ላይፍ አዲስ ሆስፒታል ከቤተክርስቲያን ተከራይቶ በዘመናዊ መንገድ የሚያሳድሰውን ሆስፒታል በብፁዓን አባቶች አስጎበኘ።
ሰኔ 28 ቀን 2018 ዓ.ምአዲስአበባ -ኢትዮጵያ
የላይፍ አዲስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት
የተከራየውን ሕንጻና የሕክምና ተቋም አገልግሎት አሰጣጥ ይበልጥ ለማዘመንና ዓለም አቀፍ መሥፈርቶችን ወደሚያሟላ ከፍተኛ ደረጃ ለማሸጋገር የጀመረውን ሰፊ የእድሳትና የማስፋፊያ ሥራ አሁናዊ አፈጻጸም ለመገምገም የሚያስችል የሱፐርቪዥን ጉብኝት ተካሂዷል።
በዚህ መርሐ-ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የሸገር ከተማና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ የሐድያና ስልጤ ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቀ ሥዩማን እስክንድ ገብረ ክርስቶስ የቤቶችና ሕንጻዎች ልማት ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅና የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዋና ኀላፊ የመንበረ ፓትርያርክ ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች የሆስፒታሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች በተገኙበት በሆስፒታሉ ቅጥር ግቢ ውስጥ ሰፊ ምልከታ ተደርጓል።
የላይፍ አዲስ ሆስፒታል ከተከራየው የቤተክርስቲያኗ ይዞታ ላይ የመሠረተ-ልማት አደረጃጀቱን ለመለወጥና ተቋሙን በዘመናዊ መልክ ለመቅረጽ እያከናወነ ያለው አጠቃላይ የእድሳት እንቅስቃሴ አበረታች ደረጃ ላይ እንደሚገኝ በጉብኝቱ ወቅት ተመልክቷል። በተደረገው ምልከታ፣ ብፁዓን አባቶችና የሥራ ኃላፊዎቹ አጠቃላይ የሆስፒታሉን የውስጥ ክፍሎች ተዘዋውረው የተመለከቱ ሲሆን፣ ክፍሎቹ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ጠብቀው ሙሉ የላቦራቶሪና የሕክምና አገልግሎት መስጠት በሚችሉበት መልኩ ሰፊ የብርሃንና የቦታ አጠቃቀምን ታሳቢ አድርገው እየተገነቡ መሆኑ በማብራሪያው ላይ ተገልጿል።
በተጨማሪም ሆስፒታሉ ለብፁዓን አባቶችና ለክቡራን እንግዶች የሚመጥን ልዩ የቪአይፒ (VIP) የእንግዳ መቀበያና ማረፊያ ቦታዎችንም ጭምር ያካተተ ዘመናዊ አደረጃጀት ማዘጋጀቱ ተገልጿል።
በመቀጠልም በሆስፒታሉ ውስጥ ለተለያዩ የሕክምና ዘርፎችና ለታካሚዎች ማቆያነት የተዘጋጁትን የውስጥ መተላለፊያ ኮሪደሮች፣ የሕክምና መስጫዎችና የክፍል አደረጃጀቶች በዝርዝር ተጎብኝቷል ። ይህ ሰፊ የእድሳት ሥራ ሆስፒታሉ ከቤተክርስቲያን በተከራየው በዚህ ተቋም ለኅብረተሰቡ የሚሰጠውን የሕክምና ጥራት፣ ደኅንነትና ምቾት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያሳድገው ተመላክቷል።
በጉብኝቱ ማጠቃለያ ላይ ብፁዓን አባቶች ሆስፒታሉ የቤተክርስቲያንን ንብረት ይዞታ ይበልጥ በሚያሳምርና የሕዝቡን ጤና ለመጠበቅ በተሟላ መልኩ የሕክምና አገልግሎት ለመስጠት እያከናወነ ያለውን ይህንን ዘመናዊ የልማትና የእድሳት እንቅስቃሴ በላቀ ሁኔታ አድንቀዋል።