የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ያስገነባው 1B+G+8 ሕንጻ በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ ተመረቀ።
ሐምሌ 25 ቀን 2018 ዓ.ምየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ከበኲረ ምእመናን ከበደ ተካልኝ በስጦታ ባገኘው በ22 ማዞሪያ ጎላጎል ሕንጻ አጠገብ ያስገነባው B+G+8 ሕንጻ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ቡራኬ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል ።
በሕንጻው ምርቃት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና ሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ ፣ ሀዲያ እና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል ።
ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሢራክ አድማሱ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስተዳዳሪ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት አስተላልፈው ጸሎተ ኪዳን ደርሷል።
ላዕከ ሰላም ሽታው ብርሃኑ የካቴድራሉ ዋና ጸሐፊ የሕንጻው ሥራ የተመለከተ ሪፖርት አቅርበዋል ።
በሪፖርታቸውም በኲረ ምእመናን ከበደ ተካልኝ የግል ይዞታቸውን 1636 ካሬ ሜትር ቦታ ለካቴድራሉ በስጦታ የሰጡ ሲሆን በዚህም በ1080 ካሬ ላይ ያረፈ ከምድር በታች የመኪና ማቆሚያ ጨምሮ ባለ 9 ወለል ያለው ባለ ሁለት ሊፍት ሕንጻ ሲሆን ለግንባታው 200,150,916.79 ወጪ መደረጉን ገልጸዋል ።
ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሢራክ አድማሱ በሕንጻው ሥራ ያጋጠሙ ችግሮች እና የተወሰዱ መፍትሔዎችን ገልጸው በሥራው ድጋፍ ያደረጉትን ባለድርሻ ተቋማት እና ግለሰቦች አመስግነዋል ።
የአዲስ አበባ ፣ ሐድያ እና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ይህ ሕንጻ በቤተክርስቲያን በየክብረ በዓላቱ የሚከናወነው ጥላ መዘቅዘቅ እና ልመና በማስቀረት ቤተክርስቲያን በኢኮኖሚ ራሷን ችላ መንፈሳዊ እና ማኅበራዊ አገልግሎቷን እንድታከናውን የሚያደርግ ነው ብለዋል።
የሕንጻ ግንባታ ሥራውም ሌሎች አድባራት እና ገዳማት ሊማሩበት ይገባል ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሕንጻው ረጅም ጊዜ ወስዶ እንደ መሠራቱ አጨራረሱ ያማረ የሠመረ ነው። ይኸም ለካቴድራሉ ዘላቂ ጥቅም የሚሰጥ ነው ብለዋል።
መርሐ ግብሩ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጸሎተ ቡራኬ ተጠናቋል።©የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/