የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ልዩ ጽ/ቤትና የውጭ ጉዳይ መምሪያ የሥራ ሓላፊዎችና ሠራተኞች ርእሰ ዓውደ ዓመት በማስመልከት ከቅዱስነታቸው ቡራኬና የሥራ መመሪያ ተቀበሉ።
በመርሐ ግብሩ የሁለቱ የሥራ ክፍሎች ተወካይ ባደረጉት ንግግር የዓመቱን ሥራ በቅዱስነታቸው ቡራኬ መጀመራቸው ታላቅ ዕድል መሆኑን አስታውሰው፤ “የቅዱስነትዎን የዕለት ከዕለት አባታዊ የሥራ መመሪያ እየተቀበልን በማገልገል፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ከነሙሉ ክብሯ ለማሻገር እንችል ዘንድ ቡራኬዎና ጸሎትዎ አይለየን…” ሲሉ በመንፈሳዊ የልጅነት አክብሮት ጠይቀዋል።ብፁዕ ወቅዱስነታቸውም “ዘመነ ማርቆስ ከነበርካታ ችግሮቹ በማለፉ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፤ የጀመርነውን ዘመነ ሉቃስ መልካም ዓመት ያድርግልን፤ እናንተም ይህንኑ አስባችሁ እንኳን አደረስዎ ለማለት በመቅረባችሁ አመሰግናለሁ፤ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤትና የውጭ ጉዳይ መምሪያ ሰላም፣ ፍቅር፣ መተሳሰብና መከባበር የሰፈነበት መሆኑ የሚያስደስት ሲሆን በአዲሱ ዘመንም ይህንኑ የሥራ መንፈስ አጠናክራችሁ በመቀጠል፤ የተሰጣችሁን ታላቅ የቤተክርስቲያን ሓላፊነት በሐቀኝነት፣ በቅንነትና በታማኝነት እየተናበባችሁ ልትወጡ ይገባል…” ሲሉ የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል።
የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት እና የውጭ ጉዳይ መምሪያ ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ዐበይት ተግባራት የሚከናወኑባቸው ታላላቅ የቅድስት ቤተክርስቲያናችን ተቋማት መሆናቸው ይታወቃል።©EOTCTV