“በአዲሱ ዘመንም ሕዝቡ የጠማው ሰላም ነው”ቅዱስነታቸው
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ ሐላፊዎች በክቡር ዋና ሥራ አስኪያጅ መሪነት በአዲስ ዓመት ዋዜማ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክን እንኳን አደረሰዎ በማለት ቡራኬ ተቀብለዋል።ጳጉሜን ፭/፳፻፲፰ ዓ/ም
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ ሐላፊዎች በክቡር ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ መሪነት በአዲስ ዓመት ዋዜማ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክን እንኳን አደረሰዎ በማለት ቡራኬ ተቀብለዋል።
በዛሬው ዕለት በተከናወነው መርሐ ግብር የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ የሀገረ ስብከቱ ዋና ዋና ክፍል ሐላፊዎች የተገኙ ሲሆን ቅዱስነታቸው መቀጫ ጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ በመገኘት እንኳን ከዘመነ ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ ወደ ዘመነ ቅዱስ ሉቃስ ዜናዊ በጤና ጠብቆ በመንበርዎ አጽንቶ በሰላም አደረሰዎ በማለት ከቅዱስነታቸው ዝቅ ብለው አባታዊ ቡራኬ ተቀብለዋል።
ከሀገረ ስብከቱ ሥራ ሐላፊዎች የተወከሉ ሊቀ ሊቃውንት አባ ጥዑመ ልሳን ኪዳነ ማርያምና መልአከ ምሕረት ዘካርያስ ሐዲስ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን በመልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ ዋና ሥራ አስኪያጅነት የሚመራው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን ሐላፊነት አባቶችን የሰጡትን አደራ ከምስጋና ጋር በጥሩ ውጤት ለመመለስ እየሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።
ለዚህም በዋናነት የቅዱስነትዎ ጸሎትና ቡራኬ የሥራ መሪ የዕቅድ አሳማሪ በመሆኑን እንኳን አደረሰዎ ከማለት ጎን ለጎን ለሥራችን ጉልበት የሚሆነንን አባታዊ ቡራኬ በመቀበላችን በጣም ደስ ብሎናል ብለዋል።
ክቡር ሥራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ በበኩላቸው ለቤተ ክርስቲያናችን ልዩ ስጦታ ለዘመናችን ምልክት የሆኑትን ብፁዕ ወቅዱስ አባታችንን ዕድል ገጥሞን በጸሎትዎ ረድቶን በፊትዎ ቆመን እንኳን አደረሰዎ ለማለት ስለበቃ እግዚአብሔርን እናመሰግናን።
ቅዱስ አባታችን በጤና ጠብቆ እንኳን ከዘመን ዘመን አሸጋገረዎ በረከትዎ አይለየን ጸሎትዎ ትርዳን በማለት በሀገረ ስብከቱ የተዘጋጀውን የእንኳን አደረሰዎ መልካም ምኞት መግለጫ ካርድ ለቅዱስነታቸው እነሆ ብለዋል።
ክቡር ሥራ አስኪያጅ አክለውም የተሰጠንን ሐላፊነት በአግባቡ እንድወጣ የቅድስነትዎ ጸሎትና ቡራኬ ስለሚያስፈልገን በሁለንተናዊ አባታዊ ቡራኬና መመሪያ እንዲሁም ጸሎት እንዳይለዩን በማለት ተማጽነዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሀገረ ስብከቱ የሥራ ሐላፊዎች መጥተው እንኳን አደረሰዎ ስላሏቸው በእጅጉ አመስግናለሁ እግዚአብሔር ሥራችሁን ይባርክ ቤተ ክርስቲያናችን ይጠብቅ የሰላም ዘመን ይሁንላችሁ ብለዋል።
ቅዱስ አባታችን ቀጥለውም መስከረም ወንዞች የሚጠሩበት አበቦች የሚፈኩበት ክረምቱ እየገፈፈ የሚሄድበት ወርኅ ነው ወዲህ ደግሞ አዲስ ዓመት ነው። ይሁንና በዚህ በአዲስ ዓመት ቢሆንም ሕዝቡ የጠማው ሰላም ነውና ሁሉን በሁሉ ማድረግ ወደ ሚችለው እግዚአብሔር መጸለይ ይገባናል ብለዋል።
በብዙ ጉዳይ ልቡ ለተከፈለ በብዙ ግርፋት ሰንበሩ ላልጠፋበት ቅዱስ ሕዝብ ዝቅ ብሎ ማገልገል ተገቢ ነው ። በተለይም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን አስተዳዳር ጤናማና ለቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ምቹ ከማድረግ አኳያ አሁን ካላችሁት መሪዎች ብዙ ይጠበቃል ። አገባባቹሁ መልካም እንደሆነው ሁሉ ሥራችሁም በመልካም የተመሠከረ ሊሆን ይገባል በማለት አሳስበዋል።
በመጨረሻም አዲስ ፳፻፲፱ የምሕረት ዓመት የሰላ፣ የጤና
ና የቤተ ክርስቲያን ክብር የሚጠበቅበት ዘመን እንዲሆን ተመኝተው መርሐ ግብሩ በቅዱስነታቸው ጸሎትና ቡራኬ ተጠናቋል።
ነቢዩ ሚክያስ