“በአዲሱ ዓመት የአስተዳደር ችግሮችን ሌላ አካል መጥቶ እንዲፈታልን ከመጠበቅ ይልቅ በጋራ ኃላፊነት መፍትሔ ማምጣት የተሻለው አማራጭ ነው”። ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ በመልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ መሪነት ከሀገረ ስብከቱ ዋና ክፍል ኃላፊዎችና ሠራተኞች ጋር በመሆን ለ2019 ዓ.ም. አዲስ ዓመት፣ ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላም በጤና አደረስዎ በማለት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የአዲስ ዓመት መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።።የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ክፍል ኃላፊዎችና ሠራተኞች በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቢሮ በመገኘት እንኳን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ አደረሳችሁ በማለት ለብፁዕነታቸው መልካም የሥራ ዘመን እንዲሆንላቸው ተመኝተዋል።
በመርሐ ግብሩ ሥራ አስኪያጁን ጨምሮ ዐራት የሥራ ሐላፊዎች መልአከ ምሕረት ዘካርያስ ሐዲስ ፣ መልአከ ገነት ልሳነ ወርቅ ተስፋ ና መልአከ ፀሐይ አባ ኃይለ መለኮት ይኄይስ ጉባኤውን በመወከል የመልካም ምኞት መግለጫ መልእክት ለብፁዕነታቸው ገልጸዋል።
በመልእክታቸውን ላይ ብፁነታቸው መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለን ለሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አድርገው ስለሾሙ በእጅጉ እናመሰግናለን በቀጣይ የሥራ ውጤቱ እንዳለ ሆኖ እስካሁን ከተመደቡበት ጊዜ ጀምሮ ላሳዩት መልካም አፈጻጸምና ቁርጠኝነት በእጅጉ ኮርተናል ብለዋል።
ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላምና በጤና እንኳን አሸጋገረዎ በማለት ለብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ደስታቸውን የገለጹት የሀገረ ስብከቱ ኃላፊዎች፣ በዚህ ማዕበል በበዛበትና በተለያዩ ፈተናዎች በተሞላው ዘመን ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓቷን በማስከበር በተሻለ ሁኔታ እየመሩ በመገኘታቸው ምስጋና አቅርበዋል።
በተለይም ከዚህ ቀደም ከቤተ ክርስቲያን እጅ ወጥተው በልዩ ልዩ አካላት ተይዘው የቆዩ የቤተ ክርስቲያን ርስቶችና ቦታዎች በሰላማዊ መንገድ ወደ ባለቤታቸው እንዲመለሱ መደረጉ ታላቅ ድል መሆኑን ገልጸዋል።
በዘመነ ማርቆስ በአንድ ዓመት ውስጥ ያሳዩትን ለውጥ በማድነቅ፣ ዘመነ ሉቃስም በሰላምና በጤና እንዲጠብቃቸውና የቤተ ክርስቲያናችን ኩራትና ክብር የሆነ ሥራ እንዲያሳዩ ልባዊ ምኞታቸውን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ በበኩላቸው ብፁዕነታቸውን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላምና በጤና አደረስዎ በማለት መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
መልአከ ብርሃን ሰሎሞን በቀለ በመልእክታቸው በዘመነ ማርቆስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በጸሎትና በአመራር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለውጦችን ያሳዩበትና ቤተ ክርስቲያኗም ታላቅነቷን የምታሳይበት ደረጃ ላይ እንድትደርስ ያደረጉት ጥረት የሚደነቅ መሆኑን ገልጸዋል።
በዘመነ ሉቃስም ከዚህ በበለጠ አርአያና አቅጣጫ የሚሰጥ ለውጥ እንደሚያመጡ ተስፋ እንደሚያደርጉ ጠቁመዋል። በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም እየታዩ ያሉትን ችግሮች በቅርብ በመሆን፣ አመራርና መመሪያ በመስጠት ለውጥ ለማምጣት ቀንና ሌሊት እየሠሩት ላለው ሥራ ከልብ ምስጋና አቅርበዋል።
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱና በብፁዕነታቸው መመሪያና አቅጣጫ ሰጪነት በልማት ሥራዎች ላይ በመሥራት፣ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋትና ከተገፉ ሊቃውንት ጎን በመቆም ለመሥራት እየተዘጋጁ እንደሚገኙም ገልጸዋል።
የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በበኩላቸው ለመጀመሪያ ጊዜ የአሁኑ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ ሐላፊዎች ላደረገላቸው የአዲስ ዓመት መልካም ምኞት ምስጋና አቅርበው፣ በአዲሱ ዓመት ቤተ ክርስቲያንን በእግዚአብሔር በተሰጠን ሐላፊነት በሥርዐት በመመራት፣ በጋራ ቁርጠኝነትና በትብብር ማስተዳደር እንደሚገባ አሳስበዋል።
ቤተ ክርስቲያንን ስናስተዳድር ከሙስናና ከዘረኝነት ነፃ ሆነን፣ በታማኝነት፣ በፍትሐዊነትና በኃላፊነት መምራት ከቻልን ውጤታማ ሥራ መሥራት እንደምንችል ጠቁመዋል። እንዲሁም በየዘመኑ የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን በንቃት መከታተልና የሚነሱ ችግሮችን በጋራ መፍታት እንደሚገባ የቤተ ክርስቲያንን ችግሮች ሌላ አካል መጥቶ እንዲፈታልን ከመጠበቅ ይልቅ በጋራ ኃላፊነት መፍትሔ ማምጣት እንዳለብን አሳስበዋል።
አክለውም አሠራሮችን በየጊዜው በመፈተሽ፣ ስህተቶችን በማረም አዳዲስ የሚመጡ አመራሮችን በምክርና በትብብር በማገዝ የቤተ ክርስቲያንን ሥራ ወደ ተሻለ ውጤት ማሸጋገር እንደሚቻልም ገልጸዋል።
በመጨረሻም አዲሱ ዓመት እግዚአብሔር አምላካችን ሀገራችንንና ቤተ ክርስቲያናችንን እንዲጠብቅልን፣ ዘመኑንም የሠላም፣ የፍቅር ፣ የሥራ፣ የስኬት፣ የበረከትና የጤና ዘመን ያድርግልን በማለት አባታዊ መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ ጽናት አስቻለው
ነቢዩ ሚክያስ