የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው መንበረ ጵጵስና በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ ተመረቀ።
ሐምሌ 6 ቀን 2018 ዓ.ምየደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት አዲስ መንበረ ጵጵስና ሠርቶ መንበረ ጵጵስናው በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ፣ በብፁዕ አቡነ ቄርሎስና በብፁዕ አቡነ ኤርምያስ ቡራኬ አስመርቋል።
ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ፣ የደቡብ ወሎና በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ኬሚሴ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት የእንኳን ደህና መጣችሁ አባታዊ መልእክት አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘው መንበረ ጵጵስና በ1940ዎቹ የተገነባ መሆኑን አስታውሰዋል።
ደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት የሰሜን ወሎ፣ የዋግኸምራ፣ የአፋርና ኬሚሴ አህጉረ ስብከትን አካቶ ሲያስተዳድር የነበረ ጥንታውያን ገዳማት፣ አድባራትና የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማት መገኛ አንጋፋ ሀገረ ስብከት በመሆኑ ታሪኩን የሚመጥን መንበረ ጵጵስና ለመገንባት እቅድ ተይዟል ብለዋል።
ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ ዘመኑን የዋጀ መንበረ ጵጵስና ሳይኖራቸው ለ34 ዓመታት በታሪክ የሚዘከሩ ዘመኑን የዋጁ ሥራዎችን ሠርተዋል ያሉት ብፁዕነታቸው በሁለቱም አረጋውያን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጸሎት፣ ቡራኬና ምክር እየተመራን የአካባቢውን ታሪክ ለማሳወቅና ክብሩን ለመመለስ እንሠራለን ብለዋል።
በቀጣይ የደቡብ ወሎን ታሪክ የሚመጥንና ዘመኑን የዋጀ
መንበረ ጵጵስና እስከምንገነባ አሁን የተሠራውን መጠነኛ መንበረ ጵጵስና በአባቶች ለማስባረክ የተዘጋጀ መርሐ ግብር መሆኑንም ተናግረዋል።
መንበረ ጵጵስናው 470 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈ ሲሆን ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተጨማሪ የሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስ አንድነት ገዳም አበምኔት፣ የደሴና ኮምቦልቻ ከተሞች አብያተ ክህነት ሥራ አስኪያጆችና የአድባራት አስተዳዳሪዎች የታላላቅ ጉባኤ ቤት መምህራን በተገኙበት ተመርቋል።©የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት፧