የካቲት ፩/፳፻፲፰ ዓ/ም
እጨጌ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
+++++++++++++++++++++++++
በወላይታ ሀገረ ስብከት በቦሎሶ ሶሬ ወረዳ ቤተ ክህነት በሊቀ ኄራን ተክለ ወልድ አጥፉ አስተባባሪነት የተገነባው የሔንቤቾ ደብረ ፀሐይ ብዙኃን ማርያም አዲሱ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ጸሎት በትናንትናው ዕለት (በዋዜማው) የተባረከ ሲሆን በዛሬው ዕለት የቅዳሴ ቤቱ ክብረ በዓል በደማቅ ሁኔታ ተከብሮ ውሏል።

በቅዳሴ ቤቱ ክብረ በዓሉም ላይ ሊቀ ኄራን ተክለወልድ አጥናፉ የጠቅላይ ሚንስትሩ የፋይናንስ አማካሪ ሚኒስተር፣ አምባሳደር ተሾመ ቶጋ፣ አቶ ገብረ መስቀል ጫላ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ፣ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ ክብርት ወ/ሮ እታገኝ ኃ/ማርያም የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ፣ አቶ ዳጋቶ ኩንቤ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮምሽን ዋና ኃላፊ እንዲሁም የፌደራል፣ የክልል፣ የዞን እና የከተማ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የገዳማት እና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ መምህራን፣ ካህናት፣ ዲያቆናት፣ የሰንበት ት/ቤት አገልጋይ ዘማርያን እና በርካታ ምዕመናን ተገኝተዋል።

በበዓሉም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እና የሶዶ ኦቶና ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ፈለገ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት ያሬዳዊ ዝማሬ ያቀረቡ ሲሆን በተጋባዥ መምህራን ዕለቱን እና በዓሉን የተመለከተ ትምህርት ወንጌል በሰፊው ተሰጥቷል።

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ክቡር ዲያቆን ተክለወልድ አጥናፉ የአባታቸውን ሊቀ መዘምራን አጥናፉን አደራ ተቀብለው ከቤተሰቦቻቸው ጋር በመመካከር ርስታቸውን ከመስጠት ጀምሮ 18 ወራትን ብቻ የፈጀ የዚህ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ግንባታ ሥራ ላይ ቁልፍ ሚና በመጫወታቸው ከዛሬ ከየካቲት 01/2018 ዓ/ም ጀምሮ “ሊቀ ኄራን” ተክለወልድ አጥናፉ ተብለው እንዲጠሩ ሰይመዋል። በዚህ ሕንጻ ቤተ ክርስስቲያን የግንባታ ሥራ የበኩላቸውን አስተዋጽዖ ያበረከቱትን ሁሉ አመስግነው ትምህርት፣ ቃለ ምዕዳን እና ቡራኬ ሰጥተው የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።