ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በጠቅላይ ቤተክህነት ጽርሐ ተዋሕዶ አዳራሽ በተካሄደው የአቀባበል መርሐ ግብር ላይ ያስተላለፉት አባታዊ መልዕክት

ቅሩብ እግዚአብሔር ለየዋሃነ ልብ ወያድኀኖሙ ለትሑታነ መንፈስ እግዚአብሔር ልባቸው ለተሰበረ ቅርብ ነው መንፈሳቸው የተሰበረውንም ያድናቸዋል፡፡” መዝ 33፤ 18

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዘመነ ብሉይ የብሉይ ኪዳንን አስተምህሮ በሐዲስ ኪዳን ደግሞ በጃንደረባው አማካይነት ክርስትናን ከተቀበለች በኋላ የውስጥ እና የውጭ ችግሮች ቢኖሩም ዘመናትን በመሻገር ዶግማዋን እና ቀኖናዋን በመጠበቅ ለዛሬ ደርሳለች፡፡

ለዚህም የክርስትና እምነት ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚያሰጥ መንፈሳዊ ጉዞ በመሆኑ አባቶቻችን ሊቃውንት እና ብጹዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት አንድ ላይ በመሆን የሕዝቡ መንፈሳዊ ጉዞ ረዥም እንደሆነ በመገንዘብ እያንዳንዱ ሃይማኖታዊ ትሑፊት ለትውልዱ እንዲተላለፍ ለማድረግ ለቤተ ክርስቲያኒቷ በተሠራላት ሕግ መሠረት በየጊዜው የሚመሯትን አባቶች በመምረጥ ቤተ
ክርስቲያኒቷን እንዲመሩ የሚያደርጉ በመሆኑ በዚሁ መሠረት ባሳለፍነው የ2017 ዓ.ም የግንቦት ርክበ ካህናት ለቀጣይ ሦስት ዓመታት ቤተ ክርስቲያኒቷን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እንድንመራ አባቶች አደራ ሰጥተውናል፡፡

አደራው ግን እጅግ ከባድ እንደ መሆኑ መጠን አደራውን መወጣት እንድንችል የሁላችንም ኃላፊነት ከመቼውም ጊዜ በላይ ከባድ እና ጥብቅ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቷን ለማገልገል የምናደርገው ጥረት በመንፈሳዊ መሠረት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ያስፈልጋል ለዚሁም የአባቶቻችን ጸሎት እንደሚረዳን እናምናለን፡፡

አሁን በዚህ ዘመን ያለችቷ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ሁኔታዋ እናመንፈሳዊ አገልግሎቱ እንዲሁም ሁለንተናዊ የልማት ጉዞዋ እጅግ ውስብስብ እንደመሆኑ መጠን ይህን ለመወጣት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንደተጠቀሰው እኛም በትሑት ልብ ነህምያ የፈረሰችውን የኢየሩሳሌምን ቅጥር መልሶ ለመገንባት እኛ ልጆቹ ተነስተን እንሠራለን የሰማይ አባታችንም ያከናውንልናል በማለት የሥራው መጀመሪያ አደርጎ እንደተናገረው አሁንም ከዚህ ትምህርት በመውሰድ በጥልቅ እምነት በጸሎት በአስተዋይነት እና በቁርጠኝነት የሚቃወሙት እና እርሱ ቅጥሩን እንዳይሠራ የሚይፈልጉ ወገኖች ቢኖሩም እነርሱን ተሸግሮ የእግዚአብሔርን አጋዥነት ተስፋ በማድረግ የኢየሩሳሌምንቅጥር መልሶ እንደገነባ ሁሉ ዛሬም ያለብንን ችግር ፈትቶ ትውልዱ ከሚዘፈቅበት
ዓለማዊነት በማላቀቅ ቤተ ክርስቲያኒቷን ለትውልድ ለማሻገር እኔም ሆንኩኝ ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንደ ነህምያ መሥራት ይጠበቅብናል፡፡

ብጹዕ ወቅዱስ አባታችን
ብጹዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት

ነህምያ ከሁሉ በፊት ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ መንገዱን ለእግዚአብሔር በመስጠት ያሉ ችግሮችን በማጥናት የፈረሰውን ቅጥር በምሽት ዞሮ በማየት ቅጥሩ ለመፍረስ የቻለበትን ችግር ተረድቶ እንደገና እንዳይፈርስ ለማድረግ ለመገንባት እንደጀመረ ሁሉ ከእኛ ቀደም ብሎ በቦታው ላይ የነበሩት ኣባቶች ዘመናቸው በፈቀደላቸው መጠን እንደሠሩት እኛም ዛሬ ቤተ ክርስቲያን ወደ ፊት እንድትራመድ እንደ ቀድሞ ክብሯ እና ገናናነቷ እንዳትታይ ያደረጓትን ችግሮች በማጥናት እና በማየት በማቀድ መሥራት እንደሚገባን ይጠቁመናል፡፡

እርግጥ በነህምያ ዘመን የነበሩት አንዳንድ ወገኖቹ የእርሱን ሃሳብ እና የእግዚአብሔርን መንገድ ባለመረዳት ቅጥሩን መልሶ መገንባት እንደማያስፈልግ በጦቢያ እና በጌሼም የሚመሩ ተቃዋሚዎች ተነስተው በማስፈራራት እና በማፌዝ ሴራ ቢያሴሩበትም እርሱ ግን እጅ ባለመስጠት እኛ ልጆቹ ተነስተን
እንሠራለን የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል በማለት በጸሎት በንቃት እንደተቋቋማቸው ሁሉ እኛም በዙሪያችን የሚፈጠሩትን ችግሮች ለእግዚአብሔር በመስጠት ቤተ ክርስቲያናችንን በቁርጠኝነት መንፈሳዊ አስተዳደራዊ እና ማኀበራዊ ጉዳዮቿ በአንዳንድ ቢታዎች ላይ የሚታዩ አስተዳደራዊ ክፍተቶችን በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚነሱ አለመግባባቶችን ፣ የንብረት አያያዝ ችግሮችን ፣በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ የሚታዩ ክፍተቶችን በማከም በሁሉም አቅጣጫ የሚገኙት ምዕመናን ልጆቻችን ከቤተ ክርስቲያናቸው ጋር ያላቸውን መዳከም ፣ በተለያዩ ምክንያቶች እኛ የበለጠ ባለመሥራ
ታችን ከቤተ ክርስቲያኒቷ የሚርቁ እንዳይኖሩ ፈተናዎችን ለማሻገር ተግተን ልንሠራ ይጠበቅብናል ፡፡

ብጹዕ ወቅዱስ አባታችን
ብጹዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት

ቤተ ክርስቲያን አሁን ያለችበት ዘመን 21 ኛው ክፍለ ዘመን ላይ በመሆኑ እንደ ከዚህ ቀደሙ በዘልማድ ብቻ ልንጓዝ ስለማይቻል በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ እና ከቤተ ክርስቲያኒቱ ውጪ ያለውንም በመቃኘት ዕቅድ በማውጣት መንፈሳዊ አስተዳደራዊ ማኀበራዊ ክፍተቶችንም በመለየት ተጨባጭ የመፍትሔ ዕቅዶችን
በማውጣት በጥናት ላይ የተመሠረተ ውሳኔ ልትሠጥ ይገባታል፡፡

ቤተ ክርስቲያን በዚህ ዘመን በውስጥ ብቻ ሆነን ከምንሠራው በበለጠ ከውጭ ካሉትም ከተለያዩ አካላት ጋር ከመንግሥትም ጭምር በአስተዋይነት እና በጥበብ በመቅረብ ቤተ ክርስቲያኒቷ ተከብራ እንድትሻገር ካላደረግን የትውልድን ቅብብሎሽ ሊያደክምብን ይችላል፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን ከመንፈሳዊ አገልግሎቷ ጎን ለጎን አገልግሎት ለምትሰጣቸውም ሕዝብ በመራራት ልትደርስላቸው ስለሚገባት የቤተ ክርስቲያኗን የውስጥ ሰላም በማጠንከር በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ ዜጎቿ ወደ ሰላም መንገድ እንዲመጡ መነጋገር እንዲችሉ የቤተ ክርስቲያን ድርሻዋ ከፍተኛ በመሆኑ እና ሊሠራ ስለሚገባ ትልቅ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡

በመጨረሻም እግዚአብሔር ቢፈቅድ ባሉን ቀጣይ ሐዋሪያዊ የአገልግሎት ዘመናት በውስጥም ሆነ በውጭ ዓለማት የምትገኙ ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት የሁላችን ድርሻ ትልቅ በመሆኑ ከፊትለፊታችን ያለውን የቤተ ክርስቲያን አንድነት ላይ ምላሽ ለመስጠት ሁላችሁም በተወከላችሁበት በተሰጣችሁ
ኃላፊነት ተግታችሁ እንድትሠሩ በአባታዊ ፍቅር አደራ እንላለን፡፡

ሰው በተሰጠው ኃላፊነት ላይ በትጋት በታማኝነት ፣ በቅንነት መሥራት የቤተ ክርስቲያኒቷን ሕልውና ከፍ ስለሚያደርግ በሥራ ቦታም ሆነ በግል ሕይወታችሁ ሰላምን እና መግባባትን ጠብቃችሁ እንድትሠሩ ግጭቶችን እና አለመግባባትን በሰላማዊ መንገድ መፍታት ወሳኝ እና ቤተ ክርሰቲያንም ከዚህ አትራፊ መሆንዋን ማሳሰብ እወዳለሁ፡፡

እግዚአብሔር ለልበ ቅኖች ቅርብ እንደመሆኑ መጠን ልባችንን ቅን በማድረግ ሕዝባችንን እና ቤተክርስቲያንን ለማገልገል በቅዱስ ሲኖዶስ የተጣለብንን አደራ መወጣት እንድንችል ከቅዱስ አባታችን መመሪያ በየጊዜው በመቀበል የምንሠራ ሲሆን ጸሎታቸውም ይርዳን እያልን በቤተ ክርስቲያንውስጥ ከአንድ ማዕድ እየተቋደስን በሃሰብ ልዩነቶች ውስጥ የሚገኙትን
በማቅረብ በሀገሪቷ ውስጥም በየቦታው በፖለቲካ ምክንያት የሚታዩትን አለመግባባት ተቀርፎ ሰላም እንዲመጣ ድርሻችንን በመወጣት ሕዝቡ ሰላማዊ አየር እንዲተነፍስ እንድናደርግ አምላከ ቅዱሳን እንዲረዳን በመጸለይ በሰላም በኢኮኖሚያዊ ማኀበራዊ የልማት ሥራዎች ከመንግሥት ጋርም ሆነ ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር የቤተ ክርስቲያናችንን ዋና ተልዕኮ እና መብት በማስጠበቅ አብረን ለመሥራት ዝግጁ መሆናችንን እየገለጽን ፡፡

በዚህ በ2017 ዓ.ም የግንቦት ርክበ ካህናት ከእኔ ጋር የቤተ ክርስቲያኑን መንጋ እንድትጠብቁ የተሠየማችሁ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ ብጹዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ እና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን የተሸማችሁነትን ምልካም የሥራ ዘመን እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ፡፡

የቅዱስነትዎ ጸሎት እና በረከት በሥራችን ስኬታማ እንድንሆን ይርዳን ፡፡

አመሰግናለሁ።
ግንቦት 25/09/2017 ዓ.ም

አባ ሳዊሮስ
የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የደቡብምዕራብ
ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ