ከባሌ ጎባ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ የኮርስ ሰልጣኞች ስልጠናቸውን በተሳካ ሁኔታ በማጠናቀቃቸው በዛሬው ዕለት በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተመረቁ ።
ሐምሌ 03 ቀን 2018 ዓ/ም
በምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ጎባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቅራቢነት እና በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በመንበረ ፓትርያርክ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ስራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን ሙድኃኔ ዓለም ገዳም የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ መመሪያ ሰጭነት በተዘጋጀው ስልጠና ከባሌ ጎባ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ የኮርስ ሰልጣኞች በሰንበት ትምህርት ቤቱ የተሰጡ መንፈሳዊ ትምህርቶችን እና የኮርስ ስልጠናዎችን በተሳካ ሁኔታ በማጠናቀቃቸው በዛሬው ዕለት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተመርቀዋል።
በመርሐ ግብሩም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በመንበረ ፓትርያርክ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ስራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የበላይ ኃላፊ ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ ተገኝተዋል
ከ24 በላይ የሚሆኑ ደቀ መዛሙርት በቀን እና በሌሊት ትምህርታችቸውን በመከታተል ከ12 በላይ የሚሆኑ ትምህርቶችን አጠናቀው ለምርቃት በቅተዋል።
፩• ሀልዎተ እግዚአብሔር እና ሥነ ፍጥረት
፪• ኦርቶዶክሳዊ የስብከት ዘዴ
፫• አምሥቱ አእማደ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን
፬ • የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት
፭ • ነገረ መንፈስ ቅዱስ ፣ ነገረ ማርያም ፣ነገረ ቅዱሳን፣ ነገረ ሃይማኖት ፣ነገረ ድኅነት
፮• የሶሻል ሚዲያ አጠቃቀም
፯ • ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር
፰ • ዕቅበተ ዕምነት
፱• ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን
፲• የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ እና በዓለም መድረክ
፲፩• ሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ትምህርቶችን ተምረው አጠናቀዋል ።
በመርሐ ግብሩም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ለደቀ መዛሙርቱ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን በመልዕክታቸውም ደቀ መዛሙርት በተለያየ አጋጣሚ የተማራችሁትን ትምህርት ለማስተማር እንዲሁም ወንጌል የተራበውን ዓለም በወንጌል የምታክሙ የወንጌል ሐኪሞች መሆናችሁን አውቃችሁ ምእመኑን እውነተኛውን የክርስቶስ ቃል በቁርጠኝነት ማስተማር አለባችሁ በማለት አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
በመቀጠልም ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እናንተ በባሌ ጎባ ሀገረ ስብከት ሳትሰለቹ በትጋት እና በንቃት የክርስቶስን ወንጌል በምትችሉት ቋንቋ በማስተማር መንፈሳዊ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ ሲሉ አባታዊ መመሪያ አስተላፈዋል
በመጨረሻም ለደቀ መዛሙርቱ የምስክር ወረቀት እና የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ በረከት ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተበርከቶላቸው በጸሎት የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል ።©ምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም