊ የጦር መሣሪያዎች በመሆናቸው ለሀገር እና ለቤተ ክርስቲያን ሰላም በትጋት ጸልዩ” ሲሉ አደራ ብለዋል።
ለሁለት ቀናት በስኬት ሲካሄድ የቆየው ይህ የምክክር እና የሥልጠና ጉባኤም፣ በአረጋዊው አባት በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ
አባታዊ ቃለ ምዕዳን እና ቡራኬ ተጠናቋል።©EOTC t.v.