የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ መምህራንና ሠራተኞች ለተባባሪ ፕሮፌሰር ለብፁዕ አቡነ ፊልጶስ(ዶ/ር) የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በመመረቃቸው ልዩ የደስታና የምስጋና መርሐ ግብር አካሄዱ።
ነሐሴ ፴ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም
ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት እና የደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለተባባሪ ፕሮፌሰር ለብፁዕ አቡነ ፊልጶስ(ዶ/ር) በሰሜን አሜሪካ ከሚገኘው Liberty University በEducational Leadership (Doctor of Education) በከፍተኛ መዐርግ የዶክተሬት ዲግሪያቸውን በማጠናቀቃቸው የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ ሠራተኞች፣ የዩኒቨርሲቲው ቦርድና ሴኔት አስተዳደር ደስታቸውን ገልጸዋል።
መልአከ ኃይል አባ ጽጌ ደንግል የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርስቲ አስተዳደር ምክትል ፕሬዚደንት ለእንግዶች የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላልፈዋል። በመልእክታቸውም በብፁዕ አቡነ ፊልጶስ (ዶ/ር) እና በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ ስም፣ የደስታ፣ የምስጋናና የክብር በዓል እንኳን በሰላም መጣችሁ ብለዋል። አያይዘውም ዛሬ በዚህ ታላቅ ቀን እዚህ ተሰብስበን ያለነው የዩኒቨርሲቲያችን መሪና አባት፣ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ (ዶ/ር)፣ በአሜሪካ ከሚገኘው ሊበርቲ ዩኒቨርሲቲ በትምህርት አመራር የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በስኬት በማጠናቀቃቸው የምርቃታቸውን ደስታ በጋራ ለመጋራት መሆኑን ገልጸዋል።
“ለእኛ ለዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ይህ የደስታ ቀን ከመደበኛ የምርቃት በዓል የተለየ ትርጉም አለው” ያሉት መልአከ ኃይል “ዛሬ የምናከብረው የአንድ ሰው የትምህርት ስኬት ብቻ ሳይሆን፣ ለዩኒቨርሲቲያችን፣ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሚመጣው ትውልድ የሚተላለፍ የዕውቀትና የተስፋ ምንጭ ነው።እኛ የምንከተለውን የትምህርትና የአመራር መንገድ በተግባር የሚመሰክር የዕውቀት፣ የጥበብና የትጋት ፍሬ ነው” በማለት አብራርተዋል።“የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ዛሬ በብፁዕነትዎ ስኬት እጅግ ደስ ብሎናል። ያገኙት ትምህርት፣ የጨመሩት ዕውቀትና የተጎናጸፉት የዶክትሬት ደረጃ ለእርስዎ የስኬት አክሊል ብቻ ሳይሆን፣ ለዩኒቨርሲቲያችንም ትልቅ አቅምና ክብር የሚጨምር ነው። ለእኛ ደግሞ የተሻለ ነገን የሚያመለክት ተስፋ በመሆኑ፤ ይህ ስኬት የብፁዕነትዎ ብቻ ሳይሆን፣ የቤተ ክርስቲያናችንና በተለይም የዩኒቨርሲቲያችን ማኅበረሰብ የጋራ ደስታና ኩራት ነው” በማለት ገልጸዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ ላይ የብፁዕነታቸውን የሕይወት ታሪክ የሚያስረዳ ፍኖተ ሕይወት መጽሔት እና ከአሜሪካ እስከ ጂንካ የሚል ዘጋቢ ፊልም ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የዩኒቨርሲቲውን ከምሥረታ ጀምሮ አሁን የደረሰበትን ደረጃ የሚያሳይ ዐውደ ርዕይ ቀርቧል። በዐውደ ርዕዩ በ፲፱፴፯ ዓም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የተመሠረተው ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ከመጀመሪያው የካህናት ማሠልጠኛ ጀምሮ እስከ ዘመናዊው ዩኒቨርሲቲ ድረስ ተቋሙ በርካታ ሊቃውንት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እንዳፈራ፣ ራሱንም በትምህርት እያሳደገ እንደመጣ የሚሳይ ነው፡፡
ፕሮፌሰር አባ ኃይለ ገብርኤል ግርማ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት የብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የዶክትሬት ዲግሪ መመረቂያ ጽሑፍ ዳሰሳ ጥናት አቅርበዋል። በዳሰሳ ጥናት እንዳብራሩት፡- የብፁዕ አቡነ ፊልጶስን (ዶክተር፣ ተባባሪ ፕሮፌሰር) የላቀ የትምህርት ስኬትን በታላቅ ደስታ በማክበር ብፁዕነታቸው ከስድስት ዓመታት በላይ ትጋት በተሞላ ጥናትና፣ ምርምር እንዲሁም በጽናት መንፈስ ሰሜን አሜሪካ ቨርጂንያ ከሚገኘው ከታዋቂው ከሊብርቲ ዩኒቨርሲቲ (Liberty University) በትምህርት ሥራ አመራር ዘርፍ የዶክትሬት (Ed.D.) ዲግሪያቸውን በስኬት በዚሁ ዓመት አጠናቀዋል። የብፁዕነታቸው የዶክትሬት ማሟያ ጥናታዊ ጽሑፍ (Dissertation) ርዕስም፦ Servant Leadership in the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church: The Lived Experiences of Work Engagement and Spirituality. – (አገልጋይ መሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በአገልግሎት ተሳትፎ እና በመንፈሳዊነት ላይ የተመሠረተ የሕይወት ተሞክሮ) የሚል መሆኑን ገልጸዋል፡፡
“የመመረቂያ የጥናት ጽሑፉ ሦስት ዋና ዋና የምርምር ክፍተቶችን ለይቶ አሳይቷል” የሚሉት ፕሮፌሰር እነዚህም፡- አገልጋይ መሪነትን በኢኦተቤ በሥራ ላይ ባሉ ኃላፊዎች በተኖረ የሕይወት ልምድ በኩል የሚመረምሩ ተግባራዊ ጥናቶች አነስተኛ መሆኑን ተጠቁሟል። ከዚህ ቀደም በዚህ ዘርፍ የተጠኑ ጥናቶች አለመኖሯቸው እነዚህም የምርምር ክፍተት መሆኗቸው ተገልጿል። የጥናቱ ዋና አስተዋፅኦ አገልጋይ መሪነትን፣ የሥራ ተነሣሽነትን እና መንፈሳዊነትን በኢኦተቤ ዐውድ ውስጥ ማቀናጀቱ አስፈላጊ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በአጠቃላይ የብፁዕነታቸው የመመረቂያ ማሟያ ጥናት ጽሑፉ አስፈላጊና በበቂ ሁኔታ ያልተጠናን ርዕስ የሚዳስስ መሆኑን በዳሰሳ ጥናታቸው አሳይተዋል፡፡ የጥናቱ ጥንካሬም አገልጋይ መሪነትን በቀላሉ የውጫዊ የመሪነት ንድፈ-ሐሳብን ከመተግበር ይልቅ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መሪዎች የተኖረ የሕይወት ልምድን መመርመሩ ነው። የአገልጋይ መሪነት፣ የሥራ ተነሣሽነት እና የመንፈሳዊነት ቅንጅት በሥራ ዘርፎች መካከል ያለውን የምርምር አስተዋፅኦን ያጠናክራል። ከሁሉም በላይ ጥናቱ ኦርቶዶክሳዊ ነገረ-ሰብእ (Anthropology)፣ ቤተ ክርስቲያናዊ አስተምህሮ እና መንፈሳዊነት የመሪነትን ትርጉምና ትግበራ እንዴት እንደሚቀርፁ ያሳየ ነው፡፡ ስለሆነም የጽሑፉ አስተዋጽኦ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ አገልጋይ መሪነትን ከመለየት አልፎ፣ መሪነትን እንደ ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት፣ መንፈሳዊ እድገት እና በክርስቶስ ማዕከልነት ያለው ጥሪ አድርጎ የሚያስረዳ መሆኑን የዳሰሳ ጥናታቸው አሳይቷል፡፡
ተባባሪ ፕሮፌሰር ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ(ዶ/ር) በአዳራሹ ለተገኙት በሙሉ ምስጋናቸውን አቅርበው የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ “የሚማር ሰው ውጤታማ እንዲሆን አምስት ነገሮችን መያዝ አለበት” ብለዋል፡፡ እነዚህንም ሲያብራሩ፡- አንደኛ ግልጽ ዓላማ ማስቀመጥ ለአንድ ተማሪ አስፈላጊ ነው፡፡ ሁለተኛ ጽናትን ራስን መግዛት ሊኖረው ይገባል፡፡ በትምህርት ጉዞ መሰልቸት፣የተለያዩ የሥነ ልቦና ጫናዎች ቢያጋጥሙም ያንን መቋቋም አለበት፡፡ ሦስተኛው ውጤታም የጊዜ አጠቃቀምና ዕቅድ አራተኛ ትክክለኛ የጥናት ስልት መከተል አለበት፤ አምስተኛ የአካባቢና ማኅበራዊ ጉዳዮች ድጋፍ ናቸው፤ ብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አያይዘውም “ዛሬ በዚህ የተሰባሰብነው ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የዩኒቨርሲቲው መምህራንና ሠራተኞች፣ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የመጣችሁ፣ መንፈሳዊ ቤተሰቦቼ ጠቅላላ ይሄ ደስታ የቤተክርስቲያን ደስታ ነው፤ ይህ ውጤት የቤተክርስቲያን ውጤት ነው ብላችሁ አክብራችሁ ስለመጣችሁ በጣም ነው የማመሰግነው” ሲሉ ደስታቸውን ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ባስተላለፉት መልእክት ዛሬ ቤተክርስቲያን ትልቅ እረኛ አባት፣ ምሳሌ የሚሆኑ፣ ጊዜውን የዋጁ አባት አይተናል፡፡ ሁላችንም አባቶች ደስ ብሎናል፡፡ ዛሬ በዚህ ዘመን በጎችን ጠብቅ የተባለው እንዲህ ነው፡፡ የዛሬው በግ ጥበቃ እንደ ትናንቱ አይደለም፡፡ የትናንቱ በትናንቱ ነው የሚታየው፡፡ ዛሬ ደግሞ ከሀገር በቀል ዕውቀት ጋር ዓለም አቀፍ የሆነ የዘመኑ ዕውቀት መያዝ ያስፈልጋል፡፡ የብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ዘመኑን የዋጀ ትምህርት ለትውልዱ ትልቅ ትምህርት ነው፡፡ ቤተክርስቲያናችን በእውነት ትልቅ አባት አግኝታለች፡፡ አባታችን ለሁላችንም አርአያ፣ ምሳሌ ሆነውናል፡፡ ስለዚህ አባታችን እንኳ ደስ አለዎ፣ እንኳን ተወለዱ እንደነዚህ ያሉ አባቶች ደጋግመው ይወለዱ ለሀገር ለቤተክርስቲያን ያስፈልጋሉና ሲሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዕንጦንስ የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣የጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያና የድርጅት ኃላፊዎች፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የዩኒቨርሲቲው የቦርድ፣ የሴኔትና የአስተዳደር አባላት፣መምህራንና ሠራተኞችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡©Eotc tv