የዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም መንፈሳዊ ትምሕርት ቤት ተማሪዎች የምርቃት ሥነ-ሥርዓት በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ እየተካሄደ ይገኛል።
ሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፲ወ፰ ዓ.ምበርካታ እውቅ ሊቃውንትን ያፈራውና በታሪክ ታላቅ ስፍራ ያለው የጥንታዊው የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም የመምህራንና ቀሳውስት ማሠልጠኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ያስተማራቸውን ደቀመዛሙርት የምርቃት ሥነ-ሥርዓት በአሁኑ ሰዓት በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ በድምቀት እየተካሄደ ይገኛል።
በዚህ ታላቅ መርሐ-ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ የምዕራብ ካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ የገዳሙ የበላይ ኃላፊዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንዲሁም የተመራቂ ቤተሰቦችና ወዳጅ ዘመዶች ታድመዋል።
ተመራቂዎቹ በገዳሙ የነበራቸውን የመንፈሳዊና የቀለም ትምህርት አጠናቀው ለዚህ ማዕረግ የበቁ ሲሆን፣ በዚህ ታላቅ መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መርሐ ግብሩን በፀሎት ከፍተዋል።በመቀጠልም በገዳሙ አስተዳደር በሊቀ ሊቃውንት ቆሞስ አባ ተ/ኃይማኖት ወልዱ ሪፖርት ቀርቧል።
በሪፖርቱም እንደተጠቀሰው ገዳሙ ከ1995 ጀምሮ በርካታ ደቀ መዛሙርት ማፍራቱ ተገልጿል። በዚህም የማስተማር ሥራው በዓለማዊውም መድረክ ቢሆን ሀገር ከመምራት ጀምሮ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ደቀ መዛሙርትን ያፈራ የሀገር ባለ ውለታ መሆኑን አንስተዋል።ገዳሙ በዛሬው የምረቃ መርሐ ግብርም 263 ተማሪዎችን ለምርቃት ያበቃ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 79 የአብነት ተማሪዎች ሲሆኑ ቀሪዎቹ በቅዳሜና እሑድ በመጽሐፍ ቅዱስ እና በሌሎች የትምህርት ዘርፎች የሚመረቁ መሆናቸውን ገልጸዋል ።
አክለውም የገዳሙ ትምሕርት ቤት በኮሪደር ልማት ምክንያት የፈረሰ በመሆኑ አዲስ ለመሥራት በዝግጅት ላይ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ተመራቂ ደቀመዛሙርት ወረብ ያቀረቡ ሲሆን በቀጣይም ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ የሠርተፊኬት አሳጣጥ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚከናወን እና ልዩ ልዩ መንፈሳዊ መርሐ ግብራት ይከወኑበታል ተብሎ ይጠበቃል።
የሥነ-ሥርዓቱን አጠቃላይ ሂደትና ማጠቃለያ ዝርዝር መረጃ መርሐ-ግብሩ ከተጠናቀቀ በኋላ ይዘን የምንመለስ ይሆናል።
©የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/