ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የዕብራውያን አዲስ ዓመት መጀመሪያ “ሮሽ ሐሻናህ” በዓል ላይ በእስራኤል ኤምባሲ ተገኝተው የእንኳን አደረሳይሁ መልዕክት አስተላለፉ።
ጳጉሜን 3 ቀን 2018 ዓ.ምአዲስአበባ -ኢትዮጵያ
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የዕብራዊያን አዳስ ዓመት መጀመሪያ
“ሮሽ ሐሻናህ” በዓል በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ጷጉሜ 2ቀን 2018 ዓ.ም ሲከበር በኤምባሲው ተገኝተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ።
(ሮሽ ሐሻናህ) በዕብራውያን ዘንድ የዓመት መጀመሪያ በመሆን የተጀመረው በኖህ ዘመን መሆኑን የገለጹት ብፁዕነታቸው ኖህና ልጆቹ ከመርከብ ከወጡ በኋላ አዲሱን ዓመት በመስከረም አክብረዋል፤ ከዚያም በሁሉም በሴም፣ በካምና በያፌት ትወልድ ይኽው ሲከበር ከሙሴ ደርሷል፤ እነሆ ይህ በዓል በየ ዓመቱ ሲከበር ቆይቶ እዚህ ዘመን ላይ የደረሰ በዓል በመህኑ እንኳን አደረሳችሁ ብለዋል።
የኢትዮጵያውያን አዲስ ዓመት ከሦስት ቀናት በኋላ ይከበራል ያሉት ብፁዕነታቸው በዛሬው ዕለት ያከበርነው የሮሽ ሐሻናህ በዓል ኢትዮጵያውያን አዲስ ዓመት በምናከብርበት ዋዜማ የተከበረ መሆኑ ልዩ ያደርገዋል ካሉ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ለአገሮቻችን እድገት፣ሰላምና ፍቅርን ይስጥልን በማለት መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ ባስተላለፉት መልዕክት ኢትዮጵያና እስራኤል የረጅም ዓመት ወዳጅነት ያላቸው አገራት መሆናቸውን ገልጸው ይህንን የረጅም ዘመን ወዳጅነታችንን አጠናክረን በመቀጠል ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር እንሰራለን ካሉ በኋላ መላው ኢትዮጵያንን እንኳን ለአዲሱ ዓመት 2019 ዓ.ም በሰላም አደረሳችሁ፤ አዲሱ ዓመት የሰላም፣የእድገትና የፍቅር ዘመን እንዲሆንላችሁም ልባዊ ምኞቴን እገልጻለሁ ብለዋል።
በበዓሉ ላይ መምህር ሰሎሞን በቀለ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ተገኝተዋል።